1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፋን ኦሮሞ ትምህርት በኢትዮጵያ ከፍተኛ ተቋማት

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 4 2010

«በጎርጎረሳዉያኑ 1842 አካባቢ ሉድቪግ ክራፍ የተባለ ጀርመናዊ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ሳለ ኦሮምኛን ለማስተማር አንድ የኦሮምኛ ስዋስዉ ንድፍን ጽፎአል።ሉድቪግ የሥነ ቋንቋ ተመራማሪ ስለነበር፤ ኦሮምኛ የተለያዩ ድምፀት ያላቸዉን ፊደላት ለማዉጣት አስቸጋሪ በመሆኑ በአማርኛ ፊደላት ሊከብድ ይችላል ብሎ ይህንን ንድፍ ፅፎ ማቅረቡም ይነገራል። 

https://p.dw.com/p/2vxFw
Afaan Oromoo Logo
ምስል Yemane Bayesa

የአፋን ኦሮሞ ትምህርት በኢትዮጵያ ከፍተኛ ተቋማት

«የኦሮምኛን ቋንቋ ከላቲን በወሰደዉ ፊደላት አጣርሶ ለመፃፍ ሞክሮአል። ሉድቪግ የዝያን ጊዜ የጻፋቸዉ ቃላቶች ዛሬ የሚታየዉን አይነት ቁቤ ግን አይደለም። ከዝያ ወድያ የመጣዉ የቁቤ ጽሑፍ ይመስለኛል ወደ 1970ዎቹ አካባቢ« ፊርማተ ዱቢ» የሚል አንድ መጽሐፍ ወጥቶአል። ደራሲዉ ማን እንደሆን አላዉቅም። ግን በየጊዜዉ ኃይሌ ፊዳ ነዉ ይላሉ። በሌላ በኩል ደግሞ የሃርርጌ ክፍለሃገሩ ዶ/ር ረሻድ አብዱሌ ቁቤን ሲጠቀሙ እንደነበር የሚያሳዩ መረጃዎች አሉ። እና በላቲን ፊደላት የኦሮምኛ ቋንቋን መጻፍ መቼ ተጀመረ ለሚለዉ ነገር አንዳንዱ 16 ኛዉ ክፍለ ዘመን አንዳንዱ 17 ኛዉ ሌላዉ 18ኛዉ ክፍለ ዘመን ሲል ይናገራል። ግን የተፃፈ ነገር የተገኘዉ እኔ እስከማዉቀዉ 1840ዎቹ ዉስጥ ነዉ። ሌላዉ በ 1970ዎቹ ዉስጥ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር «ኦነግ» ቡድን የፅሑፍ መግባብያቸዉ ብሎም ቋንቋዉን በጽሑፍ ለመማር ይጠቀሙበት እንደነበር መረጃዎች አሉ»  

በጅማ ዩንቨርስቲ ለረጅም ዓመታት በሥነ-ቋንቋ ትምህርት ዘርፍ በረዳት ፕሮፊሰርነት ያገለገሉትና በአሁኑ ወቅት በኦስሎ የሥነ ቋንቋና የሥነ ፆታ ትምህርት የዶክትሬት ዲግሪያቸዉን በመስራት ላይ የሚገኙት አቶ አማኑኤል ራጋ ነበሩ። የኦሮምኛ ቋንቋ አፋን ኦሮሞ በኢትዮጵያ በሚገኙ የተለያዩ ከፍተኛ ተቋማት መሰጠት ከጀመረ ከአስር ዓመታት በላይ ማስቆጠሩን የዘርፉ ባለሞያዎች ይናገራሉ። በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የምርምር ቋንቋ ሆኖ በማገልገል ላይ የሚገነዉ የኦሮምኛ ቋንቋ እድገቱን በማጠናከር በተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች በመጀመሪያ በሁለተኛና በሦስተኛ ድግሪ ጭምር በሺዎች የሚቆጠሩ ብቁ ዜጎችን በማፍራት ላይ እንደሚገኝ የቋንቋዉ ምሁራን ይገልፃሉ። በቅርቡ የባህርዳር ዩንቨርስቲ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም፤ አፋን ኦሮሞ ማለት የኦሮምኛ ቋንቋ ትምህርትን ለመጀመር ዝግጅቱን በማጠናቀቅ ላይ እንደሆነ ገልፆአል። ይህም በአማራ ክልል ቋንቋዉ ከኬሚሴ ዞን ለጥቆ በከፍተኛ ተቋም ደረጃ በምርምር ቋንቋነት ለማገልገል ሲዘጋጅ የባህርዳር ዩንቨርስቲ የመጀመርያዉ እንደሆነም ተገልፆአል።  የኦሮምኛ ቋንቋ አፋን ኦሮሞ የፌዴራል መንግስቱ የስራ ቋንቋ ይሁን ሲሉ የሚጠይቁ ጥቂቶች አይደሉም።

