1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአዉሮፓዉ ህብረት እና የስደተኞ ጉዳይ

ማክሰኞ፣ ጥር 8 1999

የወቅቱ የአዉሮፓ ህብረት የፕሪዝደንትነት ስልጣን የያዘችዉ ጀርመን በህብረቱ አባል ሐገራት የሚኖሩ ስደተኞች መብትን ለማስከበር እንድትጥር አሚስቲ ኢንተርናሽናል ጠየቀ

https://p.dw.com/p/E0hQ

የአዉሮፓዉ ህብረት እና አባል መንግስታቱ ስለ ስደተኞች የሚከተሉትን መርሆ እና ይዞታ የተለያዩ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ይተቹታል። የዶቸ ቬለ ዘጋቢ Peter Stützle እንደዘገበዉ አሚስቲ ኢንተርናሽናል የወቅቱ የህብረቱን የፕሪዝደንት ስልጣን የያዘችዉ ጀርመን የህብረቱ አባል አገራት ስለ ስደተኞችና ተገን ጠያቂዎች ያለዉን ወቅታዊ መርህ እንድታቀርብ ጠይቋል።

የአዉሮፓዉ ህብረት ስለስደተኛ ማለት ስለተገን ጠያቂ ጉዳይ ለስብሰባ በጠረቤዛ ዙርያ ሲቀመጥ የመጀመርያ እና ግልጽ የሆነዉ መርሆዉ፣ በድንበር አካባቢ ያለዉን የጥበቃ ስራ ማጠናከር፣ የሚል ነዉ። በድንበር እና የመግቢያ ኬላዎችን በር ማጥበብ እና ጥበቃዉን ማጠናከር ሲባል ደግሞ፣ በአንደኛ ደረጃ፣ ድንበር ላይ ጠንካራ ፍተሻ እና ጥበቃ፣ በሁለተኛዉ ግልጽ የሆነዉ ደግሞ በአዉሮፓዉ ህብረት አባል አገራት ድንበር ላይ ጥገኝነት ወይም ተገን ለመጠየቅ የደረሱት ህዝቦች ላይ የጭካኔ እርምጃ መዉሰድ ይሆናል። አለም አቀፍ የሰብአዊ ጉዳይ ተሟጋች ድርጅት በእንጊሊዘኛ ምጽሃረቃሉ Amnesty International የአዉሮፓዉ ህብረት ስለ ስደተኞች ጉዳይ ያለዉን አንዳንድ ፖሊሲ ወይም ፖለቲካ ማለፍያ ቢያደርገዉም በሌላ በኩል በድንበር ላይ የሚፈጸመዉን ኢሰብአዊ ድርጌቶች ሲል ያወግዘዋል። በጀርመን የአረንጓዴዎች ፓርቲ መሪ ክላዉድያ ሮት የAmnesty International ን ሃሳብ ደጋፊ ናቸዉ

«ስለ ተገን ጠያቂዎች የሚነሳዉ ፖሊሲ ሁልግዜም ከጥበቃ እና ጸጥታ ፖለቲካ ጋር ይያያዛል። ነገር ግን እዚህ በቅድምያ መነሳት ያለበት ጥበቃ፣ ጸጥታ ሳይሆን ፣አዉሮፓ ለተገን ጠያቂዎች ከለላ ቦታ መሆን አለባት ወይም ቢያንስ የከለላ የመስጠት ፍላጎት ማሳየት አለባት የሚለዉ ነዉ። ከለላ የመስጠቱም ተግባር በቅድምያ በመዉሰድ የመጀመርያዉ መርሆዋ ማድረግ አለባት»
በሶሻልዲሞክራቱ የአዉሮፓ ምክር ቤት እንደራሴ Wolfgagng Kreissl- Dörfler የባልደረባቸዉ የወ/ሮ ክላዉድያ ሮትን አጠቃላይ የሆነ ትችት ሙሉ በሙሉ ባይቀበሉም የአዉሮፓዉ ህብረት በየአገራቱ ያሉ ስደተኞች እና ተገን ጠያቂዎች በስደተኛ ቢሮ ያስገቡት ማመልከቻ ዉድቅ መደረጉ ትክክል አይደለም ባይ ናቸዉ
«አንድም ግዜ በስርቆት ወይም በሌላ ወንጀል ሳይከሰሱ በእስር ቤት ዉስጥ ተይዘዉ ወራትና ከዝያም በላይ ታስረዉ፣ ከዝያም ይባስ ብሎ፣ ወደ የመጡበት በግዳጅ የሚመለሱት ስደተኞች ሁኔታ ነዉ። ልክ አንድ ትልቅ ወንጀል እንደሰሩ ነዉ የሚያዙት። እዚህ ላይ በእዉነቱ መግለጽ የምፈልገዉ በዚህ ሁኔታ መቀጠል የለበትም ነዉ»
የአለም አቀፍ የሰብአዊ ጉዳይ ተሟጋች ድርጅት ስደተኞች ወደ የመጡበት አገር መመለሳቸዉን ፈጽሞ አይነቅፍም። ስደተኛዉ ከለላ የጠየቀበት አገር መቆየት የሚችለዉ በፖለቲካ ጉዳይ ተፈላጊ ብቻ መሆኑ ከታወቀ እና የሰዉ ነፍስን ለማትረፍ የታሰበ ከሆነ ሲል ድጋፉን ይሰጣል። ነገር ግን ባለፉት ግዝያት ዉስጥ በሰላማዊዉ ዉቅያኖስ በኩል አዉሮፓ የሚገቡት ስደተኞች ጉዳይ የተነሳ የሰባዊ ጉዳይ ተሟጋች ቢሮን እጥርጣሪ ዉስጥ ጥሎታል። በጀርመን የአረንጓዴዉ ፓርቲ መሪ ክላዉዲያ ሮት የብዙሃን መገናኛን ነቅፈዋል።

«ሰዎች ወደ አዉሮፓዉ ህብረት አገራት በድንበር በኩል ሾልከዉ ሲገቡ ወይም ለማምለጥ ሲሞክሩ፣ የሚያሳየዉን የቴሌቭዝንም ሆነ የራድዮ ዘገባ ለህዝብ ሲሰራጭ፣ ስለ ስደተኞች በበጎ መታሰቡም ሆነ መወራቱ ይቀራል። በዚያም ሰበብ ህገወጥ ስለሆነ ሁኔታ ብቻ መነገር ይጀምራል። ያ ማለት ስደተኛ የሚለዉ ቃል ከለላ ጠያቂ የሚለዉ ትርጉም መሰጠቱ ይቀርና ህገወጥ ይሆናል»