1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሳቴላይቶች ስብርባሪና ጽዳት

ረቡዕ፣ የካቲት 5 2006

ታላላቆቹ መንግሥታት ፤ ዩናይትድ ስቴትስ፤ ሩሲያ፣ ቻይና ፣ ህንድና ሌሎችም ኅዋን በማሰስ ፤ ጨረቃንና ማርስን ዒላማ በማድረግ ፉክክራቸውን እንደቀጠሉ ናቸው። አዳዲስ የኅዋ ጣቢያዎችን የማቋቋም እቅድም አላቸው። የተጠቀሱት ሀገራት ብቻ ሳይሆኑ ፤

https://p.dw.com/p/1B7eE
ምስል picture-alliance/ dpa

የተለያዩ የአውሮፓ ሃገራትን የሚያስተሣሥረው ፤ የአውሮፓ የኅዋ ድርጅትም አለ።በዳርምሽታት ፤ ጀርመን የሚገኘው የአውሮፓ የኅዋ ድርጅት የጠፈርተኞችን የበረራ ተልእኮ የሚመለከተው ክፍል ዋና ሥራ አስኪያጅ ቶማስ ራይተር ፣ እንዳስታወቁት፣ እስካሁን ለዓለም አቀፉ የኅዋ የምርምር ጣቢያ ሰፊ ወጭ በማድረግ በምርምር ላይ ይበልጥ ቢያተኩርም፣ ከ 20 በማያንሱ የአውሮፓ ፤ በአመዛኙም የአውሮፓው ኅብረት አባል ሃገራት እ ጎ አ በ 1975 ዓ ም የተቋቋመው ፣ዋና ማዕከሉ ፣ በፓሪስ ፣ ፈረንሳይ የሚገኘው ፣ የአውሮፓ የኅዋ ምርምር ድርጅት(ESA)፣ ወደፊት፣ ራሱን ችሎ ፣ በራሱ መርኀ ግብር ጠፈርተኞቹን ወደ ኅዋ መላኩ የማይቀር ነው ። ይህን ዓላማውን ለማሣካትም በኮሎኝ ከተማ መዳረሻ በ PORZ የጠፈርተኞች ማሠልጠኛ ጣቢያ ካቋቋመ ቆይቷል። ቶማስ ራይተር እንዳስረዱት ድርጅቱ ፣ ጠፈርተኞችን በቀጥታ ወደ ጨረቃ ከመላኩ በፊት፤ በቅድሚያ ፤ ከ 4 ዓመት በኋላ የጨረቃን ደቡባዊ ዋልታ የሚያጠና መንኮራኩር የማምጠቅ እቅድ አለው።

Laser Prisma The Dark Side of the Moon von Pink Floyd
ምስል cc by LightwaveIntl sa 3.0

ጨረቃ ላይ የምርምር ጣቢያም ይቋቋማል፤ ይህ በፊናው በምድራችን የሚሆነውን በጥሞና ለመከታተል፤ የአየር ንብረት ለውጥን ለማጥናት ይበጃል ነው የተባለው። ይህ ብቻ አይደለም፤ የስልክ መገናኛን ለማሻሻል፤ እንዲሁም በሳቴላይት ድጋፍ አቅጣጫ የመምሪያ አገልግሎትን ለማበርከት በጨረቃ ላይ የሚገነባው ጣቢያ ሰፊ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ነው የሚነገረው።

ተማስ ራይተር እንደሚሉት ከሆነ፣ የአውሮፓው የኅዋ ምርምር ድርጅት ቀጣይ ጥረት ወይም ግብ በጨረቃ የሚገደብ አይደለም ፤ ጨረቃ እንዲያውም ፤ ከዚያ ለሚርቅ እንበል ወደ ማርስ ለሚደረግ ጉዞ መናኸሪያ፤ መዘጋጃና ልምምድ ማድረጊያ ትሆናለች። «ወደፊት፣ አንድ አውሮፓዊ በማርስ ቀይ አቧራማ ሜዳ ወይም ኮረብታ ላይ እግሩን ማሳረፉ አይቀርም። ይህ ሲሆን ፤ ምቹ ወንበር ላይ ተቀምጬ፣ በቴሌቭዥን ፣ ድርጊቱን እንደማይ ተሰፋ አለኝ » ሲሉም ፣ አሁን የማደረጃቱን ተግባር የሚያከናውት የቀድሞው ማለትም እ ጎ አ ከ 1992 -2007 ጠፈርተኛ የነበሩት ቶማስ ራይተር ምኞታቸውን ገልጸዋል።

