የቻርልስ ቴይለር ብይንና መልዕክቱ
ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 20 2004
ይታወቁ የነበሩ የተባባረው ዓብዮታዊ ግንባር ዓማፅያንን በመደገፋቸው፡ ባጠቃላይ በስብዕና አንጻር ፈፅመውታል በተባለው ወንጀል ጥፋተኛ ሆኖ አግኝቷቸዋል።
በአንድ የቀድሞ የሀገር መሪ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ የተላለፈውን ብይን ችሎቱን በፍርድ ቤት ሆነው የተከታተሉት የሲየራ ልዮን ዜጋ የሆኑት የ «ኦፕን ጃስቲስ ኢኒሺየቲቭ»የተባለው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ታጋይና ጠበቃው አልፋ ሴሴይ ፍትሕ ድል ማድረጉን ያሳየ ሲሉ አሞግሰዋል።
« የዛሬው ብይን ለሕግ የበላይነት ከፍተኛ ክብር ያሳየ እና ከባድ ወንጀል የፈጸሙ ግለሰቦችም፣ የፈለገውን ያህል ጠንካራ ቢሆኑም እና የትኛውንም ከፍተኛ ሥልጣን ቢይዙም፣ በሕግ እንደሚጠየቁ ያረጋገጠ ወሳኝ ርምጃ ነው። »
እንደ አንድ የሲየራ ልዮን ዜጋ ችሎቱን ተዓማኒ እና ትክክለኛ ነበር ያሉት ሴሴይ በስብዕና አንጻር ወንጀል እንዲፈፀም ትዕዛዝ የሰጠ አንድ የቀድሞ የሀገር መሪ በሕግ ፊት በኃላፊነት በመጠየቁ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል። ከአሁን በኋላ የሚጠበቀው ፡ ይላሉ ሴሴይ የቴይለር እና የአበሮቻቸው ወንጀል ሰላባ የሆኑት የሲየራ ልዮን ዜጎች ተገቢው ድጋፍ ሊደረግላቸውና የሚገባቸውን ፍትህ እንዲያገኙ ነው።
በቻርልስ ቴይለር ላይ የተላለፈው የጥፋተኝነት ብይን ለሌሎች መቀጣጫ እንደሚሆን ነው ናይጀሪያዊው ጂብሪል ኢብራሂም ከዴሞክራሲና ልማት ማዕከል ያምናሉ።
« በሥልጣን ላይ ያሉ መሪዎች፣ በሥልጣን ላይ ባሉበት ጊዜ ለሚወስዱት ርምጃ ሁሉ በኃላፊነት ሊጠየቁ እንደሚችሉ ጠቋሚ ነው። ቴይለርም በሥልጣን በነበሩበት ጊዜ የመንግሥትን ንብረት ለመግደል፡ ለማጥፋት፡ ለመስረቅ እና ሰዎችን አካል ተጎጂ ለማድረግ ተጠቅመውበታል። እና፣ በስብዕና አንጻር ለፈፀሙት ወንጀል፣ ተገቢውን ቅጣት ማግኘት አለባቸው። »
የቀድሞው የላይቤርያ ፕሬዚደንት ቻርልስ ቴይለር የተላለፈውን ብይን የተመድ እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች አሞገሱ። የጅምላ ነፍሰ ገዳዮችና ፈላጭ ቆራጮች ከሥልጣን ከወረዱ በኋላ በውጭ ሀገሮች በምቾት የሚኖሩበት ጊዜ ማክተሙን የተመ የሰብኣዒ መብት ተመልካች ምክር ቤት ኃላፊ ናቪ ፒላይ አስታወቁ።ይህ በዓለም አቀፍ የሕግና ፍትህ አሰራር ላይ ያላጥርጥር ታሪካዊ ሂደት መሆኑንም ፒላይ አክለው አስረድተዋል።
« የሲየራ ልዮንን የጦር ወንጀል የመረመረው ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ዛሬ በቻርልስ ቴይለር ላይ ያስተላለፈው ብይን በጣም ወሳኝ ነው፤ ምክንያቱም በወንጀል ላይ የተሰጠ ዓለም አቀፍ ፍትሃዊ ብይን ነው። ዓለም አቀፉ የወንጀል መርማሪ ሕግ ምን ያህል መጠናከሩን፡ ማለትም፡ ከፍተኛ ባለሥልጣናትን ሳይቀር በኃላፊነት ከመጠየቅ ወደኋላ እንደማይል አሳይቶዋል። አንድ ዓለም አቀፍ የጦር ወንጀል ተመልካች ፍርድ ቤት አንድ የቀድሞ የሀገር ርዕሰ ብሔርን ጥፋተኛ ብሎ ብይን ሲያሳልፍ ይህ የመጀመሪያ ጊዜ መሆኑን የቻርልስ ቴይለር ጉዳይ በግልጽ አሳይቶዋል። በጣም በከፍተኛ ሥልጣን ላይ ያሉና የነበሩ ሁሉ በዓለም አቀፉ ሕግ ፊት ተጠያቂ ናቸው። »
