1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የባለሥልጣናት ግድያ፤ የሥራ ዕድል፤ የራስ ገዝ አስተዳደር

እሑድ፣ ሰኔ 30 2011

«በመላው ሃገሪቱ የአማራ የፖለቲካ ውክልና ሊኖር ይገባል፤ አንቀጽ 39 ካልተነሳ የባቢሎን ግንብ ካልፈረሰ ሁሉም ፍቅር አንድነት እየተባለ የሚስበክው ውሽት ነው። የብሔር ፓለቲካን ቆፍራችሁ ቅበሩት፤ 2012 ዓም የበጀት ዓመት መጨረሻ 3 ሚሊዮን የሥራ እድል ለመፍጠር ታቅዶአል።

https://p.dw.com/p/3LfLg
Äthiopien Empfang einer Delegation in Arbaminch
ምስል Fitsum Arega

የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ቅኝት

የኢትዮጵያዉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐብይ አህመድ የመንግሥታቸዉን ዓመታዊ የዕቅድ አፈጻጸምን በተመለከተ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያቀረቡት ዘገባና ከምክር ቤቱ አባላት ለቀረቡ ጥያቄዎች የተሰጠዉ መልስና ማብራርያ የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴ ተጠቃሚዎችን ትኩረት ከሳቡ ጉዳዮች ቀዳሚዉ ነዉ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሰጡት ገለፃና ማብራርያ በርከት ያሉ አስተያየት፤ ክርክርና ትችት ያስከተሉት ሦስት ናቸዉ። የኢትዮጵያ መንግሥት መፈንቅለ መንግሥት ያለዉ የሰኔ 15 ቱ የባለሥልጣናት ግድያ ፤ የሐገሪቱ ምጣኔ ሐብትና፤ የራስ አስተዳደርን የሚጠይቁ በተለይ ሲዳማን የመሳሰሉ ዞኖች ወይም ወረዳዎች የሚያነሱት ጥያቄ ነዉ።

Ruanda Kigali - Äthiopiens Premierminister Abiy Ahmed bei Rede zum 25. Gedenktag des Völkermord 1994
ምስል Getty Images/AFP/Y. Chiba

  
የሰኔ 15 ቱ የባለሥልጣናት ግድያ
የመጀመርያዉ ማለትም ግድያዉን በተመለከተ፤ ጃፋር ካዛሊ የተባሉ የፌስቡክ ተከታታይ «ወንጀለኞችን በቁጥጥር ስር ማዋል መፍትሄ እያመጣ አይደለም! ያለፈው ስርዓት የኢትዮጵያን ሕዝብ ቀጥ አድርጎ ለብዙ ዓመታት የያዘው ለዲሞክራሲ የታገለውንም ወንጀለኛውንም የማያዳግም እርምጃ ማለትም የሞት እና እድሜ ልክ እስራትን በአጭር ጊዜ በይኖ ብዙሃኑን ያስተምርበት ስለነበር ነው። የለውጡ መሪዎች ለሀገሪቷ አንድነት ከተጨነቁ ቢያንስ የወንጀለኛን መቅጫ፤ ካለፈው ሰርአት መማር አለባቸው። የሕጉ መላላት ሃገሪቷን ዋጋ እያስከፈላት ነው።» አብዩ ዘለቀ በበኩላቸዉ «አላማው አማራን ማዳከም ነው መሪዎችን ገደለ ለመከፋፈል እየጣረ ነው። አብንንም ለማፍረስ እየጣሩ ነው» መንግሥቱ መለሰ አንድ ሁለት ብለዉ ያስቀመጥዋቸዉ አስተያየቶች «አማራ ያነሳቸው አንኳር ጥያቄዎች» ሲል ይጀምራል 
« 1, የአማራ ማንነት መከበር እና በማንነቱ እንዲኖር መደረግ አለበት!
2, ፍትሃዊ አሰራር እና ፍትህ መስፈን አለበት።
3, አማራን የበደሉ አካላት ዳግም እንዳይበድሉ መደረግ አለበት። የተበደሉ ለምሳሌ ጥፍራቸው የተነቀሉ፣ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ፤ የአካባቢውን ሕዝብ በልማት ተሳታፊ በማረግ ወዘተ መፍትሄ መስጠት። 
4, በመላው ሃገሪቱ የአማራ የፖለቲካ ውክልና ሊኖር ይገባል። ለምሰሌ በኦሮሚያ በቤንሻንጉ በሐረር 

