የሶሪያ ዉጊያ፤ተቃዋሚዎችና ሐያሉ ዓለም
ሰኞ፣ ጥቅምት 26 2005
05 11 12
የሶሪያ ጦርነት ለወትሮዉ የሐብት-ቴክኖሎጂ ጉልበቷን ያክል በዓለም ፖለቲካ ተፅኖ በማሳረፍ ብዙም የማትታወቀዉን ጃፓንን ጣልቃ አስገብቷል።የሶሪያ አማፂያንን በግልፅ የሚረዱት፥የእስራኤል ጥብቅ ወዳጆች ፈረንሳይና ብሪታንያ በልማዱ የእስራኤል «ጠላት» ለሚባሉት አረቦች የጦር መሳሪያ ለመሸጥ እየባተሉ ነዉ።የሶሪያ መንግሥት ደጋፊ የምትባለዉ የሩሲያ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር፥ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ልዩ መልዕክተኛም ካይሮ ነበሩ።ከአንድነታቸዉ ይልቅ ልዩነታቸዉ የጎላዉ የሶሪያ አማፂያን ደግሞ ዶሐ-ቀጠር ላይ ተሰብስባዋል።የሶሪያ ተቃዋሚዎች ስብሰባ መነሻ፥የጦርነቱ ግመት ማጣቀሻ፥ የሐያሉ ዓለም ርብርብ መድረሻችን ነዉ ላፍታ አብራችሁኝ ቆዩ።
የዓለም ብቸኛ ልዕለ ሐያሊቱ ሐገር እንደ አብዛኛዉ ዓለም ሁሉ በሶሪያ ጦርነት፥ ዉዝግብ የምትሳራፍዉ ተፅዕኖ እንዴት፥ወዴትነትን ለማወቅ የነገዉን ምርጫ ዉጤት መጠበቅ ግድ ነዉ።የዩናይትድ ስቴትዋ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሒላሪ ክሊንተን ባለፈዉ ሳምንት እንዳሉት ግን ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ የያዙትን ሥልጣን እንደያዙ ከቀጠሉ ዋሽግተን ትልቁ በሚባለዉ የሶሪያ ተቃዋሚ ቡድን ላይ የነበራት እምነት ተስፋ፥የምትሰጠዉ ድጋፍም እንደነበረ አይቀጥልም።
«SNC ከእንግዲሕ እንደ ተቃዋሚዎች ዋና መሪ እንደማይታይ ግልፅ አድርገናል።እነሱ የሰፈዉ ተቃዋሚ አካል ሊሆኑ ይችላሉ፥ ተቃዋሚዉ ደግሞ ሶሪያ ዉስጥና ሌላ ሥፍራም ያሉ፥ ድምፃቸዉን የማሰማት ተገቢዉ መብት ያላቸዉን ሁሉ የሚያካትት መሆን አለበት።»
የቀድሞዉን የሊቢያ የረጅም ጊዜ መሪ የኮሎኔል ሙዓመር ቃዛፊን አገዛዝ ለማስወገድ ተሰይሞ ከነበረዉ ስብስብ፣ ሥም፥ ቅርፅ እና አላማዉን፥ የወረሰዉ የሶሪያ ብሔራዊ ምክር ቤት (SNC) በርግጥም ደጋፊዎቹ እንደፈለጉት ጠንካራ ተቃዋሚ መሆን አልቻለም።የቡድኑ መሪዎችም ደጋፊ-ረዳቶቻቸዉን አለማስደሰታቸዉን ጠንቅቀዉ ያዉቁታል።
እንደ ሊቢያ ብጤዎቻቸዉ የደማስቆ ቤተ-መንግሥትን ፈጥነዉ ያለመያዛቸዉ ድክመት ወይም ምክንያት ግን የምክር ቤቱ ሊቀመንበር አብዱል ባሲጥ ሰይዳን እንዳሉት ቡድናቸዉ የሊቢያ ቀዳሚዉን አይነት ድጋፍ ከምዕራባዉያን ባለማግኘቱ ነዉ።
የሊቢያ አማፂያን ትሪፖሊ ቤተ-መንግሥት የዶለዉ የምዕራባዉያን ሐይል ጦር ድብደባ ነበር። ምዕራባዉያኑ የኮሎኔል ሙዓመር ቃዛፊ አገዛዝን ለማስገድ ያዘመቱትን አይነት ጦር በፕሬዝዳት በሽር አል-አሰድ ላይ ለማዝመት እስካሁን አቅሙና ፍላጎቱ ያላቸዉ አይመስልም።ቢኖራቸዉ እንኳን የሩሲያና የቻይና ተቃዋሚዎቻቸዉን እንደከዚሕ ቀደሙ ማግባባት ወይም ማታለል አልቻሉም።