ፒለይ በጦር እና በስብዕና አንጻር ወንጀል ፈጽመዋል በሚል በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ክስ ተመስርቶባቸው በእስር የሚገኙ ወይም የእስር ማዘዣ የተላለፈባቸውን አንዳንድ መሪዎችን በመጥቀስ እንዳመለከቱት፡ ብይኑ በስብዕና አንጻር ወንጀል የሚፈፅም ግለሰብ ከሕግ በላይ አለመሆኑን ግልጹን መልዕክት አስተላልፎዋል።
« ከቻርልስ ቴይለር ጎን ሌሎች የቀድሞ የሀገር መሪዎችም ክስ ተመስርቶባቸዋል። የኮትዲቯር ፕሬዚደንት ሎውሮ ባግቦ፡ ሟቹ የቀድሞ የሊቢያ መሪ ሞአመር ጋዳፊ እና በዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ችሎታቸው በመካሄድ ላይ የሚገኙት የቀድሞ የሰርቢያ ፕሬዚደንት ራዶቫን ካራጂች ይጠቀሳሉ። በሱዳን ፕሬዚደንት ኦማር ሀሰን ኧል በሺርም ላይ ከጥቂት ጊዜ በፊት የእስር ማዘዣ ተላልፎዋል። እስከዛሬ ድረስ ፍትሕ እንዲከበር ሲጠይቁና ይህ ጥያቄአቸው መልስ ተነፍጎባቸው ለቆዩት የጦር ወንጀል ሰለባዎች ሁሉ ፍትሕ መገኘቱን ያመላከተ ርምጃ ነው። ይህ ሁሉ፣ ከባድ ወንጀል ከመፈፀም መቆጠብ አስፈላጊ መሆኑን የሚገልጽ በጣም ጠንካራ መልዕክት አስተላልፏል። »
የሲየራ ልዮን ሕዝብ ብይኑን በደስታ ቢቀበለውም፡ ብዙዎች የቴይለር ደጋፊዎች በሚገኙባት በጎረቤት ላይቤርያ ብዙዎች ቴይለርን ጥፋተኛ አድርገው አይመለከቱም። እንዲያውም በነጻ እንዲለቀቁ ነው የሚጠይቁት።
የቴይለር ቤተሰብ የቅርብ የሆኑት ሳንዶህ ጆንሰን የዴን ኻጉን ብይን የአሸናፊዎች እና የምዕራቡ ሴራ አድርገው ነው ያዩት።
« አሜሪካውያንና ብሪታንያውያን አሸንፈዋል። ፀጉረወርቃማዎቹና ሰማያዊ ዓናማዎቹ በአፍሪቃውያን አንጻር ድል አድርገዋል። ይሁንና፡ ቴይለር አንድም እኩይ ነገር አልሰሩም። ቶኒ ብሌር እና ጆርጅ ዳብልዩ ቡሽ ለራሳቸው ክሽፈት ሰበብ ነው ያደረጉዋቸው። የይግባኝ ማመልከቻ እናስገባለን። ከቴይለር ጎን ቆመናል። ጥሩ ሰው ናቸው እና ምዕራቡ ዓለም፣ በዚህ ፖለቲካን መሰረት ላደረገው ብይን በኃላፊነት ይጠየቅበታል። »
ሌላው ምሬት የተሰማቸው ጋዜጠኛው ቶም ካማራ በሲየራ ልዮን የጦር ወንጀል ሰለባ የሆኑትን ግለሰቦችን ችግር የሚረዱ ብዙ ላይቤሪያውያን አሉ።
« እንደሚመስለኝ ዛሬ ለላይቤርያ ብቻ ሳይሆን ለመላ ምዕራብ አፍሪቃ ፍትሕ ወርዶዋል። ይህ አዲስ ጅምር ነው። ብይኑ ማንም ከሕግ በላይ አለመሆኑንና ወንጀል የፈጸመ ሳይቀጣ እንደማያልፍ አሳይቶዋል። እርግጥ የሰለባዎቹ ቁስል ገና አልዳነም። ወጣቱ ትምህርት፡ ስራ የለውም። በጦርነቱ ብዙ ዓመታት ጠፍተዋል። ጦርነቱ አሁን አብቅቷል። »
እርግጥ፡ ሲየራ ልዮን ውስጥ የኤኮኖሚው ችግር ጎልቶ ይታያል። በ ተባበረው ዓብዮታዊ ግንባር ዓማፅያን የጦር ወንጀል የአካል ተጎጂዎች ለሆኑት የስራ ዕድል የለም። ብዙዎቹ ከልመና ወይም ከቤተሰባቸው ርዳታ ለማግኘት በተስፋ ከመጠባበቅ በስተቀር ሌላ አማራጭ አላገኙም። ለተቀረው የሀገሪቱ ሕዝብም ኑሮ ቀላል አይደለም። ጦርነቱ ካበቃ ከብዙ ዓመታት በኋላም በሲየራ ልዮን እና በላይቤርያ ትምህርት ቤት የሚሄዱትና ሕፃናት ቁጥር እጅግ ንዑስ ሲሆን፡ በወሊድ ጊዜ ሕይወታቸውን የሚያጡ እናቶች ቁጥር በብዙ የዓለም ሀገሮች ከሚታየው በጣም ብዙ ነው።
የሰሞኑ ብይን ለብዙ ሰለባዎች እፎይ የሚያሰኝ ቢሆንም፡ ፍትሕ ገና አልሰፈነም። ይህ የሚሆነው በሲየራ ልዮንና በላይቤርያ ጦርነቱ ትቶት ያለፈው ቁስል ሲድን ብቻ ይሆናል።
አርያም ተክሌ
መሥፍን መኮንን