1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የናይጀሪያ ክርስትያኖች ሥጋት

ሰኞ፣ የካቲት 26 2004

በሰሜን ናይጀሪያ በሚገኙት የካኖ፡ የጆስ እና የሱሌጃ ከተሞች ያሉ አብያተ ክርስትያን የአክራሪው ሙሥሊም ድርጅት ቦኮ ሀራም ተደጋጋሚ ጥቃት ሰለባ ሆኑ። ባለፉት ወራት በመቶዎች የሚቆጠሩ የክርስትና እምነት ተከታዮች በጥቃቱ ሕይወታቸውን አጥተዋል።

https://p.dw.com/p/14DnT
ምስል DW

በመሆኑም ብዙዎቹ ለደህነንታቸው ሠግተዋል። በአፍሪቃ በሕዝብ ብዛት ቀዳሚውን ቦታ የያዘችው የናይጀሪያ መንግሥት በቦኮ ሀራም አንጻር ሊወስደው የሚችለው ሥልት አለው የለውም በሚል ብዙዎች እያጠያየቁ ነው። እርግጥ፡ ሁሉም ስለ አሸባሪው ቡድን ይነጋገራል፤ ግን፡ ድርጅቱን በሚገባ የሚያውቅ አንድም የለም።

በካኖ ከተማ በብዛት ክርስትያኖች በሚኖሩበት የሳቦን ጋሪ ሠፈር ቤተክርስትያን ዘማሪዎች ነበሩ።
ዕለቱ እሁድ ነው። ለወትሮው ቤተክርስትያንዋ በምዕመናን ብዛት ትጨናነቃለች። የዚያን ዕለት ግን ብዙ ሰው አልነበረም። ምክንያቱም ባለፈው የሣምንት መጨረሻ በፕላቶ ፌዴራዊ ክፍለ ሀገር የጆስ ከተማ እንደታየው ቦኮ ሀራም አዘውትሮ በአብያተ ክርስትያን ደጃፍ ቦምብ ያፈነዳል። አማካ ኡዞ ስለጆሱ ጥቃት ስታስብ አሁንም ይዘገንናታል።

«በጣም ፈርተን ነበር ። ይህን ቀን በሕይወት እናሳልፋለን ብለን አልጠበቅንም ነበር። በእግዚአብሔር ርዳታ ልንተርፍ ችለናል። ፈጣሪ ራሱ ይጠብቀናል። አሁን ሁኔታው ከነበረው ተሻሻሎዋል። ደህና ነን። »
ሁለት መቶ ሰዎች በተገደሉባት የኤኮኖሚ መናኸሪያ በሆነችው የካኖ ከተማ አሁን ሁኔታዎች ወደነበሩበት ተመልሰዋል። እንዲያም ቢሆን ግን፡ በሺዎች የሚቆጠሩ፡ ብዙዎቹ ከደቡብ ምሥራቅ የኒዠር ደለል የሄዱ የክርስትና እምነት ተከታዮች ባለፉት ሣምንታት ከተማይቱን ለቀው ወጥተዋል። በዚህም የተነሳ አቡነ ፒተር ኤቤዴሮ የሚመሩት ሥርዓተ ፀሎትን ብዙም ሰው አልተከታተለውም። አቡኑ ከብዙ ምዕመናን ጋ ካካሄዱት ውይይት በኋላ ብዙዎች ለምን ካኖን እየለቀቁ እንደሚወጡ እንዲህ አስረድተዋል።

Christen in Nordnigeria Katholische Kirche Kano
ምስል picture-alliance/dpa


« ብዙ ሰዎች ካኖን እየለቀቁ የሚወጡት በተፈፀመው ጥቃት ሰበብ አይደለም። ጥቃቱ ቢደገም ጠንካራ ሊሆን ይችላል በሚል ሥጋት ነው። እኔ ግን ይህ ዓይነቱ ጥቃት እንደማይደገም ነው የሚሰማኝ። ከተደገመም እንዳለፈው ጠንካራ አይሆንም። »


