1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሶማሊያ 50ኛ ዓመት የነጻነት በዓል

ሐሙስ፣ ሰኔ 24 2002

አክራሪው እስላማዊ ቡድን በዓሉ ላይ እገዳ ጥሏል። በዚህም የተነሳ ከሞቃዲሾ የተወሰነ ክፍል በስተቀር በአብዛኛው ሶማሊያ የነጻነት በዓሉ አይከበርም።

https://p.dw.com/p/O8NQ
ሶማሊያ በነጻነት ቀኗም ሰላም አላገኘችምምስል AP

ጁላይ 1 1960- ሶማሊያ ነጻነቷን የተጎናጸፈችበት ቀን። 50ኛ ዓመቷን ዛሬ ትዘክራለች። ለሶማሊያውያን በእርግጥ ታላቅ ዕለት ነው። ህዝቡ በዚህ ዕለት እንኳን አደረሰህ እያለ እርስ በእርሱ ደስታውን የሚገልጽበት ዕለት ነው።ይህ ዕለት ለሶማሊያውያን ልዩ ትርጉም አለው። በሀገሪቱ የፓለቲካና የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ አዲስ አቅጣጫን ያመጣ ዕለት ነው። አንዳንድ ሶማሊያውያን ስለዚህ የነጻነት ቀን ሲገልጹ፤ ህዝቡ ሀሳቡን ፣ ምኞቱን ፣ ለሀገሩ ያለውን ፍቅር የሚጋራበት አንድ ቀን ቢኖር ዛሬ ነው በማለት ነው። እናም ይህ ቀን ትርጉም ያለው ታላቅ ዕለት ነው።

በእርግጥ በዚህ ዕለት በመላ ሀገሪቱ ፌሽታዎች ነበሩ። በዓላት ነበሩ። በዚህ ልዩ ቀን ህዝቡ በከፍተኛ ስሜት ውስጥ ሆኖ ያከብር ነበር። ሆኖም አሁን ያን ማድረግ አልቻለም። ነገሮች የተለየ መልክ ይዘዋል። በተለይ በደቡባዊ ሶማሊያ ያለው ህዝብ በዚህ ዓመት የነጻነት ቀኑን እንዲያከብር እድል አልተሰጠውም። ምክንያቱም የእስላማዊ ቡድኑ የሶማሊያ 50ኛ ዓመት ክብረበዓልን በተመለከተ ማንኛውንም ዓይነት ዝግጅት እንዳይደረግ በመከልከላቸው።

እገዳው በሸሪዓ ህግ መሰረት የተደረገ ነው። በሚቆጣጠሯቸው አከባቢዎች የሸሪዓ ህግ ተግባራዊ እንደሆነ ገልጸዋል። ማንኛውም ዓይነት በዓል በተለይም ህዝብ ተሰብስቦ ፣ በሙዚቃ እየጨፈረ የሚያከብራቸው ሥነሥርዓቶች ፈጽሞ የተከለከሉ መሆናቸውን አክራሪው ቡድን ይናገራል። በአጭሩ በእስልምና ፌሽታ የተከለከለ ነው ይላል። ከመንግስት አንጻር አልያም ከማንኛውም ቡድን ጋር በተያያዘ ሳይሆን በሸሪዓ ህግ የተነሳ እንደተከለከለ ነው የሚገልጸው።

ብዙው ሰው በሁኔታው በጣም ተቆጥቷል። ይህን ታላቅ ቀን መዘከር አለመቻሉ አበሳጭቶታል። በተለይ ከሶማሊያ ውጭ የሚኖሩ ሶማሊያውያን የተጣለውን ማዕቀብ አውግዘውታል። የሆኖ ሆኖ በዚህ ጊዜ እንኳን ከባድ ግጭቶች በሞቃዲሾ እየተካሄዱ ናቸው። አሁን እየተናገርኩ ባለሁበት ቅጽበትም በሞቃዲሾ ጦርነቱ ቀጥሏል። እናም ህዝቡ በዚህ ሁኔታ በዓሉን የማክበር ፍላጎቱ ያለው አይመስለኝም። ሶማሊያውያን እርስ በእርስ እየተላለቁ ፣ የነጻነት ቀንን ማክበር ትርጉም የለውም የሚል ስሜት አድሮበታል።

የሶማሊያ መንግስት መሠረት የሆነው የሞቃዲሾ ሬዲዮ፣ 50ኛ ዓመት የነጻነት በዓልን የተመለከተ ልዩ በዓል በሞቃዲሾ ቤተመንግስት እንደሚያከብር የሚገልጽ ማስታወቂያ እያስለፈፈ ነው። ይሁንና እስላማዊ ቡድኑ በሚቆጣጠራቸው የሶማሊያ የተቀሩ ክፍሎች በተጣለው እገዳ የተነሳ ማንም ሰው ለበዓሉ ዝግጅት እያደረገ አይደለም።

መሳይ መኮንን

አርያም ተክሌ