1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአይቮሪኮስት መፃዒ እጣ ፈንታ

ሰኞ፣ ጥር 1 1998

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰላም አስከባሪ ጦር ከፈረንሳይ ጋር በመተባበር አረጋግቷታል ተብሎ የተገመተዉ አይቮሪኮስት እንደታሰበዉ የተረጋጋች አትመስልም። ገና ጥቂት ቀናት ያስቆጠረዉ የፈረንጆቹ 2006ዓ.ም. ለአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ከባድ ፈተና ይዞ ቀርቧል። በዓመቱ መጀመሪያ ሳምንትም ከመዲናዋ አቢጃን በስተምስራቅ ብዙም ባልራቀዉ የአኩዌዶ ወታደራዊ ካምፕ ላይ የተሰነዘረዉን ጥቃት ማን አደረሰዉ እንዴትስ ተጠያቂዉ አካል ይዳኝ የሚለዉ ብዙ የሚያለፋ

https://p.dw.com/p/E0jB

��ዉ እንደሚሆን ተገምቷል። የአገሪቱም እጣ ፈንታ ምን ይሆን የሚለዉ የሚያነጋግር ሆኗል።

አዲሱ ዓመት በባተ በሁለተኛዉ ዕለት ነበር ያልታወቀዉ ቡድን በአኩዋዶ ወታደራዊ ሰፈር ላይ መዓቱን ያወረደዉ።
በወቅቱም ሶስት የመንግስት ወታደሮች ሲገደሉ ከጥቃት አድራሾቹ ወገንም በርካቶች ሞተዋል የሚሉ ቢኖሩም በተጨባጭ ሰባት መሆናቸዉ ተነገረ።
አምስት የመንግስት ወታደሮች ከአደጋ አድራሾቹ ጋር ግንኙነት አላቸዉ በሚል ጥርጣሬ መታሰራቸዉ ቢነገርም የመንግስት ባለስልጣናት ሁኔታዉን አስተባብለዋል።
በመንግስት ወታደሮችና በባለስልጣናት መካከል በደሞዝ ሳቢያ መቃቃር መፈጠሩ ሲነገር ባለስልጣናቱ የወታደሮቹ ጥያቄም ሆነ የተባለዉ አለመግባባት እንደሌለ ነዉ የሚናገሩት።
በአቢጃን የመንግስት ሰራተኛ የሆኑት አንቶኒ ኮፊ እንደሚሉት የአኩዌዶ ጥቃት ወታደራዊ ተቃዉሞን ለማሳየት የተወሰደ መሆኑ ብዙም አያስገርምም።
እንዲህ አይነቱ የተቃዉሞ እንቅስቃሴ በአይቮሪኮስት የተጀመረዉ የወቅቱን ፕሬዝደንት ሄንሪ ኮናን ቤዲን ለመገልበጥ በጀነራል ሮበርት ጉዊኒ የዛሬ ሰባት ዓመት በታህሳስ ወር መገባደጃ ሲሆን በቀላሉ ይቆማል የሚል እምነት እንደሌላቸዉም ይገልፃሉ።
ቤዲን ለመገልበጥ በአይቮሪኮስት የተካሄደዉ በታሪክ የመጀመሪያ የሆነዉ እርምጃ በአገሪቱ ላለዉ ብጥብጥ በር ከፋች መሆኑ ይነገርለታል።
በድጋሚም በፈረንጆቹ 2002ዓ.ም. ሎረንት ገባግቦ ፕሬዝደንትነትን አልመዉ ያካሄዱት መፈንቅለ መንግስት የቅርብ ጊዜ ትዉስታ ነዉ።
ከዚያ ወዲህ በሰሜናዊቷ አፍሪካ አገር በአይቮሪኮስት የሰሜን ግዛቷ በአማፅያን ቁጥጥር ስር ዉሎ ደቡቡን መንግስት ያስተዳድረዉ ገባ።