ዩናይትድ ስቴትስ በሶሪያዉ ብሔራዊ ምክር ቤት ላይ ያላት ዕምነት የተሸረሸረዉ ወይም ሌላ አማራጭ ለመፈለግ የተገደደችዉ ግን ምክር ቤቱ የደማስቆ ቤተ-መንግሥትን ፈጥኖ ባለመቆጣጠሩ አይደለም።በተራዘመዉ ጦርነት ምዕራባዉያን ከሚፈልጓቸዉና ለዘብተኛ ከሚሏቸዉ አማፂያን ይልቅ ክሊንተን እንዳሉት ሐይማኖታዊ ፅንፈኞች እየተበራከቱ ምናልባትም የበላይነትን እየያዙ መምጣታቸዉ ሥላሰጋቸዉ ነዉ።
«እኛ ከዚሕም በተጨማሪ የሶሪያን አብዮት ለመጥለፍ ፅንፈኞች የሚያደርጉትን ጥረት አጥብቆ የሚቋቋም ተቃዋሚ እንደልጋለን።ፅንፈኞች፥ጨቋኝ አገዛዝን በመቃወም የተቀሰቀሰዉን ተገቢ አብዮት ለራሳቸዉ አላማ ለማዋል ወደ ሶሪያ እየገቡ መሆናቸዉን የሚጠቁም ዘገባ አለ።»
የሶሪያ ብሔራዊ ምክር ቤት ሊቀመንበር አብዱል ባሲጥ ሳይዳን ለክሊንተን ወቀሳ፥ «ለአክራሪዎች መበራክት ተጠያቂዉ እራሱ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ነዉ-ከማለት ሌላ ዝር ዝር መልስ ለመስጠት አልደፈሩም።
በሶሪያዉ ጦርነት ሙስሊም አክራሪዎች ደማስቆን ከማሸበር እስከ ፊትለፊቱ ዉጊያ እንደሚሳተፉ በተደጋጋሚ ሲያስተነትኑ የነበሩት የፖለቲካ ተንታኞች፥ የመብት ተሟጋቾችና ጋዜጠኞች ግን በክሊንተን የዘገየ አነጋገር ፈገግ ሳይሉ አይቀሩም።RT በሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ የሩሲያ ዓለም አቀፍ ቴሌቪዥን ጣቢያ የፖለቲካ ተንተኛ ደግሞ «ዩናይትድ ስቴትስ አፍቃኒስታን ዉስጥ የምትዋጋቸዉን አክራሪዎች» ሶሪያ ዉስጥ እየደገፈች ነዉ በማለት እስከመተቸት ደርሶ ነበር።
ለሶሪያ ሕዝብም ሆነ፥ ዩናይትድ ስቴትስን ከመሸም ቢሆን ያሰጋዉን የአክራሪዎችን ሩጫ ለመግታት፥ ወይም ለሶሪያ ሕዝብ ለሚያስቡ ተዋጊዎች ሁሉ አብነቱ ሠላም ማስፈን ነዉ።
ሠላም የማስፈን ተልዕኮ የተሰጣቸዉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትና የአረብ ሊግ ልዩ መልዕክተኛ ላሕዳር ብራሒሚ ግን ሰላም ለማዉረድ እስካሁን የተከሩት የለም።የድሮዉ አለቃቸዉ እና የልዩ መልዕክተኝነቱን ሥልጣን «በበቃኝ» የተዉት ኮፊ አናን በተደጋጋሚ ብለዉት የነበረዉን ከመድገም ግን አሁንም አልቦዘኑም።
«የሶሪያ ቀዉስ በጣም፥ በጣም አደገኛ ነዉ።ሁኔታዉ መጥፎ ነዉ።እየበሰ ነዉ።የሶሪያ ሕዝብ ከቀዉሱ የሚያወጣዉ መፍትሔ እንዲያገኝ ለመርዳት መላዉ አለም አቀፍ ማሕበረሰብ በጋራ መቆም አለበት።»
በልማዱ «ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ» የሚባለዉን ወገን ባንድ መስመር የማጓዝ ጉልበት፥ ሐይል፥ አለም አቀፋዊ ሥልጣንም ያላቸዉ አምስቱ የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ቋሚ አባል ሐገራትን እንኳን አንድ አቋም አልያዙም።በሳምንቱ ማብቂያ ሊባኖስን የጎበኙት የፈረንሳዩ ፕሬዝዳት ፍራንሷ ኦላንድ ቤይሩት ላይ በሊባኖስ ላይ የሚቃጣ አደጋን ለመመከት መንግሥታቸዉ ከሊባኖሶች ጎን እንደሚቆም ቃል ገብተዋል።
