1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአዉሮጳ የስደተኞች ፖሊሲ

ማክሰኞ፣ መስከረም 29 2005

የሶሪያ ጦርነትን ተከትሎ የተነሳው የስደተኞች ጎርፍ የአውሮፓ ደጃፍ ላይ ደርሷል። ለሶሪያውያን ብቻ ሳይሆን ለብዙ ሰዎች አውሮፓ የተስፋ ምድር ናት። አውሮፓ ግን ትግሉን የፋይናንስ ቀውስ ብቻ ሳይሆን አንድ የጋራ የተገን አሰጣጥ ለማውጣትም ጭምር ፤

https://p.dw.com/p/16N3e
ምስል picture-alliance/dpa

ጭምር  የመብት ተሟጋች ድርጅቶች አውሮፓ በሩዋን ለስደኞች ክፍት አላደረገችም ብለው ይከሳሉ።
እአአ እስከ 2012 ዓ.ም መጨረሻ  በአውሮፓ አንድ የጋራ የሆነ የተገን አሰጣጥ ሥርዓት መውጣት አለበት።  ቢሆንም የተገን ፈላጊዎች  የኑሮ ሁኔታና በተገን ሰጪ ሀገራት ውስጥ ያለው የአገልግሎት ጥራት ከአንዷ የአውሮፓ ህብረት ሀገር ወደ ሌላው ይለያያል። የተገን አሰጣጥ ሂደትም ከሀገር ወደ ሀገር ይለያያል። የዓለም አቀፉ የመብት ተሟጋች ድርጅት አምንስቲ ኢንተርናሽናል፣ የስደተኞች አያያዝ ባለሙያ፣ አኔሊሴ ባልዲቺኒ ግን ተስፋ አዘል ነገር ይታያቸዋል፣

«ይህ ረዥም ጊዜ የሚወስድ ጉዳይ ነው። በአውሮፓ ደረጃ የጋራ  የሆነ መለኪያና አሳሪ ህግጋት  አሉን። ነገር ግን በያንዳንዱ አባል ሀገር ውስጥ ለዚህ የሚያስፈልገውን  መዋቅር አቋቁሞ ወደ ሥራ እስኪለወጥ ደረስ ረዥም ጊዜ መውሰዱ አይቀሬ ነው።  

ትልቅ የስደተኞች ቁጥር በሚታይባት ግሪክ ውስጥ ፤ለተገን ጠያቂዎች የሚደረግ አያያዝ በጣም መጥፎ ነው።  ከግሪክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ እንደሚገልጸው እአአ በ2011 በየቀኑ ከ500 በላይ ስደተኞች በኤፍሮስ ግዛት የሚገኘውን የግሪክና የቱርክ የጋራ ድንበር  ቋርጠዋል። የአውሮፓ ህብረት የሀገር አስተዳደር ጉዳዮች ተጠሪ
ሲሲሊያ ማልምሽትሮም በስፍራው ያዩትን እንዲህ ያስታውሳሉ፣

«በግሪክ ኤፍሮስ አንድ ከአፍጋኒስታን የመጣ  ህጻን ወንድ ልጅ ትዝ ይለኛል፣ 14 ዓመቱ እንደሆንና እዚያም ከአፍጋንስታን ረዥምና አድካሚ ጉዞ አድርጎ እንደመጣ ነገረኝ። አንድ ትንሽዩ ክፍል ውስጥ ከሌሎች ስልሳና ሰባ  ከሚሆኑ ወጣቶች ጋር ተጣቦ ይኖራል። ሁለት መጸዳጃ ቤቶች ብቻ ነበራቸው። ከሁለቱ አንደኛው አገልግሎት አይሰጥም።  ለናቴ ስልክ መደወል እፈልጋለሁ ብሎ ትንሽ ዩሮ ለመነኝ ። ምክንያቱም እናቱ እጅግ እንደምትጨነቅለት ያውቅ ነበርና።»

በያዝነው የፈረንጆች ዓመትም ችግሩ  ሊባባስ ይችላል። እንደ የተባበሩት መንግስታት ግምት ከሆነ እስከ 2012 ዓ,ም መጨረሻ፣ 70,000 ሰዎች ሶሪያን ለቀው ይሸሻሉ። እስከ ዛሬ ድረስ 300,000 የሶሪያ ስደተኞች ወደ ጎረቤት ሀገራት በተለይም ወደ ሊባኖስ, ኢራቅ, ዮርዳስና ወደ ቱርክ   ሸሽተዋል።  ከነኚም ሀገራት የሶሪያ ስደተኞች በብዛት የሚሸሹት ወደ ግሪክ ነው። ሽሽትኑም የተያያዙት በሰሜን ግሪክ በጣም ቁጥጥር በሚደረግበት በኤቭሮስ ግዛት በኩል ሳይሆን፣ በምስራቅ በኩል በምትገኘው ኤጌይስ በተባለች ደሴት በኩል ነው። የአምንስቲ ኢንተርናሽናሏ አኔሊሴ ባልዳቺኒ የአውሮፓ ህብረት ሀገራት ስደተኞቹን ለመቀበል ፍቃደኝነታቸውን እንዲያሳዩ ይማጸናሉ፣

«ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት የቀውሱን  መቀስቀስ ተከትሎ    ስንት ሰደተኞች ናቸው በርግጥ ወደ እውሮፓ ህብረት የመጡት? 12,000 የሚሆኑ። ይህ ከሶሪያ ወደ አውሮፓ የገባው የስደተኞች ቁጥር ትልቅ አለመሆኑን ያሳያል። በርግጥ ቁጥሩ ጨምሮዋል። ሆኖም ግን ይህ ማንንም ሊያሳስብ አይገባም። ነገር ግን አብዛኞቹ መንግስታት እርምጃ መውሰድ አለባቸው።»

በርግጥ ግሪክ ካጋጠማት ግዙፍ የዕዳ ቀውስ አንጻር ስደተኞችን በልኩ መቀበል አለባት።  ይህች የስደተኞች መሸሻ የነበረች ሀገር እያደገ ያለውን የስደኞች ቁጥር ለስተናገድ የሚረዱ በቂ የተገን አሰጣጥና  የውጭ ዜጎች የሚተዳደሩበት ህግ የላትም። ግሪክ ላለፉት 20 ዓመታት የውጭ ዜጎች በብዛት የሚሄዱባት  ሀገር ሆና ቆይታለች። 11 ሚሊዮን ከሚሆኑ ነዋሪዎቿ ውስጥ 1ሚሊዮን የሚጠጉ የውጭ ዜጎች መሆናቸው የግሪክ ባለስልጣናት ይገምታሉ። የስደተኞች ጉዳይ ባለሙያዋ ባልዳቺኒ ሁኔታውን ሲገመግሙ፣

«የግሪክ ባለስልጣናት እንደ መጠለያ፣ ምግብና በቂ ልብስ የመሳሰሉ የስደተኞቹን መሰረታዊ ፍላጋቶች  እንኳ ማሟላት የተሳናቸው ይመስላሉ። በዚያ ደግሞ አብዛኞቹ ስደተኞች ልጆች ያሏቸው ቤተሰቦች ናቸው። ይህ የሚያሳየው ግሪክ አሁንም ችግሮቹን አለመፍታቷ ነው።

የጋራ የሆነ የአውሮፓ  ህብረት የተገን አሰጣጥ ሥርዓት ፖሊሲ ለማውጣት የተጀመረው ወደ መጠናቀቁ መድረሱ ምናልባት መፍትሔ ሊያስገኝ ይችላል ይላሉ የአውሮፓ ህብረት የሀገር ውስጥ አስተዳደር ተጠሪ ማልምሽትሮም። ማልምሽትሮም እንደገለጹት EUROPEAN ASYLUM SUPPORT OFFICE የተባለው አዲሱ የአውሮፓ ህብረት ድርጅት ስደተኞችን የሚቀበሉ ሀገራት  በተለይም በቀላሉ ለጉዳት ሊጋለጡ የሚችሉ ወላጅ የሌላቸው ልጆችን  ተገቢ አቀባበል እንዲደረግላቸው ይረዳል። 

«በርግጥ የተወሰኑ መሻሻሎች ታይተዋል። እንደ ሆላንድ ያሉት አንዳንድ ሀገራት ስደተኞችን የማስተናገድ ፕሮግራም አውጠተው  መልካም ለውጥ አስመዝግበዋል።  ለአውሮፓ ድንበሮች አስተዳድር ወኪል ድርጅትፍሮንቴክስ እና አዲስ ለተቋቋመው የአውሮፓ ተገን ፈላጊዎች የእርዳታ ጽሕፈት ቤት ወይ EUROPEAN ASYLUM SUPPORT OFFICE ምስጋና ይግባውና፣ ከለላ የሌላቸው ህጻናትን የሚቀበሉ  አባል ሀገራት ሰራተኞች ልዩ ስልጠና ያገኛሉ።

መንበሩን በማልታ ያደረገው  የአውሮፓ ተገን ፈላጊዎች የእርዳታ ጽሕፈት ቤት በእንግሊዘኛው ምህጻሩ EASO ፣ እዚያ ያሉ ባለስልጣናትን እንዲረዱ  የተገን ፈላጊዎጥ ረዳት  ቡድኖችን ወደ ግሪክ ልኮ ነበር። እንደ አኔሊሴ ባልዳቺኒ እምነት ከሆነ የእርዳታ ሰጪው ቡድን ስራ እንዲሁ ለማስመሰል ብቻ አይደለም ብለው ተስፋ አድርገዋል።

