1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጲያውያን ተማሪዎችና ምሩቃን ማህበር በጀርመን (DÄSAV)

ዓርብ፣ ኅዳር 10 2003

በኮሎኝ ከተማ የኢትዮጲያውያን ተማሪዎችና ምሩቃን ማህበር በጀርመንኛ ምህፃሩ(DÄSAV)ከተመሰረተ አንድ አመት ሆኖታል። እራሱን ለህዝብ ሲያስተዋውቅ ግን ያለፈው አርብና ቅዳሜ የመጀመሪያው ነው።

https://p.dw.com/p/QDO8
የኢትዮጵያውያን ተማሪዎችና ምሩቃን ማህበር በጀርመንምስል DÄSAV

በመክፈቻው ዝግጅት ላይ 140 እንግዶች ተገኝተዋል። ከሶስት ዓመት በፊት በሀሳብ ልውውጥ ተጀምሮ፤ ዛሬ በጀርመን ሀገር በማህበርነት ደረጃ እውቅናን አግኝቶ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ሊቀመንበር እስጢፋኖስ ሳሙኤል ይገልፃል። በ DÄSAV „ኢትዮጵያ ትናንትና እና ዛሬ" የተሰኘው ዝግጅት፤ ዶክተር ልጅ አስፋ ወሰን አስራተ ካሳ፣ „የጀርመን የልማትና የቴክኒክ ትብብር ድርጅት" ወይም የ GTZ ተወካይ፤ የኮሎኝ ከተማ የአፍሪቃውያን የተማሪዎች ማህበር ተጠሪ እንዲሆም ሌሎችም ግብዣ የተደረገላቸው ተገኝተው በተለያዩ ነጥቦች ላይ ሰፋ ያለ ገለፃ አድርገዋል። ከነዚህም ውስጥ ሃንስ ክርስቶፍ ቦፕል ከNRW የፍትህ ሚንስቴር አንዱ ነበሩ። „ጀርመን ለምታከናውነው የጋራ የልማት እንቅስቃሴ የበለጠ ትኩረት ከሚደረግላቸው አገሮች መካከል ኢትዮጵያ አንዷ ናት። ወደፊትም ሆና ትቆያለች። በ NRW እና በኢትዮጵያ መካለል ያለው ግንኙነት በይበልጥ እየተስፋፋ መቷል። የትምህርት ልውውጥ አለ፤ የከፍተኛ ትምህርት አጋሮች አሉ። እነዚህን ነገሮች ደግሞ ልናበረታታ ይገባናል። ለዚህም ድጋፍ አደርጋለሁ።"

በሰባት አመቷ ጀምሮ በጀርመን ሀገር የምትኖረውን ፍሬወይኒ ማማዬ የማህበሩ አባል ናት። ምክንያቷም፤ „እኔ የመጣሁት ከፍራንክፈርት አካባቢ ነው፤ ብዙ ያገሬ ሰዎች የሚኖሩበት ግን ያልተሰባሰቡበት ከተማ! እናም የዚህ አይነቱ ግንኙነት በተሻለ መልኩ እንድንሰባሰብ ዕድል ይከፍትልናል።" ትላለች።

በኮሎኝ ዮንቨርስቲ ከቀረበው „ኢትዮጵያ ትናንትና እና ዛሬ" አንዱ ክፍልም የሽልማት ስነ ሥረዐት ነበር። ሽልማቱን ያገኙት ትምህርታቸውን አጠናቀው የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን እንዲሁም 2ኛ ዲግሪያቸውን ላገኙ የማህበሩ አባላት ሲሆን ከዚያም አልፎ ደግሞ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በፕሮፌሰርነት ማገልገል ለቻለ አባል ልዩ እውቅና ተሰቷል።

ወጣቶቹ እንደሚገልፁት ይህንን ማህበር የሚያንቀሳቅሱት ከትምህርትና ከስራ ጎን ነው።

ስለ ማህበሩ ምንነት ምስረታና አላማ የበለጠ ማወቅ ከፈለጉ ዘገባውን ያድምጡ!

ልደት አበበ

ነጋሽ መሐመድ