1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢራቅ አማፅያን ግስጋሴ

ሐሙስ፣ ሰኔ 5 2006

የኢራቅ ኩርዶች የሰሜናዊቷን የነዳጅ ዘይት አምራች ከተማ የኪርኩክን አንዳንድ አካባቢዎች በዛሬው እለት በቁጥጥር ስር ማዋላቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል የዓይን ምስክሮችን ጠቅሶ ዘግቧል ። ትናንት ሞሱልንና ቲክሪትን የተቆጣጠሩት የኢራቅ ሱኒ አማፅያን ደግሞ ይዞታቸውን በማጠናከር ወደ ኢራቅ ዋና ከተማ ባግዳድ ለመገስገስ መዛታቸው ተሰምቷል ።

https://p.dw.com/p/1CHWM
Peshmerga Kämpfer Irak Archivbild 2012 bei Kirkuk
ምስል Marwan Ibrahim/AFP/Getty Images

የኢራቅ ጠቅላይ ሚኒስትር ኑሪ አል ማሊኪ የሃገሪቱ ፓርላማ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲያወጣ ቢጠይቁም አልተሳካም ። በኢራቅ ሁኔታዎች በፍጥነት በመለዋወጥ ላይ ናቸው ።አማፅያን የተለያዩ የኢራቅ ከተሞችን በእጃቸው ማስገባታቸው ቀጥሏል ። የኢራቅና የሌቫንት እስላማዊ መንግሥት የሚባለው የኢራቅ ሱኒ አማፅያን ቡድን ትናንት ከዋና ከተማይቱ ከባግዳድ በስተሰሜን የሚገኙ ዋና ዋና ከተሞችን ብዙም ሳይዋጋ መያዙ አስደምሞ ሳያበቃ ዛሬ ደግሞ የኢራቅ ኩርዶች ከራስ ገዝ ግዛታቸው ውጭ ወደ ምትገኘዋ ሁሌም ወደ ሚመኟትን ኪርኩክ ገብተዋል ። ከማክሰኞ አንስቶ ደግሞ የሱኒ አማፅያን የኢራቅ ሁለተኛይቱን ትልቅ ከተማ ሞሱልንና የቀድሞው የኢራቅ አምባገነን መሪ ሳዳም ሁሴን የትውልድ ከተማ ቲክሪትን ፋሉጃንና ሌሎች ሰሜን ባግዳድ የሚገኙ ሱኒዎች የሚያመዝኑባቸውን ከተሞች በቀላሉ ይዘዋል ። አነዚህ ከተሞች በአማፅያኑ እጅ የወደቁት የኢራቅ ወታደሮች በከተሞቹ የሚገኙ እዞቻቸውን ለቀው ከወጡ በኋላ ነው ።የነኔቬ ክፍለ ሃገር ዋና ከተማ ሞሱል በአማፅያን እጅ መግባት ሺአዎች ለሚያመዝኑበት ለኢራቁ ጠቅላይ ሚኒስትር አል ማሊኪ መንግስት ትልቅ ሽንፈት ተደርጎ ነው የተወሰደው ።አል ማሊኪ የፀጥታው ችግር በደፈናው ሴራ ያመጣው ችግር መሆኑን ተናግረው እዞቻቸውን ለቀው የሸሹት የፀጥታ ኃይሎች መቀጣት እንደሚገባቸው አስታውቀዋል።የተያዙትን ከተሞች ከአማፅያኑ እንደሚያስለቅቁም ተናግረዋል

ISIS Kämpfer Checkpoint bei Mosul 11.06.2014 Karussel
ምስል Reuters

«ኔኔቭን ከአሸባሪዎች የሚፀዱ ወታደሮችን እንደገናና በቡድን እያሰባሰብን ነው ። በሌሎች እርዳታ አንተማመንም ። ከዚያ ይልቅ ይህን ሴራ ለመቋቋም በፈቃደኝነት ጠመንጃ በሚያነሱ የኔነቬ ልጆችነው የምንተማመነው »

የኢራቅ ጦር በየከተሞቹ የሚገኙ ህንፃዎችንና የጦር መሳሪያዎችንም ጭምር ነው ለአማፅያኑ ለቆ የወጣው።አንዳንድ የፀጥታ ምንጮች እንደሚሉት ሚሊሽያዎች ወታደሮች ትተውት የወጡትን ከዋና ከተማይቱ ከባግዳድ 90 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ከተማ እየጠበቁ ነው እነርሱ እንደሚሉት ድጋፍ የሚሰጣቸው ጦር እስኪመጣ ከተማይቱ በአማፅያን እንዳትያዝ እየተከላከሉ ነው ። አል ማሊኪ በአማፅያን በተያዙት ከተሞች የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲደነገግ የሃገሪቱን ፓርላማ ጠይቀው ዛሪ ቢሰበሰብም ቁጥር ባለመሟላቱ እርምጃው ተግባራዊ ሊሆን አልቻለም ። በሌላ በኩል ዛሬ የኢራው አየር ኃይል በሞሱል የ,ማፅያን ይዞታዎችን መደብደብደቡን የሚያሳይ ምስል በኢራቅ ቴሌቪዥን ታይቷል ።።የኢራቅ ሁኔታ መባባስ ብዙዎች አሳስቧል ጀርመናዊው የመካከለኛ ምስራቅ ጉዳዮች አዋቂ ጉንተር ማየር የኢራቁ ሁኔታ እየተባባሰ መሄዱ የማይቀር ነው ይላሉ ።

Rebellen im Irak - Kirkuk
ምስል Getty Images

«ሁኔታው የሚረግብበት መንገድ አይታየኝም ። በተቃራኒው በሱኒ በሺአዎችና በኩርዶች መካከል የሚካሄደው የሥልጣን ሽኩቻ ተባብሷል ። በስተመጨረሻ ብሄራዊ አንድነቱን የሚበታትነው የኢራቅ የርስ በርስ ጦርነት ተጀምሯል ። ይህ ግጭት እንዴት በሰላማዊ መንገድ ሊፈታ እንደሚችል ማወቅ አይቻልም ።»

የሱኒ አማፅያን እርምጃ በዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ በመወገዝ ላይ ላይ ነው ። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሃፊ ባን ኪሙን የአሸባሪዎቹን እንቅስቃሴ ለመግታት ዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ በህብረት እንዲቆም ጠይቀዋል ። የሰሜን አትላንቲክ የጋራ መከላከያ ቃል ኪዳን ድርጅት በምህፃሩ ኔቶ የሱኒ አማፅያን ያገቷቸውን የቱርክ ዜጎችበአስቸኳይ እንዲለቁ ጠይቋል ። አማፅያኑ ትናንት ነበር ሞሱል ከሚገኘው የቱርክ ቆንስላ 49 የቱርክ ዜጎችን ያገቱት ። የቱርክ መንግሥት ዜጎቹን ለማስለቀቅ ኢራቅ ከሚገኙ ቡድኖች ጋር እየተነገጋረ መሆኑን አስታውቋል ።

ሂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