አቡን ፒተር ኤቤዴሮ ግን ያደጉባትን የካኖ ከተማን ለቀው የመውጣት ዕቅድ የላቸውም።፤ ምንም እንኳን በወቅቱ ያንን ጥሩ የልጅነት ጊዜን የሚያስታውሳቸው ሁኔታ ባይኖርም። በአሁኑ ጊዜ በካኖ መንገዶች ብዙ ፖሊሶች ተሰማርተው ተየሚንቀሳቀሱ ተሽከርካሪዎችንና አነስተኛ ሞተር ሳይክሎችን ይፈትሻሉ። ግን፡፡መንግሥት አሁን በቦኮ ሀራም አንጻር በጀመረው ዘመቻ የሚካሄደው የፍተሻና ቁጥጥር ስራ ከልብ የመነጨ ባለመሆኑ የፈለገ ግለሰብ ፈንጂ ይዞ ሊያልፍ ይችላል። በሌላ በኩል ብዙዎች ከቦኮ ሀራም ጋ ውይት መጀመር ጠቃሚ ሊሆን ይችላል ብለው ያምናሉ። አቡነ ፒተር ኤቤዴሮ ግን ይህን አብዝተው ይጠራጠሩታል።

« መንግሥት ከቡድኑ ጋ መወያየት እንደሚፈልግ ይናገራል። ግን መንግሥት ምን ማድረግ እንደሚፈልግ በወቅቱ ማወቅ አልተቻለም፡ ምክንያቱም፡ ከቡድኑ ጋ መወያየት ወይስ ቡድኑን ተከታትሎ መደምሰስ ለሚለው ጥያቄ ግልጽ መልስ አላገኘም፤ ግራ የተጋባ ነው የሚመስለው፤ ቡድኑ በኅቡዕ የሚንቀሳቀስ በመሆኑ ከሱ ጋ ውይይት ማካሄዱ አዳጋች ነው የሚሆነው። »

Polizeiposten in Millionenstadt Kano, Nordnigeria
ምስል Katrin Gänsler


የሙሥሊሞቹ ምሁራን ምክር ቤት ዋና ፀሐፊ ሙዜሚል ሳኒ ሀጋ ም የአቡኑን አስተሳሰብ ይጋራሉ።
« ቦኮ ሀራም በመላ ሰሜን ናይጀርያ ሥር ሰዶዋል። አንድ የሚከተለው ርዕዮተ ዓለም ስላለውም ተፋጥኖ በመስፋፋት ላይ ይገኛል። በሄደበት ቦታ ሁሉ ዓላማ ያደረገው ድሆችን እና ሥራ አጦችን ሲሆን፡ እነዙሁ ግለሰቦች ለሚገኙበት አስቸጋሪ ሁኔታ ተጠያቂው የሀገሪቱ አመራር ነው፡ እና መንግሥትን አስወግደን አዲስ አመራር እንፍጠር እያሉ ይሰብካሉ። »


ይሁንና፡ ቦኮ ሀራም ምንም እንኳን ጥቃቱን ማጠናከሩ ባይቀርም፡ መንግሥት የማስወገድ አቅም አለው ብሎ የሚያምን ሰው የለም። ቦኮ ሀራም ግን አንድ የደረሰው ነገር መኖሩ አይካድም። ይኸውም፡ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ እየተጠናከረ የመጣውን የኃይል ርምጃ የተከታተሉት ናይጀሪያውያን ሀገሩ ናይጀሪያ ሰሜንና ደቡብ ናይጀሪያ ተብላ ትከፋፈል አትከፋፈል በሚለው ጥያቄ ላይ ውይይት እንዲጀምር ማድረጉ ነው። ሙሥሊሞቹ በሰሜን እና ክርስትያኖጩ ደግሞ በደቡቡ የየራሳቸውን ሀገር ሊያቋቁሙ ይችላሉ የሚለውን አስተሳሰብ ግን ማንም እንደጥሩ የመፍትሔ ሀሳብ አይመለከተውም። በዚያም በዚህ ግን በሰሜን ናይጀሪያ የሚኖሩ ብዙዎቹ የደቡብ ናይጀሪያ ተወላጆች በዚያ መኖር የሚቀጥሉበት ድርጊት ለሕልውናቸው አስተማማኝ እንዳልሆነ በመናገር አካባቢውን መልቀቁን መርጠዋል።

ካትሪን ጌንስለር
አርያም ተክሌ
መሥፍን መኮንን

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