እ ጎ አ በ ጥቅምት ወር 1957 ዓ ም ፣ የያኔዋ ሶቭየት ሕብረት ፤ በዓለም ውስጥ የመጀመሪያቱን ሰው ሠራሽ ሳቴላይት (ስፑትኒክ)ካመጠቀችበት ጊዜ አንስቶ በኅዋ የሚወነጨፉ ጥቃቅን ነገሮችን የሚከታተለው የዩናይትድ ስቴትስ የኅዋ የቁጥጥር መረብ

(Space Surveillance Network)(SSN)ከ 12 ቀናት በፊት ይፋ ባደረገው መግለጫ መሠረት ፤ ከ 24,500 በላይ በአመዛኙ ፣ ምኅዋራቸውን በትክክል ሳይከተሉ ከመሬት ፈንጠር ብለው ኅዋ ላይ የሚዞሩ ፈጣን የሳቴላይት ስብርባሪዎችን ሂደት ይቆጣጠራል። SSN ስብርባሪዎቹ ከየትኛው ሀገር ሳቴላይት እንደሆኑም ለይቶ መመዝገብ የቻለ የቁጥጥር መረብ ነው። የዩናይትድ ስቴትሱ፣ ብሔራዊ የበረራና የኅዋ አስተዳደር መሥሪያ ቤት እንደሚለው ከሆነ ፣ ኅዋ ውስጥ በግምት 8,000 ከሚሆኑት ሰው ሠራሽ ቁስ አካላት መካከል ተግባራቸውን የሚያከናውኑ 3,000 ያህል ሳቴላይቶች ይገኛሉ። እነዚህ ሁሉ ከምድራችን 200 ኪሎሜትር ፈንጠር ብለው ነው ኅዋ ላይ ምኅዋራቸውን ይዘው የሚከንፉት።

Upperstage explosion H1
ምስል ESA

አንድ የመገናኛ አልግሎት ሰጪ ሳቴላይት ከ 5 እስከ 20 ዓመት ያህል ነው የሚያገለግለው። ከቀድሞዋ ሶቭየት ኅብረት የተረከበችው ሩሲያ ፤ እ ጎ አ ከ 2008 ወዲህ ባጠቃላይ 1n400 ያህል ገደማ ዩናይትድ ስቴትስ 1,000 ፣ ጃፓን ከ 100 በላይ፤ ቻይና 80 ያህል፤ ፈረንሳይ ከ 40 በላይ፤ ህንድ ከ30 በላይ፤ ጀርመን ወደ 30 የሚጠጉ፤ ብሪታንያና ካናዳ 25፤ ኢጣልያ፤ አውስትሬሊያ፣ ኢንዶኔሺያ ብራዚል ፤ ስዊድን፤ አርጀንቲና ፤ ስዑዲ ዐረቢያና ደቡብ ኮሪያ እያንዳንዳቸው ከ 10 ያላነሱ ሳቴላይቶች ያሏቸው መሆኑ ነው የተገለጠው።

ታዲያ ከዓለም አቀፉ የኅዋ ምርምር ጣቢያ ወይም ቤተ ሙከራ ጋር ንዑስ ነገር እንኳ ቢላተም እጅግ እስከፊ ሁኔታ ነው የሚከሠተው። ዳርምሽታት ፣ ጀርመን ውስጥ ፣ በአውሮፓው የኅዋ ምርምር ድርጅት ፤ በኅዋ የስብርባሪ አካላትና ትቢያ አጥኚ ክፍል ኀላፊ ፤ ሃይነር ክሊንክራድ እንዲህ ማለታቸው ይታወሳል።