Haramaya Universität Äthiopien
ምስል DW/G. Godae

ሂዩማኒቲስ ፋኩልቲ፤ ይሰኛል የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲን ጨምሮ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሠብዓዊ ሳይንስ፤ የአፋን ኦሮሞ አማርኛ፤ ትግርኛን እና የተለያዩ የዉጭ ቋንቋዎችና የጋዜጠኝነት ትምህርት የሚሰጥበት ኮሌጅ። በባህርዳር ዩንቨርስቲ ዉስጥ በሚገኘዉ በዚሁ የተለያዩ የግዕዝ ቋንቋን ጨምሮ የተለያዩ የዉጭና የአገር ዉስጥ ቋንቋዎች የሚሰጥበት ኮሌጅ አፍን ኦሮሞን ማለትም የኦሮምና ቋንቋ ትምህርትን ለመስጠት ዝግጅቱን በማጠናቀቅ ላይ እንደ ሆነ ገልፆአል። በባህርዳር ዩንቨርስቲ ዉስጥ የሂዩማኒቲስ ኮሌጅ ዋና ተጠሪ ዶ/ር ዳዊት አሞኘ እንደነገሩን አፋን ኦሮሞን በሰeተፊኬት ደረጃ ለመማር ምዝገባ ጀምረናል።  

«ሰርተፊከት ፕሮግራም ያልነዉ በዩኒቨርስቲ ዉስጥ ብዛሃነት ያለ በመሆኑ ፤ ዩንቨርስቲዉ የፌደራል መንግስቱ በመሆኑ ከዚህ በተጨማሪ በዩኒቨርስቲያችን የሚገኙ  የኦሮሞ ተማሪዎች ቁጥር ከፍተኛ እየሆነ በመምጣቱ ብሎም ቋንቋዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ካለዉ ጠንካራ መሰረት የተነሳ ፤ ይህን የስልጠና መረሃ ግብር ብንከፍት በሚል ቆየት ያለ እቅዳችን ነዉ» ከዘጠኝ ዓመት በፊት ማለትም በ2001 ዓ.ም የመጀመርያዎቹ 26 የአፋን ኦሮሞ ተማሪዎች ከአዲስ አበባ ዩንቨርሲተ መመረቃቸዉን ከ2003 ዓመት ጀምሮ ደግሞ በዩንቨርስቲዉ በኮሌጅ ደረጃ በቋሚነት ቋንቋዉ መሰጠት መጀመሩን የነገሩን የትምህርት ክፍሉ የወቅቱ ሊቀመንበር እና በትምህርት ክፍሉ የሥነጽሑፍና የባህል ትምርት መምህር ዶ/ር ጥላሁን ተሊላ፤ ወደ ኮሌጁ ለመግባት የሟሟያ ነጥብ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።   

