1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የቦምብ ጥቃቶች በሶማሊያ

ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 24 2006

ሶማሊያ መዲና መቅዲሾ በሚገኝ አንድ ሆቴል አጠገብ ትናንት ምሽት በተከታታይ በደረሱ የቦምብ ፍንዳታዎች የሞቱት ሰዎች ቁጥር ወደ 13 ከፍ ማለቱ ተዘግቧል ። ከሟቾቹ መካከል ፖሊሶችም ይገኙበታል ። የሶማሊያው ደፈጣ ተዋጊ ቡድን አሸባብ ለጥቃቱ ሃላፊነቱን ወስዷል ።

https://p.dw.com/p/1AkYr
Somalia tödlicher Autobombenanschlag auf Hotel in Mogadischu
ምስል Reuters

ሁለቱ ፍንዳታዎች ትናንት ምሽት በተከታታይ የደረሱት መቅዲሾ ዓለም ዓቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ አቅራቢያ በሚገኘው ጀዚሪያ ከተባለው ትልቅ ሆቴል አጠገብ ነበር ። የዶቬለ የመቅዲሾ ዘጋቢ ሞሐመድ ኦማር ሁሴን እንደሚለው የመጀመሪያው ና ሁለተኛው የቦምብ ፍንዳታዎች የደረሱት በአንድ ሰዓት ልዩነት ውስጥ ነው ።

« የመጀመሪያው ጥቃት ከምሽቱ በሃገሩ ሰዓት አቆጣጠር ከምሽቱ አንድ ሰዓት ተኩል ነው የደረሰው ። በጥቃቱ የ6 ሰዎች ህይወት ጠፍቷል ። 2ተኛው ደግሞ ከ አንድ ሰዓት በኋላ የፈነዳው ። በዚህ አደጋም 6 ሰዎች ተገድለዋል ። ከመካከላቸው 2 የፖሊስ መኮንኖች ይገኙበታል ። »

የዶቼቬለው ዘጋቢ እንደሚለው ዛሬ ከሆስፒታል ባገገኘው መረጃ መሠረት በፍንዳታው የሞቱት ሰዎች ቁጥር 13 ሲደርስ የቆሰሉት ደግሞ 60 ነው ። አደጋው በደረሰበት ወቅትም በሆቴሉ ውስጥ የሶማሊያ ምክር ቤት አባላት ነበሩ ። አነርሱ ግን ከአደጋው ተርፈዋል ። ጀዚራ የተባለው ፍንዳታው የደረሰበት ቦታ አጠገብ የሚገኘው ሆቴል ሞሐመድ ኦማር ሁሴን እንደሚለው የመንግሥት ሹማምንት ና የዲያስፖራዎች መነኻሪያ ነው ።

Somalia tödlicher Autobombenanschlag auf Hotel in Mogadischu
ምስል Reuters

« ጀዚራ በቅርቡ የተገነባ ባለ 5 ኮከብ ሆቴል ነው ። የሆቴሌ እንግዶች በሙሉ ማለት ይቻላል በውጭ ሃገራት የሚኖሩ ሶማሌዎች ና የመንግስት ባለሥልጣናት ናቸው ።»

በዚሁ ስፍራ ከጥቂት ወራት በፊት የሶማሊያ ፕሬዝዳንት እዚያ ያረፉ የኬንያ መንግሥት ልዑካንን ሲያነጋግሩ በአቅራቢያ ተመሳሳይ ጥቃት ደርሶ ነበር ። ከትናንት ምሽቱ የመጀመሪያ ፍንዳታ በኋላ ታጣቂዎች ተኩስ ከፍተው ነበር ሆኖም በጠባቂዎች የአፀፋ ተኩስ ከአካባቢው መፈግፈጋቸውን ነው ሞሀመድ የገለፀው ።

«የሆቴሉን ሥራ አስኪያጅ ሚር ሃሰንን አነጋግሬ ነበር ። እርሳቸው እንዳሉት የመጀመሪያው የአጥፍቶ ጠፊ ጥቃት ሲደርስ በአካባቢው የአሸባብ ታጣቂዎች ነበሩ ። ከፍንዳታው በኋላም ሆቴሉ ውስጥ ለመግባት ፈልገው ነበር ። ሆኖም የሆቴሉ ጠባቂዎች ና በአካባቢው የነበሩት ኃይሎች ተኩስ ከፍተውባቸው እንዲሸሹ አድርገዋል ። ወደ ሆቴሉ ዘልቀው ለመግባት አልቻሉም ። »

Somalia Mogadischu Jazira Hotel Anschlag
ምስል Reuters

አሸባብ ለቦምብ ጥቃቶቹ ሃላፊነቱን ወስዷል ። በትዊተር ባሰራጨው መልዕክቱ መሰል ጥቃቶችን ማድረሱን እንደሚቀጥልም አስታውቋል። መሐመድ እንደሚለው አሸባብ ቢዳከምም ቦምብ ማፈንዳት ግን አያቅተውም ።

« በርግጥ አሸባቦች እንደ በፊቱ ጠንካራ አይደሉም ። ከዚህ ቀደም ይቆጣጠሯቸው ከነበሩት ከዋና ከተማይቱ ከመቅዲሾም ሆነ ከሌሎች የሃገሪቱ አካባቢዎች ሁሉ እየተባረሩ ነው ። ሆኖም አሁን የትግል ስልታቸው ወደ ሽምቅ ውጊያ ተቀይሯል ። እውነቱን ለመናገር አሸባቦች አሁንም አሉ ። በየትኛውም የሶማሊያ አካባቢ በማንኛውም ጊዜ ጥቃት ማድረስ ይችላሉ ። »

ኂሩት መለሰ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