1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍጋኒስታኑ ጋዜጠኛ ፋሂም ዳሽቲ፤

ረቡዕ፣ ሐምሌ 20 2003

ለብዙዎቹ የአፍጋኒስታን ተወላጆች፤ እ ጎ አ መስከረም 11, 2001 ሳይሆን መስከረም 9,2001 የማይረሳ ዕለት ተብሎ የሚታሰበው።

https://p.dw.com/p/Rcc5
የሰሜን አፍጋኒስታን ተጓዳን ንቅናቄ ፤ የጦር መሪ የነበሩት፣ አህመድ ሻህ ማሱድ፣ምስል AP

በዚያች ዕለትም ነበረ፤ የኧል ቓኢዳ አሸባሪዎች በዚያች ሀገር እጅግ ከታወቁት የተቃውሞ ታጋዮች መካከል አንዱን ፤ አህመድ ሻህ ማሱድን ለመግደል አልመው የተንቀሳቀሱት። በጦር ስልት አወጣጥ እጅግ የታወቁት የሰሜን ጥምረት(North Alliance) የተሰኘው የሰሜን አፍጋኒስታን ንቅናቄ ፤ ሰሜናዊውን የአገሪቱን ከፊል ታሊባኖች እንዳይቆጣጠሩት የመከተ የሚፈራ ኃይል ነበረ።

ግን ምን ያደርጋል! በዚያች ዕለት የሆነው በህይወት ዘመኔ ሁሉ የማይረሳ ነው ይላል አሁን የ 38 ዓመት ጎልማሣ የሆነው፤ የፕረስ ነጻነት ታጋይ ፋሂም ዳሽቲ።

ኧል ቓኢዳ ለተልእኮ ያሠማራቸው ፊልም አንሺ መሳይ ሰዎች፤ ካሜራቸው ፊልም የሚያጠነጥን ሳይሆን ፈንጂ የሚተኩስ ነበረ። እናም ፣ በመጀመሪያው ዙር አንዳንድ ሰዎች ወዲያው ነበረ ህይወታቸው ያለፈች። በአፍጋኒስታን የሶቭየቶችን ጣልቃ-ገብነት በመቃወም ጀግንነቱን ያሥመሠከረውና በኋላም የታሊባኖች ፀር የነበረው ፤ ታላቅ ተሰጥዖ የነበረው የጦር መሪ አህመድ ሻህ ማሱድም ህይወት አለፈች። የፋሂም ዳሽቲ መትረፍ ተዓምር ነው፣እንዳጋጣሚ ፤ በግማሽ ሜትር ርቀት ብቻ ከእነርሱ አጠገብ ተቀምጦ ነበረና!። እርግጥ ሰውነቱ በፈንጂው ወላፈን ቆሳስሎ ፤ ፀጎጉሩም ተቃጥሎ ነበር።

ፋሂም ዳሽቲ፤ ከማሱድ ጋር የነበረው ግንኙነት ከአእምሮው የማይጠፋ ነው። ሁለቱም የፓንድሺር ሸለቆ ተወላጆች ናቸው። እስከአፍንጫው ታጥቆ የነበረውን ወራሪውን የሶብየት ጦር መፋለም የተጀመረበት ቦታ ነው፤ያ ሸለቆ!። እናም ፤ ዳሽቲ፤ማሱድን ከሀገር ፍቅር ጋር ነው የሚያቆራኘው። እስካሁን ድረስ፤ በዚያ ሸለቆ ከጥቅም ውጭ የሆነ የታንክ ሥብርባሪ ይገኛል። የሶቭየት ቀይ ጦር ፤ 7 ጊዜ በአየር ኃይልና በእግረኛ ጦር የማጥቃት እርምጃ አንቃሳቅሶ ነበረ። ግን ሸለቆውን በሙሉ መቆጣጠር ሳይቻለው ቀርቷል።