ኦላንድ የቀድሞ የሐገራቸዉን ቅኝ ተገዢ ለመታደግ መንግሥታቸዉ ከቤይሩት ጎን የሚቆመዉ አደጋዉ እንደ ከዚሕ ቀደሙ ከእስራኤል ሲመጣ ነዉ ብሎ መገመት ጅልነት ነዉ።ከሶሪያ እንጂ።ኦላንድ ሪያድ ሳዑዲ አረቢያ ሲገቢ ደግሞ ፥የሶሪያ ተቃዋሚዎች የሽግግር መንግሥት ቢመሰርቱ ፈረንሳይ እንደምትደግፍ አስታዉቀዋል።
የብሪታንያዉ ጠቅላይ ሚንስትር ዴቪድ ካሜሩንም ወደ መካከለኛዉ ምሥራቅ ሄደዋል።ካሜሩን ከተቃዋሚዎቻቸዉ የሚሰነዘርባቸዉን ወቀሳና ትችት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያየለ ነዉ።በተለይ የዋነኛዉ ተቃዋሚ የሌበር ፓርቲ መሪ ኤዲ ሚሊባንድ በቀደም ካሜሩንን በዉጪም በዉስጥም መርሕ እጅግ ደካማ በማለት ክፉኛ ተችተዋቸዋል።
«የአዉሮጳ መሪዎችን ማሳመን አልቻለም።የራሳቸዉን ደጋፊዎች እንኳን ማሳመን አልቻሉም።በዉጪ ደካማ ናቸዉ።ሐገር ዉስጥም ደካማ ናቸዉ።በሁሉም መንገድ ዳግማዊ ጆን ሜጄር ናቸዉ።»
ካሜሩን ሰወስት የአረብ ሐገራት ለመጎብኘት ዛሬ ከለንደን የተነሱት ይሕን መሰሉትን ተቃዉሞ ለማቀዝቀዝ ወይም ጠንካራነታቸዉን ለማሳየት ይሆን-ይሆናል።በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፥ በሳዑዲ አረቢያና በኦማን የሚያደርጉት ጉብኝት ዋና አለማ ግን ሐገራቸዉ ከሌሎች የአዉሮጳ ሐገራት ጋር ሆና የምታምርተዉን ተዋጊ አዉሮፕላን ለመሸጥ ነዉ።
በልማዱ «የእስራኤል ጠላት» የሚባሉት አረቦች አዲስ በሚታጠቁት ጄት እስራኤልን «ንክች» ማድረግ እንደማይችሉ ለማወቅ ሻጭ-ገዢዎች እስከሚናገሩ መጠበቅ አያስፈልግም።የእስራኤል ባለሥልጣናት ትናንት እንዳስታወቁትም ዋና ስጋታቸዉ ሐገራቸዉ በሐይል ወደያዘችዉ የሶሪያ ግዛት ወደ ጎላን ኮረብታ ሰወስት የሶሪያ ታንኮች መጠጋታቸዉ እንጂ የነሳዑዲ አረቢያ አዲስ ጄት የመታጠቅ እቅድ አይደለም።
ካሜሩን በጉብኝታቸዉ ወቅት እንደ ፈረንሳዩ ፕሬዝዳት ሁሉ የሶሪያ ተቃዋሚዎች የሽግግር መንግሥት ይመስርቱ ማለታቸዉ አይቀርም።ሐሳቡን ዩናይትድ ስቴትስ፥ ማንም ይምራት ማን ትቃወመዋለች ተብሎ አይጠበቅም።ኦላንድ ቤይሩትን ሲገበኙ ካይሮ የነበሩት የሩሲያዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ ግን ገና ከንግግር ያላለፈዉን ሐሳብ ዉድቅ አድርገዉታል።ሚንስትሩ እንዳሉት የሶሪያን መንግሥት የማያሳትፍ የሽግግር መንግሥት ትርጉም የለዉም።
ሩሲያና ቻይና ባይቃወሙት እንኳ የይስሙላ ካልሆነ በስተቀር የተከፋፈሉትን የሶሪያ አማፂያንን አንድ አድርጎ አንድ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ተዓምራዊ ሐይልን ማግኘት ግድ ይላል።እርግጥ ነዉ የዩናይትድ ስቴትሷ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ማስጠንቀቂያ በተሰማ ማግስት የቀጠር መሪዎች የሶሪያ አማፂያን የጋራ ግንባር እንዲፈጥሩ ለማግባባት ዶሐ ላይ ሰብስበዋቸዋል።