«አንድ ሴንቲሜትር የሚሆን ሥባሪ ዕቃ እጅግ ከፍተኛ በሆነ ፍጥነት የሚወነጨፍ በመሆኑ (በሰዓት ከ 50ሺ ኪሎሜትር በላይ ነው ፍንጥነቱ)ታዲያ በዚህ ፍጥነት ከአንድ ሳቴላይት ጋር ቢላተም የሚፈጠረው የኃይል መጠን የአንድ የእጅ ቦንብ ያክል ነው ነው።»

ይህ እንግዲህ፣ አንድ ሳቴላይት ለመደምሰስ በቂ ኃይል አለው ማለት ነው። የተፈረካከሱትና የሚከንፉት ኢምንት ቁስ አካላት 750 ሺ እንደሚሆኑ ነው የሚነገረው። በምድራችን ዙሪያ የሚሽከረከሩት እጅግ አነስ ያሉት አንድ ሚሊሜትር የሚሆኑ እንኳ የአንድን ጠፈርተኛ ልዩ ልብስ መብሳት የሚችሉ ናቸው። ጥንቃቄ የሚያሻውን የምርምር መሳሪያም በቀላሉ ከጥቅም ውጭ ነው የሚያደርጉት። እነዚህ ንዑሳን የአሸዋ ጠጠር መጠን ያላቸው የሳቴላይት ሥብርባሪዎች፣ ቁጥራቸው 160 ሚሊዮን እንደሚሆን ነው የሚታሰበው። የአውሮፓው የኅዋ ምርምር ድርጅት ጠበብት እንደሚሉት 6,500 ቶን የሚሆን የደቀቀ፤ የሳቴላይቶች ስብርባሪ ነው የትቢያ መቀነት የፈጠረው። ባለፈው ወር 16,674 ሥብርባሪ ከዚህ መካከል የብርቱካን መጠን ያለው 9464 ያህል ፍርካሽ ኅዋውን አስጨንቆታል። እ ጎ አ የካቲት 10 ቀን 2009 ዓ ም፤ ከሳይቤሪያ አናት፣ ኅዋ ላይ 800 ኪሎሜትር ርቀት፣ የዩናይትድ ስቴትስ «ኢሪዲዬም 33» የተባለውና «ኮስሞስ 2251» የተባለው የሩሲያ ሳቴላይቶች ተላትመው ፍርክስክሳቸው መውጣቱና ፤ 2,200 ያህል ሥብርባሪዎች መቆጠራቸው ነው የሚነገረው። ቻይና ፤ ከዚያ ቀደም ሲል ጥር 11 ,2007 ለፍተሻ፤ 850 ኪሎሜትር ርቀት ላይ የአየር ጠባይ ጠቋሚ ሳቴላይቷን በሌላ ሳቴላይት ባነጎደችበት እርምጃ፤ ሥብርባሪው ከ 3000 በላይ ደርሶ እንደነበረ ነው ለመገንዘብ የተቻለው።

Weltraum Schrott
ምስል ESA

በአውሮፓው የኅዋ ምርምር ድርጅት ፣ ኅዋን የማጽዳት እንቅሥቃሴ መሪ የፊዚክስ ባለሙያ ሉሲያና ኢኖሴንቲ እንዲህ ይላሉ----

«ዋናው ነገር እነዚህ ሁሉ ስብርባሪ ቁስ አካላት ፣ እንዲሁ፣ ሰው ሄዶ ፣ በቀላሉ የሚለቅማቸው አይደሉም። እንዴት መከናወን እንደሚችል፤ አናውቅም። ከባድ ነው፤ መቆጣጠር ከባድ ነው። እጅግ ከፍ ባለ ፍጥነት የሚከንፉ፣የሚወነጨፉ በመሆናቸውም ነው ---አስቸጋሪነቱ! ስለዚህ ጠጋ ብለን፤ የኃይለኛው ሙቀት ሰለባ ላለመሆንም በመጠንቀቅ ፣ ሥብርባሪዎቹን ማጥመድ፤ መሰብሰብ፤ ከዚያም ወደ ምድር በማውረድ የት ትክክለኛ ቦታ ላይ እንደምንጥላቸው እርግጠኞች መሆን ይኖርብናል። ቦታው ሌላ አይሆንም፣ ያው ውቅያኖስ ነው። »

