1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የቅዳሜ ምሽት ወጣት ሰዓሊያን

ዓርብ፣ መስከረም 28 2008

ሳምንቱ እንዲህ ወደ መጨረሻው ሲቃረብ፤ ወጣቶች የአርብ እና ቅዳሜ ምሽታችሁን እንዴት ታሳልፋላችሁ? ሁለት ኑሮዋቸውን በዩናይትድ ስቴትስ ያደረጉ ወጣቶች በተለይ ከቅርብ ወራት አንስቶ የቅዳሜ ምሽትን የሚያሳልፉበት ቦታ አግኝተዋል።

https://p.dw.com/p/1GixL
Äthiopien Kunst Beteseb
ምስል Beteseb Painting

የቅዳሜ ምሽት ወጣት ሰዓሊያን

እንደ ጀርመን እና ዩናይትድ ስቴትስ ባሉ የምዕራባዊያን ሀገራት የሚኖሩ ወጣቶች ብዙ የትርፍ ጊዜ ማሳለፊያ አማራጮች አሏቸው። የሚጠቅማቸውን እና የሚጎዳቸውን፤ የሚወዱትን እና የሚጠሉትን በመለየት ጊዜ ማሳለፊያቸውን መምረጥ ግን የራሳቸው ድርሻ ነው።

አዳም መስፍን የ 26 ዓመት ወጣት ሲሆን በ«ዩንቨርሲቲ ኦፍ ሜሪላንድ »የመጨረሻ ሴሜስተር የኮሌጅ ተማሪ ነው ። የሚተዳደረውም ከትምህርቱ ጉን ታክሲ በመንዳት ነው። ከቅርብ ጊዜ አንስቶ ደግሞ ዋሽንግተን ዲሲ ውስጥ ሁለት ኢትዮጵያውያን ሰዓሊያን በጀመሩት «ቤተሰብ» የተሰኘ የስዕል ማዕከል ውስጥ ቅዳሜ ቅዳሜ ስዕል መሳል ጀምሯል።አዳም ስዕል መሳልን ሀ ብሎ አልጀመረም። ቀደም ሲል ይኖርበት በነበረው ሲያትል የሚገኝ የትምህር ተቋም በርካታ የስዕል ትምህርቶች እንደወሰደ ገልጾልናል። ሌላው ወደዚህ የ«ቤተሰብ »መሳያ ቦታ ካለፉት አራት ወራት አንስቶ መሄድ የጀመረው ናትናኤል አበበ፤ የ3ኛ ዓመት የዩንቨርስቲ ተማሪ ነው። ናትናኤል ስለዚህ የትርፍ ጊዜ ማሳለፊያ ቦታ የሰማውም፤ ከመስራቾቹ አንዱ ከሆኑት አለሜ ታደሰ ነው።
ከህፃናት አንስቶ እስከ ጎልማሳ ኢትዮጵያውያን አንድ ቦታ ተሰባስበው ስዕል መሳል የሚችሉበትን እድል መፍጠር መስራቾቹ የፈለጉበት ምክንያት አለሜ ታደሰ ገልጸውልናል።

Äthiopien Kunst Beteseb
ምስል Beteseb Painting

ወጣት ናትናኤል፤ ከዚህ በፊት ሞክሮ የማያውቀውን የስዕል ጥበብ ከማዳበር ባሻገር ቤተሰብ ፔይንቲንግ ተብሎ ወደሚጠራው መሳያ ቦታ መሄዱ ከሌሎች ወጣቶች ጋር ለመተዋወቅ ፣ ልምድና ዕውቀት ለመለዋወጥ እድል እንደፈጠረለት ይናገራል። የመሳል ልምድ ያለው አዳም ደግሞ፤ ምንም እንኳን ለመሳል ያለው ጊዜ የተወሰነ ቢሆንም ይህ አጋጣሚ ተመልሶ ስዕል ላይ እንዲያተኩር ረድቶታል።
ምሽታቸውን በመሳል ለማሳለፍ ያሰቡ ወጣቶች ግን ወደዚህ ቦታ ሲሄዱ፤ 30 ዶላር መክፈል አለባቸው። ዋጋው ተመጣጣኝ ነው ይላል ናትናኤል።
የቅዳሜ ምሽታቸውን ዋሽንግተን ዲሲ ውስጥ ስዕል በመሳል ስለሚያሳልፉት ወጣቶች እና ስለ ጊዜ ማሳለፊያው አላማ በድምፅ ዘገባ ያገኛሉ።
ልደት አበበ
ሂሩት መለሰ