«እርግጠኛ ነው ይህ ወደ ትክክለኛ መንገድ የሚመራ አንድ እርምጃ ነው። ከአውሮፓ ህብረት ኮሚሽንም ቢሆን ለግሪክ  ከሌሎች ሀገሮች እርዳታን ለማድረስ ጥረት እየተደረገ ነው። EASO ባገራቱ መካከል ያለውን  መደጋገፍን ማጠንከር አለበት።  አሁን የተገን ፈላጊዎች ረዳት ቡድንን ወደ ግሪክ ልኳል። ለቡድኑ የሚደረግ የገንዘብ እገዛም እንዳለ, ነው።»

በግሪክ ለተገን ፍለጋ ማመልከቻ ማስገባቱ ረዥም ጊዜ ይወስዳል። የተገን ማመልከቻው ሂደት ብዙ ጊዜ ስለሚወስድ እና በጊዜያዊ መጠለያ ጣቢያዎች የሚቆዩበትን ጊዜ ስለሚያራዝም ስደተኞች ማመልከቻው ከማስገባት ወደ ኋላ እንደሚሉ የስደተኞቹ ጉዳይ ባለሙያ ማልሽትሮም ገልጸዋል።

ከሶስት ቀናት በፊት በሞልታ ዋና ከተማ ቫሌታ በተደረገው 10 የሜዲትራኒያ ባህር አከባቢ    ሀገራት መሪዎች ስብሰባ ላይ የጋራ ጸጥታንና የስደተኞችን ፖሊሲ በተመለከተ ምክክር ተካሂዷል። ሆኖም ግን ስብሰባው ላይ የተገኙ በምዕራብ ሜዲትራኒያን የሚገኙ ሀገራት አውሮጳውያቱ  ስፔን፣ ፈረንሳይ፣ ኢጣሊያን፣ ፖርቹጋል፣ ሞልታ ሲሆኑ ከሰሜን አፍሪካ ደግሞ አልጄሪያ፣ ሞሮኮ፣ ቱኒሲያና ሊቢያ እንዲሂም ሞሪታኒያ ብቻ ነበሩ። መሃል ሜዲትራኒያን የሚያዋስኑ ሀገራትም ቢሆኑ በርግጥ  የስደተኞች ችግር  ብዙ ነው። ታዲያ ተመሳሳይ ችግር እያጋጠማቸው ያሉ ሀገራት አንድ  ላይ ቁጭ ብለው መነጋገር የለባቸውም? ሆኖም አኔሊሴ ባልዳቺኒ እንዲህ አይነቱ ስብሰባ የአውሮፓን ሀገራት መለያየትን አያሳይም ባይ ናቸው፣

«እነኚህ፣ የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት ደረጃና፣  የህብረቱ ሀገራት ካልሆኑ ሀገራትም ጋር ጎን ለጎን የሚደረግ የጋራ ግንኙነት የሚመለከት የስብሰባ ሂደት ነው። ልዩና ያከባቢ ችግሮችን ለመፍታት ይረዳሉ። አሁን እየተካሄደ ያለው ጉዳይ ከምክክር አያልፍም። ስለዚህ የጋራ የሆነ የተገን ጠያቂዎች ስርዓትን ለመዝርጋት የምናደርገውን ጥረት አያደፋቅፈውም።  

ይህ የሁለቱም  የሜዲትራኒያን ባህር የሚያዋስኑ አስር የአፍሪካና አውሮፓ ሀገራት የተገኙበት ስብሰባ ላይ በባህር ላይ በስደትኞች ላይ የሚደርሰውን አደጋ ለመከላከል የሚሞክር  አንድ የሥራ ቡድን አቋቁመዋል። ከዚህ በፊት በርካታ የአፍሪቃ ስደተኞች ከአፍሪቃ ወደ አውሮፓ ለመግባት ሲሞክሩ ለስቃይ መዳረጋቸውና  በባህር ውስጥ ሰምጠው መቅረታቸው ይታወሳል። ይህን የባህር ላይ የስደተኞች ስቃይና ሞት  ጉዳዩ የሚመለከታቸው የአውሮፓ ሀገራት ችላ ብለው መቆየታቸው ብዙዎችን ቅር አሰኝቷል። 

Verbundene Hände eines Immigranten in Melilla
ምስል picture-alliance/ dpa/dpaweb
Illegale Immigranten provisorische Unterkunft Italien Flash-Galerie
ምስል picture-alliance/dpa
Überfahrt Mittelmeer Flüchtlinge retten sich nach dem Untergang ihres Bootes auf dem Mittelmeer in Thunfischnetze
ምስል picture-alliance/dpa
Symbolbild Flüchtlingstrom / Illegale Einwanderer Abschiebung vs Legalität Italien Gesetze Flash-Galerie
ምስል picture-alliance/dpa
ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