በመግቢያችን ላይ እንዳወሰነው፤ በቴክኖሎጂ የገፉት 10 ያህል መንግሥታት ብቻ ሳይሆኑ ገንዘብ ያላቸውና የመገናኛ አውታሮቻቸውን ለማሻሻል የፈለጉ በዛ ያሉ መንግሥታትና ድርጅቶችም በእነርሱ እርዳታ የመገናኛ ሳቴላይቶች መጥቀውላቸዋል። በአጠቃላይ ከ 50 በላይ የሚሆኑ መንግሥታት በዚህ ዓይነት ተጠቃሚዎች ለመሆን በቅተዋል። ወደፊትም በዛ ያሉ መንግሥታት የዚህ ሥነ ቴክኒክ በረከት ተቋዳሾች ለመሆን አጥብቀው ነው የሚሹት። ታዲያ ፤ ከምድራችን 200 ኪሎሜትር ገደማ ራቅ ብሎ ለሚገኘው በሥብርባሪ ብረታ ብረት፣ አቧራና ትቢያ ቆሸሸው፣ በተለይ ደግሞ ወደፊት ወደ ኅዋ ለሚመጥቁና ፤ በዚያም ለሚሽከረከሩ መንኮራኮሮች ብርቱ አደጋ ለደቀነው የኅዋ ከፊል የሚበጅ መላ ካልተፈለገ ከጥቅሙ ጉዳቱ ነው የሚያመዝን የሚሆነው። ከ 900 እስከ አንድ ሺ የሚሆኑ የስልክ፤ የአየር ጠባይ ትንበያና የቴሌቭዥን አገልግሎት ሰጪ እንዲሁም አቅጣቻ መሪ ሳቴላይቶችን በሌላ እንዲተኩ ለማድረግ ቢፈለግ 100 ቢሊዮን ያህል ዩውሮ ነው የሚጠይቀው። በኤኮኖሚ ላይ የሚደርሰው ጉዳት ደግሞ ከተጠቀሰው ገንዘብ እጅግ የላቀ ነው።

Trackable objects in orbit around Earth
ምስል ESA

ታዲያ ምንድን ነው የሚበጀው? በኅዋ ምርምር የገፉትንም ወደፊትም ወደዚህ ፊታቸውን ለማዞር የተነሣሱትን ሁሉ የሚያሳስብ በመሆኑ መላ መሻት የግድ ነው። በእሽቱትጋርት ከተማ የጀርመን የበረራና የኅዋ ማዕከል የቴክኒካዊ ፊዚክስ ተቋም ባልደረባ፤ ቮልፍጋንግ ሪደ ፣ አብነቱ ኃይለኛ ሙቀት የሚፈነጥቅ ሰው ሠራሽ ብርሃን LASER ነው ። በዚያው ሽቱትጋርት በሚገኘው ግዙፍ የሩቅ አጉልቶ ማሳያ መሳሪያ(ቴሌስኮፕ) የሳቴላይት ስብርባሪዎችን ምኅዋር በትክክል ማሳየት መቻሉን የገለጡት ሪደ፤የጀርመን የኅዋ ምርምር ቡድን፤ LASER በኀዋ የሳቴላይቶች ሥብርባሪ ላይ እንዲፈነጥቅ በማድረግና፤ በምድር ላይ በተተከለ ቴሌስኮፕ በመቆጣጠር ይበልጥ ለዒላማው የተጠጋ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን አስረድተዋል።ቡድኑ ፤ ኃይል ባለው LASER በኅዋ የተከማቸውን ሥብርባሪና ትቢያ እንቅሥቃሴ ፍጥነት በመግታት ፤ ወደ ምድራችን ከባቢ አየር እየወደቁ ተቀጥለው እንዲጠፉ ለማድረግ አቅድ ማውጣቱ ታውቋል።

ተክሌ የኋላ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