የቦምብ ጥቃቶች በሶማሊያ
ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 24 2006ሁለቱ ፍንዳታዎች ትናንት ምሽት በተከታታይ የደረሱት መቅዲሾ ዓለም ዓቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ አቅራቢያ በሚገኘው ጀዚሪያ ከተባለው ትልቅ ሆቴል አጠገብ ነበር ። የዶቬለ የመቅዲሾ ዘጋቢ ሞሐመድ ኦማር ሁሴን እንደሚለው የመጀመሪያው ና ሁለተኛው የቦምብ ፍንዳታዎች የደረሱት በአንድ ሰዓት ልዩነት ውስጥ ነው ።
« የመጀመሪያው ጥቃት ከምሽቱ በሃገሩ ሰዓት አቆጣጠር ከምሽቱ አንድ ሰዓት ተኩል ነው የደረሰው ። በጥቃቱ የ6 ሰዎች ህይወት ጠፍቷል ። 2ተኛው ደግሞ ከ አንድ ሰዓት በኋላ የፈነዳው ። በዚህ አደጋም 6 ሰዎች ተገድለዋል ። ከመካከላቸው 2 የፖሊስ መኮንኖች ይገኙበታል ። »
የዶቼቬለው ዘጋቢ እንደሚለው ዛሬ ከሆስፒታል ባገገኘው መረጃ መሠረት በፍንዳታው የሞቱት ሰዎች ቁጥር 13 ሲደርስ የቆሰሉት ደግሞ 60 ነው ። አደጋው በደረሰበት ወቅትም በሆቴሉ ውስጥ የሶማሊያ ምክር ቤት አባላት ነበሩ ። አነርሱ ግን ከአደጋው ተርፈዋል ። ጀዚራ የተባለው ፍንዳታው የደረሰበት ቦታ አጠገብ የሚገኘው ሆቴል ሞሐመድ ኦማር ሁሴን እንደሚለው የመንግሥት ሹማምንት ና የዲያስፖራዎች መነኻሪያ ነው ።
« ጀዚራ በቅርቡ የተገነባ ባለ 5 ኮከብ ሆቴል ነው ። የሆቴሌ እንግዶች በሙሉ ማለት ይቻላል በውጭ ሃገራት የሚኖሩ ሶማሌዎች ና የመንግስት ባለሥልጣናት ናቸው ።»
በዚሁ ስፍራ ከጥቂት ወራት በፊት የሶማሊያ ፕሬዝዳንት እዚያ ያረፉ የኬንያ መንግሥት ልዑካንን ሲያነጋግሩ በአቅራቢያ ተመሳሳይ ጥቃት ደርሶ ነበር ። ከትናንት ምሽቱ የመጀመሪያ ፍንዳታ በኋላ ታጣቂዎች ተኩስ ከፍተው ነበር ሆኖም በጠባቂዎች የአፀፋ ተኩስ ከአካባቢው መፈግፈጋቸውን ነው ሞሀመድ የገለፀው ።
«የሆቴሉን ሥራ አስኪያጅ ሚር ሃሰንን አነጋግሬ ነበር ። እርሳቸው እንዳሉት የመጀመሪያው የአጥፍቶ ጠፊ ጥቃት ሲደርስ በአካባቢው የአሸባብ ታጣቂዎች ነበሩ ። ከፍንዳታው በኋላም ሆቴሉ ውስጥ ለመግባት ፈልገው ነበር ። ሆኖም የሆቴሉ ጠባቂዎች ና በአካባቢው የነበሩት ኃይሎች ተኩስ ከፍተውባቸው እንዲሸሹ አድርገዋል ። ወደ ሆቴሉ ዘልቀው ለመግባት አልቻሉም ። »
አሸባብ ለቦምብ ጥቃቶቹ ሃላፊነቱን ወስዷል ። በትዊተር ባሰራጨው መልዕክቱ መሰል ጥቃቶችን ማድረሱን እንደሚቀጥልም አስታውቋል። መሐመድ እንደሚለው አሸባብ ቢዳከምም ቦምብ ማፈንዳት ግን አያቅተውም ።
« በርግጥ አሸባቦች እንደ በፊቱ ጠንካራ አይደሉም ። ከዚህ ቀደም ይቆጣጠሯቸው ከነበሩት ከዋና ከተማይቱ ከመቅዲሾም ሆነ ከሌሎች የሃገሪቱ አካባቢዎች ሁሉ እየተባረሩ ነው ። ሆኖም አሁን የትግል ስልታቸው ወደ ሽምቅ ውጊያ ተቀይሯል ። እውነቱን ለመናገር አሸባቦች አሁንም አሉ ። በየትኛውም የሶማሊያ አካባቢ በማንኛውም ጊዜ ጥቃት ማድረስ ይችላሉ ። »
ኂሩት መለሰ
ተክሌ የኋላ