ሁለቱን ግዛቶች የሚያማክለዉ አካባቢም በተባበሩት መንግስታትና በፈረንሳይ ሰላም አስከባሪ ጦር ቁጥጥር ስር ሆነ።
ካለፈዉ ማክሰኞ ወዲህም ወታደራዊ አዛዡ አንጌ ኬሲ ኩዋሜ ሰኞ ዕለት የተፈፀመዉን ጥቃት ሲመረምሩ ግጭት ተቀስቅሶ ወታደራዊ ሰፈሩ ወደባሰ ዉጥረት ዉስጥ ገብቷል።
ባለፈዉ ሳምንት በሰፈሩ የደረሰዉ ጥቃት ባለፉት ወራት በተለያዩ የፖሊስና የወታደራዊ ተቋማት ላይ የደረሱት ጥቃቶች አካል መሆኑ ተመልክቷል።
ባለፈዉ ታህሳስ ወር በአቢጃን የሚገኘዉ ትልቁ ብሄራዊ የፖሊስ ተቋም እንደዚሁ ባልታወቁ ጥቃት አድራሾች ጉዳት ደርሶበታል።
የተወሰኑ የመንግስት ባለስልጣናት ለደረሱት ጥቃቶች የአማፅያኑን ቡድን በተጠያቂነት ሲከሱ በተቃራኒዉ አማፅያኑ ወደገባግቦ፤ ጀነራል ፊሊፕ ማንጉና ከጦሩ ወዳፈነገጡት ዋና አዛዥ ኢብራሂም ኩሊባሊ ጣታቸዉን ጠቁመዋል።
ከዚህ ሁሉ አልፎም ባለፈዉ ወር የሞቱት የተቃዋሚ ፓርቲዉ መሪ የአላሳኒ ዖዋታራ እናት መቃብር ከተቀበሩ ከጥቂት ቀናት በኋላ ተቆፍሯል።
ይህ ሁሉ ሁኔታ በአይቮሪኮስት መከስት የጀመረዉ አሁን በህይወት የሌሉት ጉዊኒ ከዛሬ ሰባት ዓመት በፊት ካካሄዱት መፈንቅለ መንግስት ወዲህ ነዉ የሚሉ በርካቶች ናቸዉ።
ዖዋታራ በ2000 ዓ.ም. ላይ በተካሄደዉ ፕሬዝደንታዊ ምርጫ እንዳይሳተፉ ለማድረግ በአገሪቱ ህገ መንግስት አይቮሪኮስታዊ ትዉልድ የሌለዉ እንዳይሳተፍ የሚያግድ የህግ ማሻሻያ ተጨምሮበት ነበር።
የተቃዋሚዉ ፓርቲ መሪና የቀድሞዉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዖዋታራ ሙስሊም ከሚበዛባት ከሰሜናዊ አይቮሪኮስት የተገኙ ለደቡቡ ክፍል መድሎ ይደረጋል በሚል ሲቃወሙ የኖሩ መሆናቸዉ ይታወቃል።
የዲፕሎማቲክ ምንጮች እንደገለፁት ባለፈዉ ሳምንት መጀመሪያ በወታደራዊ ሰፈሩ የደረሰዉ ጥቃት በአዲሱ የአገሪቱ አስተዳደር እምነት መጣል እንደማይቻል የሚያመላክት ነዉ።
ጥቃቱ የደረሰዉ የኮናኖ ቤኒ የሽግግር መንግስት በተመሰረተ በጥቂት ጊዜያት ዉስጥ ሲሆን ይህ መንግስት በአገሪቱ የሚገኙትን የተለያዩ ኃይላት ትጥቅ አስፈትቶ በሰላማዊ መንገድ ወደምርጫ ለማምጣት አልሞ ነበር።
ይህም የአዲሱ የአይቮሪኮስት ጠቅላይ ሚኒስትር አገሪቱን ለማረጋጋት በሚያደርጉት ጥረት የሚጠብቃቸዉ ፈተና እንደሚሆን ተገምቷል።
በአገሪቱ ባለፈዉ ጥቅምት ሊካሄድ ታስቦ የነበረዉ ምርጫ ወደመጪዉ ዓመት ጥቅምት ወር ተሸጋግሯል።
አይቮሪኮስት በዓለም ከፍተኛ የካካዖ አምራች እንዲሁም በግንባር ቀደምትነት ቡና ላኪ አገር ናት።