Äthiopien Trauerfeier für General Seare Mekonnen
ምስል picture-alliance/AP Photo/M. Ayene

5,አማራን እንደ ጠላት የሚያሳየውን የጥላቻ ሐውልት ንግግር ወዘተ ለምሳሌ አኖሌ ሐውልትን ማፍረስ እና ህዝቡን ማስታረቅ። እነዚህ እና መሰል የአማራ ጥያቄዎች ከተመለሱ አማራ ይረጋጋል። ያለበለዝያ ግማሽ የሃገሪቱን ሕዝብ ሳታረጋጋ ሀገር ለማረጋጋት መሮጥ ከንቱ ድካም ነው።» ሌላዉ የፊስቡክ ተከታታይ እስካሁን ይላሉ ሞሃሙድ ሰይድ ሙሳ ይባላሉ፤ እስካሁን ድረስ እየወጡ ያሉት መረጃዋዎቸ አብዛኛዎቹ የሚያደሉት አሳምነው ፅጌ ያስገዳዩን ድርሻ እንደሚወስድ ነው የሚያረጋግጡት። ለምን ይህን አደገኛ የሆነ ድርጊት ለመፈፀም እንደወሰነ፤ ምን ውጤት ጠብቆ እንዳቀናበረው፤ ከጀርባሁነው ጉዳዩን ሲያግዙ የነበሩ ባለሀብቶችም ሆኑ ባለስልጣን ፖለቲከኛም ሆነ አክቲቪስት እነማን እንደነበሩ ገለልተኛ የሆነ አጣሪ ቡድን ተመድቦ ውጤቱን ለህዝብ ይፋ እንዲደርግ እንጠይቃለን።» ይላሉ። ሰናይት እሸቴ በበኩላቸዉ ይሄ መፈንቀለ መንግስት ነው ማለት አይቻልም እንዴት ሆኖ ባህርዳር ክልል ነች እስከ ስንት ግዜ ሊመራው ነው ፈልቅሎ። ነገ መቶ በሀይል እንደሚነጠቅ ያውቀዋል እኮ። » ጽጌሬዳ መለሰ ቀደም ካሉት አስተያየት ሰጭ ብዙም አይለዩም «እንደ ሰው ቆም ብለን ካሰብን ብዙ ነገሩ የመንግስት ሴራ መሆኑ ያስታውቃል። ምክንያቱም እንዴት ያለወትሮአቸው መረጃ ቶሎ ቶሎ መስጠት ጀመሩ? ይሄ ቀድመው ያዘጋጁት ስለሆነ ነው። የሚገርመው እኮ ማን እንደገደላቸው እንኳን ሳይሰሙ ነው በእሳቸው ያሳበቡት። ከዚህ ቀደም ሌላ ግዜ እናጣራለን ነበር የሚሉት። እንደውም ብዙ ጋዜጠኛች ሲናገሩ ፕሮግራሙ ቀድሞ ነው የደረሰን ነው ያሉት። ለወንጀሉ ቅርብ ነበሩ። አሁን ደግሞ የአማራ ህዝብን እያፈናቀሉ ትጥቅ እያስፈቱ ነው። ታዲያ ይሄ አያጠራጥርም? በጥያቄ ምልክት አስተያየታቸዉን ይጨርሳሉ። ኢማን ነጋሽ በበኩላቸዉ እናንተ ግን ምን ሆናችሁ ነው? የማንም የሞነጫጭረውን ሚዛን ደፍቶላችሁ ነው የምታነፃፅሩት? ከሟቾቹ አጠገብ የነበሩትና ትራጀዲውን በዓይናቸው ያዩት የሚነግሩን እናምንም ብለን፤ ከሰሐራ በረሀና ከሜድትራንያን ባህር ተርፈው የአውሮጳ መንግስታት በመጋዘን አጉረው ፍርፋሪ የሚወረውሩላቸውን ነፈዞች እንመን ነው የምትሉት? ሲሉ ይጠይቃሉ። 