«ተማሪዎቻችን እንደማንኛዉም ተማሪ የዩኒቨርስቲ መግብያ ነጥብን ያሟሉ ናቸዉ በምርቻም ነዉ የሚገቡት እናም የምናስተምረዉ ቋንቋዉን ሳይሆን የቋንቋዉን ሳይንስ ነዉ። ቋንቋዉን ለመማርያነት ለመግበብያነት የሚፈልጉ እንዲህ አይነት ጥያቄዎችን በአጎራባች እናስተናግዳለን።»

ዶ/ር ጥላሁን ተሊላ፤ ቋንቋዉን በአግባቡ ለማስተማር የቁሳቁስ አቅርቦቱ በቂ ነዉ ይላሉ?

«በቂ ነዉ አይደለም ብሎ ለመመለስ ትንሽ ያስቸግራል። አሁን ባለበት ደረጃ ብቁ ነዉ የሚል አመለካከት አለን። የመጀመርያ ምሩቃንን ከማስተማር ጀምሪ ነዉ በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ በሚገኘዉ የቋንቋ ኮሌጅ የምገኘዉ። በርግጥ በዝያ ወቅት አንዳንድ የማስተማር ሂደት ላይ እቸገር ነበር ። በተለይ ቋንቋዉን በማስተማር ዙርያ አፋን ኦሮሞ ቃላዊ የሆኑ በርካታ አገላለፆች አሉት፤ ያንን  ወደ ጽሑፍ በማምጣት ፤ ሌሎች የጻፉዋቸዉ እና በተለይም በመንግሥት ደረጃ 17 ሺህ የሚባል መረሃ ግብር ነበር፤ ለዝያ የተዘጋጁ ሞዱሎች ነበሩ። የመመረቅያ ፅሑፎችም እንደማስተማርያነት እያገለገሉ አሁን ባለበት ደረጃ የተሻለ ነገር እጃችን ላይ አለ፤ በርግጥ የሚቀረዉ ነገር አለ» 

Logo Haramaya Universität Äthiopien

የአፍን ኦሮሞ ትምህርትን በመስጠት የሃረማያ ዩንቨርስቲ የመጀመርያዉ ነዉ ያሉን በተቋሙ የቋንቋዉ መምህርና በቋንቋዉ እንዲሁም በኦሮሞ ባህል ላይ ጥናትና የጥናት ፅሁፎችን በማቅረባቸዉ የሚታወቁት ዶክተር የማነ ባይሳ ናቸዉ። 

«በሃረማያ ዩንቨርስቲ ሳገለግል ከአስር ዓመት በላይ ሆነኝ። በርግጥ በሃረማያ ስቀጠር በበተቋሙ የኦሮምኛ ቋንቋ ትምህርት ይሰጥ ነበር። ሃረማያ ዩንቨርስቲ ኢትዮጵያ ዉስጥ ካሉ ዩንቨርሲዎች መካከል አፋን ኦሮሞን መስጠት የጀመረ የመጀመርያዉ ተቋም ነዉ።

ዶክተር የማነ ባይሳ፤ የአፋን ኦሮሞ ማለት የቁቤ ጽሑፍ አንዳንድ ችግር አለዉ ሲባል ይሰማል በዚህ ላይ ምን አስተያየት አሎ?