ያ የተሳካ መከላከል ፤ ምንጊዜም አርአያ አድረጎ የሚመለከተው የማሱድ ሥራ ነበረ። ዳሽቲ፤ የማሱድ ህዝባዊ ጦር የከፍተኛው ተዋጊ ኃይል አባል ለመሆን ነበረ የሚጓጓው። ይሁን እንጂ ወደ ካቡል በመጓዝ መጀመሪያ ትምህርቱን ይጨርስ ዘንድ ማሱድ ላከው። ከዚያም ትምህርቱን እንዳገባደደ፤ የሙጃሂዲኖች ዘጋቢ ሆነና የማሱድን አስተዋጽዖ የሚያሳይ ዘጋቢ ፊልም ለማዘጋጀት ተነሣሣ። እ ጎ አ በ 1993 «ካቡል ዊክሊ» የተሰኘውን የማሱድ ፓርቲ ሳምንታዊ ጋዜጣ ማሳተም ጀመረ። ጋዜጠኛነቱን ሲጀምርም፤ የሚታወሰው ያልተቋረጠ ተኩስ፣ ጦርነት ነው። የቦንብ ፍንዳታ! ሰዎች በውጊያ ሲሞቱ፣ መመልከት የተለመደ ሁኔታ ነበረ ይላል። ግን ወጣት ነበርሁና ፤ ስለዚያ መዘገብ እንዲሁ ሥራ ነበረ የሚመስለኝ። በ 2002 እ ጎ አ፤ ዳሽቲ ፤ እንደገና «ካቡል ዊክሊ» የተሰኘውን ጋዜጣውን በአዲስ መልክ ማዘጋጀት ጀመረ። በታሊባኖች የአገዛዝ ዘመን የሆነው ሆኖ በጦርነት ሳቢያ በሚል ሰበብ ከህትመት ውጭ ሆነ ። ዳሽቲ፣ ከመጀመሪያውም ትክክለኛ ሥራ ካልተሠራ ሳያመነታ የሚቀወም ነበረና ፤ የካርሳይን አገዛዝም ከመንቀፍ አልቦዘነም።

ካርሳይ ፣ የጎሳዎች ቡድን በመሸንገል እንጂ የዴሞክራሲ መርኅን በመከተል የሚሠሩ እንዳልሆኑ ዳሽቲ ይናገራል። አንድ ከፈተኛ ባለሥልጣን በመኪና አደጋ ልትሞት ትችላለህ የሚል ማስጠንቀቂያም ሆነ ዛቻ እንዳሰሙትም አስታውቆ ነበር።

እ ጎ አ በ 2009 በአፍጋኒስታን ምርጫ ተካሄደ። ከአንድ ሚሊዮን በላይ የህዝብ ድምፅ ተጭበርብሯል። «ካቡል ዊክሊ» ሒስ አቀረበ። የካርሳይን የምርጫ ዘመቻ በገንዘብ ሲደግፉ የነበሩና በተጠቀሰው ጋዜጣም ማስታወቂያ በማውጣት ገንዘብ ይከፍሉ የነበሩ ከበርቴዎች ፤ ከጋዜጣው ጋር የነበራቸውን ውል አፍርሰዋል። የጋዜጣው ገቢ በእጅጉ ቢቀንስም፤ ካለፈው መጋቢት አንስቶ በማንሠራራት ላይ ነው።

ዳሽቲ ፤ ከበርቴዎችን ይበልጥ የሚያሳድገው ድሃውን ይበልጥ የሚያደኸየው የኤኮኖሚ ሥርዓት በእርሱም ላይ ዘመቻ እንዳካሄደበት ይሰማዋል።

የምዕራቡ ዓለም ተልእኮ ፣ ብዙ አዎንታዊ ሁኔታዎች ሊቀሰሙበት እንደሚችል የገለጠው ዳሽቲ፤ በ 5000 ዘመን ታሪኳ፣ አፍጋኒስታን የወጭ ኃይሎችን በምድርዋ ስታስተናግድ የመጀመሪያ ጊዜ ነው ይላል። የአሁኑ ይዞታ አጠራጣሪ መሆኑን የሚናገረው ዳሽቲ፤ ከታሊባኖች ጋር መደራደር የማይሞከር ነው ባይ ነው። እ ጎ አ እስከ 2014 «ኔቶ» ነቅሎ የሚወጣበት መርኀ-ግብርም አላማረኝም ባይ ነው። የመውCA አቅድ ነድፎ ማሳወቅ ስህተት ነው ፤ እኛ አፍጋኒስታን፤ ብዙም አይቀርብንም። ጥቂት ት/ቤቶችንና ሀኪም ቤቶችን ልናጣ እንችላለን። ጥቂትም ይሞቱብናል። ባለፉት 30 ዓመታት ከ 2 ሚልዮን በላይ ህዝባችን ህይወቱን አጥቷል። ነገር ግን ያሁኑ የአፍጋኒስታን ጦርነት በተሣካ ሁኔታ ካልተደመደመ፣ እናንተ ትሆናለችሁ፤ ነገ ጦርነቱን በርሊን ፤ ፓሪስ፤ ለንደን፤ ማድሪድና አሜሪካ ውስጥ መምራት ግድ የሚሆንባችሁ!ሲል ፋሂም ዳሽቲ ያስጠነቅቃል።

ማርቲን ጌርነር

ተክሌ የኋላ