Äthiopien TV Übertragung Beisetzung General Seare Mekonnen
ምስል ETV

የሐገሪቱ ምጣኔ ሐብት እና የሥራ እድል
እስከ 2012 ዓም የበጀት ዓመት መጨረሻ 3 ሚሊዮን የሥራ እድል ለመፍጠር ማቀዱ ተጠቅሶአል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ባሰሙት ንግግር የኢትዮጵያ አጠቃላይ የሥራ አጥ ቁጥር ከ11 ሚሊዮን በላይ መድረሱን፤ በ2011 በጀት ዓመት ለ1.4 ሚሊዮን ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል። ይህን ተከትሎ በመገናኛ ብዙኃን ዘዴዎች ላይ ከተሰጡት አስተያየቶች መካከል ሰዋገኘዉ የተባሉ በትዊተር ገፅ ላይ ባሰፈሩት አስተያየት «እዉነት ግን ተጨባጭነት አለዉ? ሲሉ ያጠይቃሉ! ሰዉ አገኘሁ በመቀጠል ለነገሩ በምርጫ ዓመት የኢንቬስተሮች ማለት ማዋለ ንዋይ አፍሳሾች ቁጥር ስለሚቀንስ ፤ በሃገሪቱ የምጣኔ ሃብት እድገትም ላይ ከፍተኛ ተፅኖ ይፈጥራል ተብሎ ነዉ የሚጠበቀዉ።» ብለዋል። አቡሃይደር በበኩላቸዉ እረ በሳቅ ሞትኩኝ ይላሉ ሲጀምሩ ፤ ኸረ በሳቅ ሞትኩኝ ሦስት ሚሊዮን ሕዝብ ተፈናቅሎ እድገት ከየት ይመጣል ጉድ ውሽት» ሲሉ እንዲሁ በትዊተራቸዉ አስተያየታቸዉን አስቀምጠዋል። ጥቁር አንበሳ የተባሉ ሌላዉ የትዊተር ተከታታይ ደግሞ ኢኮኖሚዉ ያድጋል….ብለዉ ቆም ይላሉ አሰብ እንደማድረግ ነጥብ ነጥብ አስቀምጠዉ። የኤኮኖሚዉ እድገት እንዲያ ሆኖ ከወዲሁ ሊገለፅ የሚችል ቢሆን የኔም ምኞትነበር።» «በሕወሃት ዘመን የሕይወትና የምጣኔ ሐብት ጉዳይ ሕልም ነበር። ማርቆስ አለሙ የተባሉ የማኅበራዊ ገፅ ተከታታይ ናቸዉ ማርቆስ በመቀጠል እንደዉ እዉነት ሆኖ በዐቢይ ዘመን የኤኮኖሚዉም ሆነ የፖለቲካዉ ጉዳይ ቢሻሻል ምነኛ እደሰት ነበር።» ሲሉ አስተያየታቸዉን ቋጭተዋል።   