አራት ቀን ይፈጃል የተባለዉ ጉባኤ ተሳታፊዎች ግን ስብሰባቸዉን ትናንት ከመጀመራቸዉ አንዳቸዉ ከሌለኛቸዉ ጋር ለመነጋገር ፍቀደኛ አለመሆናቸዉን በግልፅ እያስታወቁ ነዉ።በዚሕ መሐል ነዉ፥-እስከ ዛሬ ዋሽንግተኖችን ከመከተል ባለፍ በተለይ በሶሪያ ጉዳይ ድምፅዋ ተሰምቶ የማያዉቀዉ ጃፓን «የሶሪያ ወዳጆች» የሚባሉትን ሐገራት ለጉባኤ የጠራችዉ።
የሶሪያ ወዳጆች የሚባሉት ሐገራት ባለሥልጣናት ካለፈዉ ሚዚያ ጀምሮ እንደ «ወርሐዊ እቁብ ጣይ» በየጊዜዉ ይሰበሰባሉ።ስብሰባዉ ባለፈዉ ሚዚያ ፓሪስ ነበር። ሰኔ፥ ዋሽግተን፥ ሐምሌ ዶሐ፥ መስከረም ዘ-ሔግ።ጃፓኖች በያዝነዉ ማብቂያ ቶኪዮ ላይ የጠሩት ስብሰባ ወርሐዊ ልማዱን ከማሟላት ሌላ ለሶሪያ ሠላም፥ ለሐያላኑ ይሁን ለተቃዋሚዎቹ አንድነት የሚተክረዉ መኖሩ ሲበዛ አጠራጣሪ ነዉ።
ሶሪያዎች ግን እያለቁ፥ እየተላለቁ ነዉ።አንዳድ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት በየሰአቱ ስድስት ሶሪያዊ ይገደላል።የሚቆስለዉን የቆጠረዉ የለም።በሺ የሚቆጠር ይሰደዳል።የሚገደለዉን ማዳን አልተቻለም። የሚሰደደዉን ግን፥ የጀርመንዋ መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ባለፈዉ ሳምንት ለቱርኩ ጠቅላይ ሚንስትር ለጠይብ ኤርዶኻንን በርሊን ላይ እንደነገሩት ጀርመን ለመርዳት ዝግጁ ናት።
«በጀርመን በኩል፥ እርዳታዋ እስከተፈለገ ድረስ ሰብአዊ ርዳታ ለማቅረብ ፍቃደኞች መሆናችንን ገልጠናል።በሌላ በኩል የሶሪያ ግጭት ከተነሳበት ጊዜ ጀምሮ (ግጭቱ) እንዳይባባስ ቱርክ እስካሁን በጥሞና ላደረገችዉ አስተዋፅኦ መመስገን አለባት።»
ሁለተኛ ዓመቱን ሊደፍን ወራት የቀሩት ጦርነት ዘግናኝ ግፎችም እየተፈፀሙበት ነዉ።ጨቋኝ፥ ሥርዓትን ለማስወገድ እንታገላለን የሚሉት አማፂያን በተማራኪ ወታደሮች ላይ የፈፀሙት ግፍ አማፂያኑ የጨቋኞቹ ገዢዎች ግልባጭ እንዳይሆኑ እያሰጋ ነዉ።
የዓለም አቀፉ የመብት ተሟጋች ድርጅት የአምንስቲ ኢንተርናሽናል ባልደረባ ማሐ አቡ ሻማ እንደሚሉት ግፉ ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎችን በግልፅ የጣሰ ነዉ።«በቪድዮዉ እንደታየዉ የተማረኩት ሰዎች፥ ክፉኛ ተንገላተዋል፥ ተደብድበዋል፥ በመጨረሻም ተገድለዋል።ይሕ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ጥበቃ ሕግን መጣስ ነዉ።»
የጥንታዊዉ ሰዉ ሥልጣኔ መሠረት፥ የታታላቅ ሐይማኖቶቹ መዳበሪያ፥ ታሪካዊት ሐገር፥ የወደፊት ጉዞዋ አሁንም መንታ መንገድ ላይ ነዉ።የሰለጠነ፥ ያመነ፥ የተጠበባት ዓለም ግን በነባር አኩሪ ታሪኳ ላይ የልቂት ፍጅት አሳዛኝ ታሪክ እየተጨመረበት ነዉ።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።
ነጋሽ መሐመድ
ተክሌ የኋላ