1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የተመድ ልዩ ልዑክ ከሱዳን መባበር

ሰኞ፣ ጥቅምት 13 1999

የሱዳን መንግስት የተባበሩት መንግስታትን ልዩ ልዑክ ከአገር እንዲወጡ ማስታወቁ ከመንግስታቱ ድርጅትም ሆነ ከአዉሮፓ ህብረት ወቀሳ አስከትሎበታል።

https://p.dw.com/p/E0hs
የተመድ ልዩ ልዑክ ያን ፕሮንክ
የተመድ ልዩ ልዑክ ያን ፕሮንክምስል AP

የመንግስታቱ ከፍተኛ ልዩ ልዑክ ያን ፕሮክ ትናንት ከሱዳን የዉጪ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ካርቲ ጋርም ተነጋግረዋል። በወቅቱም ካርቲ ለፕሮክ የሱዳን ተልዕኮ ማብቃቱን የሚገልፅ ይድረስ ለዋና ፀሃፊ ኮፊ አናን የሚለዉን ደብዳቤ ሰጥተዋቸዋል።

ፕሮንክ በሰጡት መግለጫ ባለስልጣናት በሶስት ቀናት ዉስጥ ባስቸኳይ እንዲወጡ እንደነገሯቸዉና እሳቸዉ ዛሬ ከአናን ጋር ለመመካከር ወደኒዉ ዮርክ ለመሄድ መዘጋጀታቸዉን ነዉ የተናገሩት።

የአዉሮፓ ህብረትም በበኩሉ ሱዳን የመንግስታቱን ድርጅት ልዩ ልዑክ ማስወጣቷ ስጋት እንዳሳደረበት ገልጿል።

የወደፊት የሱዳንና የመንግስታቱ ድርጅት ግንኙነት ምን ይመስላል ይላሉ ተብሎ ከዶቼ ቬለ ለቀረበላቸዉ ጥያቄ አልታፋጂ ይህን ነዉ ያሉት

«ግንኙነቱ ከአሁኑ አስቸጋሪ እንዲሆነ እናስባለን። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ራሱ በዳርፉር ሊሰራቸዉ የሚገባዉ በርካታ ጉዳዮች አሉ። በሰብዓዊ ረገድ በተለይ ብዙ ይሰራሉ፤ የሱዳን ባለስልጣናት በዳርፉር አካባቢ ያለዉን ቀዉስ በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የመንግስታቱ ድርጅት በአካባቢዉ በጣም ገንቢና አስፈላጊ ሚና እንደሚጫወት መገንዘብ አለባቸዉ። ከዳርፉር ዉጪ በደቡብ ሱዳን የሚገኘዉ የመንግስታቱ ድርጅት ኃይል አካባቢዉን ለማረጋጋትና መልሶ ለመገንባት እያደረገ ያለዉን ጠቃሚ ተግባር ያዉቃሉ። ስለዚህ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ልዩ ተወካይ በስፍራዉ መኖራቸዉም ጠቃሚ ነገር መሆኑን ይረዳሉ ብለን ተስፋ እናደርጋለን።»

የሱዳን መንግስት እዚህ ዉሳኔ ላይ የደረሰዉ ባለፈዉ ማክሰኞ ሲሆን የሰጠዉ ምክንያት የመንግስታቱ ድርጅት ልዩ ልዑክ የስልጣን ገደባቸዉን ያለፈ ተግባር ፈፅመዋል ይላል።

ይኸዉም ከዳርፉር ጋር የተያያዘ አስተያየት በግል ድረ ገፃቸዉ በመፃፋቸዉ መሆኑ ተጠቅሷል።

አደበት ርቱዕ የሚባሉት የ66 ዓመቱ ፕሮንክ የሱዳን መንግስት የዳርፉርን ቀዉስ የሚያስታምምበትን መንገድ በመተቸታቸዉ የፕሬዝደንት ኦማር አልበሺርን አገዛዝ ክፉኛ ነዉ ያበሳጩት።

ይኸዉ የካርቱም መንግስት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰላም አስከባሪ ኃይል ወደዳርፉር መግባት የለበትም ማለቱንም አንስተዋል።

ከዚህም ሌላ የሱዳን መንግስትን የጦር ኃይል በዳርፉር የሚያሳየዉን በተመለከተ ስነምግባር የጎደለዉና ከጃንጃዊድ ሚሊሺያዎች ጋር ግንኙነት ያለዉ ሲሉም ተችተዋል።

በዳርፉር በአዉሮፓዉያኑ 2003እና 2004ዓ.ም በነበረዉ ግጭት ጃንጃዊድ ሚሊያሺያዎቹ ሆን ብለዉ እንዲያጠቁ በስልት ተለቀዋል ወይም በሱዳን ጦር ተፈቅዶላቸዋል በማለት በይፋ ፅፈዋል።

የጦር ኃይሉ በበኩሉ እንዲህ ያለዉ መረጃ በታጠቁት ኃይሎች መካከል ስነልቦናዊ ሙግት በመፍጠር የጦር ኃይሉ የአገሪቱን ደህንነት ለመጠበቅ የማይበቃ አድርጎ አቅርቧል ሲል ፕሮንክን ከሷል።

የመንግስታቱ ድርጅት የፀጥታዉ ምክር ቤት ነሐሴ 25 1998ዓ.ም በዳርፉር ሰላምና ደህንነትን ማስፈን አልቻለም የተባለዉን የአፍሪካ ህብረት ሰላም አስከባሪ ኃይል የሚተካ 20,000 ዓለም ዓቀፍ ኃይል ወደዳርፉር መላክ አለበት ብሎ ወስኗል።

የአልበሺር መንግስት ደግሞ በተደጋጋሚ ዩናይትድ ስቴትስ ሱዳንን ለመዉረርና ጥሬ ሃብቷን ለመበዝበዝ ያቀነባበረችዉ ዘዴ ነዉ በሚል የተባለዉን ሰላም አስከባሪ ኃይል እንደማይቀበል አስታዉቋል።

የመንግስታቱ ድርጅት በሺዎች የሚቆጠሩ ሰላም አስከባሪዎች በደቡብ ሱዳን እንዳሉት የሚናገሩት የድርጅቱ ባለስልጣናት የፕሮንክ ከሱዳን መባበር አገሪቱ ሊኖራት ነዉ ተብሎ የታሰበዉን የህብረት መንግስት ነገር ጥያቄ ላይ እንደጣለዉ ይናገራሉ።