የአፍጋኒስታን የመገናኛ ብዙኃን
ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 16 2004አፍጋኒስታን ውስጥ 170 የሬዲዎ እና 60 የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ይገኛሉ። እንዲሁም ከ100 የሚበልጡ ጋዜጦች። ይህም ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ ከፍ እያለ ነው። ይሁንና ከእነዚህ ጣቢያዎች እና ዕለታዊ ጋዜጣዎች አንዳቸውም ራሳቸውን ማስተዳደር አይችሉም። ገንዘቡ ብዙ ጊዜ ከውጪ ነው የሚመጣው። ይህን የአፍጋኒስታን የስለላ ድርጅት ቃል አቀባይ ሉትፉላህ ማሻል ከጥቂት ቀናት በፊት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስረድተዋል። « ታማዶን የተባለው የቴሌቪዥን ጣቢያ ከአንድ ወር ጀምሮ በካንዳሐር NATO እና የዮናይትድ እስቴትስ ወታደሮች የሚፈፅሙት ነው ያለውን ወንጀል የያዙ ዘገባዎች እያቀረበ ነው። ሀቁ መረጃ ግን እነዚህ ዘገባዎች ሆን ተብለው ለፕሮፓጋንዳ እንዲያገለግሉ ከኢራን ተዘጋጅተው የቀረቡ ናቸው።
ማሻል ከታማዶን የቴሌቪዥን ጣቢያ ጎን ሌሎች ኑር፣ ካቡል ኒውስ እና ምሻል የተባሉ የቴሌቪዥን ጣቢያዎችን ስም ዘርዝረዋል። ከዚህም ሌላ ኤንሳፍ የተሰኘውን የዕለታዊ ጋዜጣ የጎረቤት ሀገር ቱልቱላ ነው ሲሉ ተችተዋል። የጋዜጣው አንባቢያን ማሻል የጎረቤት ሀገር ሲሉ ኢራንን ማለታቸው እንደሆነ ያውቃሉ። ይህ ጋዜጣ ሁል ጊዜ የኢራንን አመራር እንዳወደሰ ነው። የዚህ ጋዜጣ አላማ ይላሉ ማሻል፤ ለታሊባን ሁኔታዎችን ለማመቻቸት እና በውጭ አገር ሰዎች አንፃር በሀገሪቱ ጥላቻ ለማስፋፋት ነው። በርካታ የፓኪስታን ዜጎች ያለ ህጋዊ ፍቃድ ተቀጥረው የሚሰሩበትን ሻምሻድ የተሰኘውን የቴሌቪዥን ጣቢያ ማሻል በምሳሌነት ጠቅሰዋል።
« የዚህ የቴሌቪዥን ጣቢያ የፕሮግራም እና የፋይናንስ ኃላፊዎች ፓኪስታናዊያን ናቸው። የዘገባው ርዕሰ ጉዳዮች የሚወሰኑት እዚያው ፓኪስታን ውስጥ ነው። የኛ ባለስልጣናት እንኳን የነዚህ ሰዎች ማንነት አያውቁም። የስራ ፍቃድም ሆነ ህጋዊ ቪዛ ይኑራቸው አይኑራቸው አናውቅም።»
ማሻል የኢራንን እና የፓኪስታንን ስም በግልፅ ሳይጠሩ በጥቅሉ «አንዳንድ የአፍጋኒስታን ጎረቤት አገሮች» ካቡል ከ ዮናይትድ እስቴትስ ጋ ያላትን ቀጣይ የትብብር ስራ ለማክሸፍ ይጥራሉ ብለዋል። ወቀሳ የቀረበባቸው ጣቢያዎች ግን ይህንን ወቀሳ አጣጥለዋል። ይህ ቀውስ ብዙዎችን አላስገረመም ብዙዎችን ያስገረመው ግን የአፍጋኒስታን መንግስት ግልፁን ወቀሳ መሰንዘሩ ነው። ምክንያት እና ስማቸው በተዘረዘረው አንዳንድ ጣቢያዎች ውስጥ ከፍተኛ ተፅዕኖ ያላቸው የአፍጋኒስታኑ ፕሬዚዳንት ሐሚድ ካርዛይ የቅርብ ሰራተኞች አሉበት። አንዳንድ ካቡል ያሉ የመገናኛ ብዙኃን ተመራማሪዎች እንደሚሉት ምናልባት ካርዛይ በዚህ አጋጣሚ ሰራተኞቻቸው የሚጫወቱትን መንታ ሚና ለማጋለጥ ፈልገው ይሆናል። አፍጋኒስታን የሚገኘው የ PRESS WATCH ድርጅት ባልደረባ ፀዲቁላ ታውሀዲ የአፍጋኒስታን መንግስት ለዚህ በአፋጣን አንድ መፍትሄ ሊያገኝለት ይገባል ይላሉ።
« የአሁኑ ሁኔታ በቅርቡ ካልተለወጠ እነዚህ ጣቢያዎች የተነሳ አፍጋኒስታን ውስጥ የርስ በርስ ጦርነት ሊከፈት ይችላል። እነዚህ ጣቢያዎች የጠላት መደበቂያ ይሆናሉ።»
ፈጣኝ መልስ ግን ከአፍጋኒስታን መንግስት በአሁኑ ሰዓት የማይታሰብ ነው። ወቀሳውን እያጣራን ነው የሚል ምላሽ ብቻ ነው ከለስልጣናቱ ማግኘት የተቻለው።
ሻሜል ራትቢ
ልደት አበበ
አርያም ተክሌ