የራስ አስተዳደርን የሚጠይቁ ዞኖች ወይም ወረዳዎች
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ በፓርላማ መልስ ከሰጡባቸዉ ርዕሶች መካከል በደቡብ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል እየተነሱ ያሉ የክልል እንሁንም ጥያቄዎች ህገ መንግሥታዊ መሆናቸውንና ነገር ጥያቄውን ከህግ ውጪ ለማስፈጸም የሚደረግ እንቅስቃሴ ተገቢ አለመሆኑን የገለፁበት አስተያየት ክርክር ትችትን አስተናግዶአል። 
ቱኒካ ፍስሃ፤ ወሬ አትንዙ...ይላሉ ወሬ አትንዙ! ይህ ሲዳማን ለማስፈራራት የተሸረበ ሴራ መሆኑ ነው? ሕገ ወጥ አካል ሕዝብ ወይስ መንግስት እንደሆነ ለማንም ግልጽ ነው። አታምታቱ! በሲዳማ በኩል መንታ ስሜት ብሎ ነገር የለም። በቅርቡ ታዩታላችሁ! «ሕይወት ወልዴ የተባሉ የፊቡክ ተከታታይ በበኩላቸዉ፤ አንቀጽ 39 ክልተነሳ የባቢሎን ግንብ ካልፈረሽ ሁሉም ፍቅር አንድነት እየተባለ የሚስበክው ውሽት ነው። የብሔር ፓለቲካን ቆፍራችሁ ቅበሩት። በስላም እንኑርበት! እናንተ አመራር ላይ ያላችሁት ኢህአዲግ የምትባሉ ድርጅቶች ያፀደቃችሁት ለስው ሁሉ ሞት ምክኒያት የሆነውን አውጡት። ኢትዮጵያዊያን በድህነት አረንቋ እንተዘፈቅን የኃልዩሽ እየሄድን የብሔር ፓለቲካ አያስፈልገን! ነገ እኮ የአማራ ዶክተር ሌላ ቦታ ሄዶ ማክም አይችልም። የኦሮሞ ዶክተር አማራ ወይም ሌላ ክልል ሄዶ ማክም አይችልም። መምህሩም እንደዛው። ሁሉም በክልል እንደደሴት ታካሎ እየተገዳደለ ከ80 ተክፍሎ እንዲኖር ነው የምትፈልጉት?»
የፊታችን ሐምሌ 11፤ 2011 ዓ.ም የሲዳማ ሕዝብ አሁን ባለዉ በደቡብ መስተዳድር ስር ለማደር የማይገደድበትና በራሱ እጣ ፈንታ ላይ በራሱ ምክር ቤት ራሱ ብቻ የወሰነበትን ውሳኔ የሚያጸናበት ቀን ነው ሲል ኤጄቶ የተባለው የሲዳማ የመብት አቀንቃኝ ቡደን ካስታወቀ በኋላ ከተሰጡ አስተያየቶች መካከል ደግሞ፤ ሚኪያስ ጥላሁን «ሲዳማን መከለሉ ትልቅ ችግር ሃገሪቷ ላይ የሚጋብዝ ነው የሚል አስተያየት አለኝ» ይላሉ ። «ክልሉ» በሁሉም አቅጣጫ ቅርቃር ውስጥ የገባ ነው። ሃዲያ፣ ጌዲኦና ጉጂ - ሲዳማ ጋር የመሬትና የወሰን ግጭት ይፈጠራል፤ የማይበርድ ግጭት። ሃዋሳ ደግሞ የመከለል - አለመከለል ስጋት ያድርባታል። ልሂቃኑ ግን መከለል ይፈልጋሉ። መከለሉ ተስፋ አይፈጥርም። ችግር እንጂ...አንድ መፍትሔ ካልተፈለገ፣ ችግር ይፈጠራልና ይታሰብበት።» ብለዋል። ሃፍታይ ሃይላይ በበኩላቸዉ «መጨፍለቅ ነው አለመረጋጋትን የምያባብሰው። ሕዝቦች ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር ያልተሸራረፈ መብት አላቸው። ይህንን መብት ለመከልከል መመኮር ነው አደገኛ የሚሆነው።» ሂርጳሳ እጅጉ የተባሉ አስተያየት ሰጭ  በበኩላቸዉ «የጠቅላይ ሚነሰቴሩን መልዕክት ያልሰሙ ሰዎች የሚያወሩትን ትታችሁ የመንግሰትን ምላሽ መጠበቁ ትርፋማ ያደርጋቸዋልና መጠንቀቁ ለሁሉም ይበጃል፡፡ ፉከራዉ ጎዳን እንጂ አለጠቀመንም።» በኢትዮጵያ ለቀናቶች የኢንተርኔት መቆራረጥ ጋርዶት የጠቅላይ ሚኒስትሩ የበጀት ዓመት የዕቅድ አፈፃፀም ሪፖርት ቢሰራጭም መዲና አዲስ አበባ ብልጭ ድርግም የሚለዉ የኢንተርኔትና የዋይፋይ አገልግሎት የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴ ተጠቃሚዎችን አስተያየትና ሃሳብ ልዉዉጥ ጨርሶ አልገታም ነበር። የኢትዮጵያዉ ኢንተርኔት መስራት ጀመረ ተከፈተ ሲባል ደግሞ በዓለም ዙርያ የፊስ ቡክ እና ዋትሳፕ አገልግሎት ድርግም ብሎ ተቋርጦ ነበር። እንድያም ሆኖ ኢትዮጵያዉያን የማኅበራዊ ተጠቃሚዎች አስተያየት መልክቶቻቸዉን ተለዋዉጠዋል። አድማጮች እናንተም አስተያየቶቻችሁን አካፍሉን። 

Äthiopien | SNNPR Kultur Woche
ምስል DW/S. Wegayehu


አዜብ ታደሰ
ኂሩት መለሰ