1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአማራና ደቡብ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ

Merga Yonas Bulaዓርብ፣ ነሐሴ 13 2008

በአማራ ክልል በተለያዩ ቦታዎች የተቃዉሞ ሰልፉን ተከትሎ ብዙ ሰዎች መሞታቸዉና መታሠራቸዉ ይነገራል።

https://p.dw.com/p/1JluG
Karte Äthiopien Amhara, Tigray, Oromia Deutsch

[No title]

በያዝነዉ ሳምንት መጀመሪያ ቀናት በተለያዩ አካባቢዎች የነበሩት አድማዎች ጋብ ብለዉ አሁን ሁኔታዉ በከፊል የተረጋጉ እንደሚመስሉ ተሰምቷል። የጎንደር ነዋሪ የሆኑትና ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የጠየቁ የዓይን እማኝ አሁን በከፍል ብረጋጋም ከፍተኛ ዉጥረት ይታያል ይላሉ። ስለባህር ዳር ወቅታዊ ሁኔታም አንድ የከተማዋን ኗሪ ስንጠይቅ ተመሳሳይ eስ ሰቶናል።

በሁለቱም ከተሞች የታጠቁ የመንግሥት የደህንነት አካላት በከተማዋ መኖራቸዉ ይባስ ሕብረተሰቡ እንዲያኮርፍ አድርጎታል፣ ከዛም አልፎ ዉጥረት ፈጥረዋል ይላሉ ሁለቱም እማኞች። በጎንደርና በደብረማርቆስ ላይ የተመታዉ የሥራና የትራንስፖርት ማቆም አድማ ከኅብረተሰቡ ጋር በመወያየት እንደተፈታና አሁን እንቅስቃሴዉ ቀጥለዋል የሚሉት የአማራ ክልል የኮሙኒኬሼን ኃላፍ አቶ ንጉሡ ጥላሁን መንግስት «ህገወጥ ተግባራት» መቆጣጠርና ህግ የማስከበር ጌዴታ አለበት ይላሉ።
በአንፃሩ ተቃዉሞዉ በደቡብ ብሄር ብሄር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል ወደ ጋሙጎፋ ዞን አርባምንጭ ከተማ መዉረዱን፤ የፀጥታ አካሉም ሰዎች እያሰረ መሆኑን፣ በኮንሶም ሰላማዊ ሰልፍ ሊካሄድ ታቅዷል በሚል ዉጥረት ተፈጥሮ እንደነበረም ተመልክቷል። በኮንሶ ያለዉን እንዲያስረዱን የጠየቅናቸዉ የአካባቢዉ ነዋሪ አቶ ገመቹ ጌንፌ ባለፈዉ ቅዳሜ ባልታወቀ አካል ሰላማዊ ሰልፍ ይካሄዳል የሚል ወረቀት ተበትኖ እንደነበር ይገልጻሉ።

የፌስቡክ ገፃችን ላይ በዚህ ላይ አስተያየት ከሰጡን ዉስጥ በክልሉ ምንም አይነት ችግር እንደሌለ ገልጸዉ «እኛ ለውጥ እንጂ ጥፋት አንሻም» ያሉን አሉ። ሌሎች ደግሞ በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በዋናው ግቢ ውስጥ አንድ ተማሪ በደህንነት ኃይሎች ታፍኖ የተወሰደበት እንደማይታወቅምና ፣የደህንነት ኃይሎችም ግቢ ገብተዋል ተብሎ እንደሚነገር ጠቅሰዋል።

መርጋ ዮናስ

ሸዋዬ ለገሰ