«የሥነ- ልሳን ባለሞያዎች እንደሚሉት ቁቤ ጽሑፍ በሳይንሳዊ መንገድ ሲታይ ምንም አይነት ችግር የለዉም። ቁቤ በተለያዩ ችግሮች ምክንያት ነዉ ከላቲን ፊደል እንዲቀረፅ የሆነዉ ። አፋን ኦሮሞ ሕግጋቱ ብዙም አይደለም ዉስን ነዉ። ወደ አምስት መሰረታዊ ሕግጋቶች አሉት። ያንን ሕግ ተከትሎ ቋንቋዉን ለመጻፍ እና ፊደሎችንም በተገቢዉ መልክ ለመጠቀም ፤ ቋንቋዉን በትክክል ለመግለጽ ተብሎ የታሰበ ነዉ። በቁቤ አጻጻፍ ምንችግሮችና ተግዳሮቶች አሉት በሚል የተለያዩ የጥናት ጹሑፎች ቀርበዋል። ነገር ግን በቋንቋዉ ተናጋሪዎች ላይ ስናይ ምንም ችግር የለዉም። በአፋን ኦሮሞ ተመሳሳይ ቋንቋዎች በብዛት ይገኛሉ። በማርዘም በማጥበቅ በማላላት አንዱ ከአንዱ ይለያሉ የሚል የቋንቋዉ ሳይንስ አለ። ስለዚህም ይህን ሁሉ ስናይ የቄቤ ፊደል ተገቢ ፊደል ነዉ ብዬ አምናለሁ»            

ቁቤ ፊደል የኦሮምኛ ቋንቋ አመልን ተከትሎ የወጣ ነዉ ያሉት ለረጅም ዓመታት በጅማ ዩንቨርስቲ መምህር የነበሩት የሥነ ቋንቋ ምሁሩ አቶ አማኑኤል ራጋ ናቸዉ።

«አንድ ቋንቋን በጽሑፍ ለማቅረብ መጀመርያ ብዜ ጥናት ተደርጎበት ነዉ። ብዙዎች የአፍሪቃ ቋንቋዎች ጽሑፍ የላቸዉም። ያማለት ፊደል የላቸዉም እነዚህ ቋንቋዎች ወደ ፊደል ሲቀየሩ ምርጫዎች ይኖራሉ። ለምሳሌ በሶማልያ ወደ 1970 አካባቢ የአረብኛ ፊደላትን ተጠቅመዉ ሲጽፉ ነበር። ሌላ ሃገራትም እንዲሁ ተመሳሳይ ነገር ታይቶአል። በዚሁ አኳያ ነዉ የሃገራችንም አፋን ኦሮሞ የላቲንን ፊደል ወስዶ ወደ ኦሮምኛ ቋንቋ ሲመጣ ፤ የኦሮምና ቋንቋን ዓመል ተከትሎ ነዉ የቀረበዉ ተቀባይነቱም ትልቅ ነበር።  በተጨማሪ ኮንፒዉተር አካባቢ ያለዉን ነገር ስናይ በኢትዮጵያ በኦሮሚያ የራሱ የሆነ ሶፍት ዌር ለማግኘት የኤኮኖሚ ችግር ይረዳል። 

በአፍሪቃ በብዛት ከሚነገሩት አምስት ቋንቋዎች መካከል ኪስዋሂሊን ጨምሮ በናይጀርያ የሚነገረዉ የኢርቦ ቋንቋ አማርና እንዲሁም ኦሮምና ይገኝበታል ያሉት በሃ,ማያ ዩንቨርስቲ የአፍn ኦሮሞ ምሁሩ አቶ የማነ ባይሳ ቋንቋዉን ለማሳደግ ጥረት መደረግ አለበት ሲሉ ይናገራሉ። የሥነ ቋንቋ ምሁሩ አቶ አማኑኤል ራጋ በበኩላቸዉ ቋንቋዉን የሃገሪቱ ቋንቋ ለማድረግ ብዙም የሚቸግር ነገር አይኖርም ባይ ናቸዉ። የባህርዳሩ የሂማኒise ኮሊጅ ዋና ተጠሪ በበኩላቸዉ ሌሎች በኢትዮጵያ የሚገኙ የከፍተኛ ተቋማትም የባህርዳር ዩንቨርስቲን በምሳሌነት ማየት ይገባቸዋል ሲሉ ጥሪያቸዉን ያስተላልፋሉ።

ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምፅ ማዕቀፉን ይጫኑ  

አዜብ ታደሰ

ሂሩት መለሰ