1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሲፕራስና የፑቲን ንግግር

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 1 2007

በሩስያ የሁለት ቀናት ጉብኝት ያደረጉት የግሪኩ ጠቅላይ ሚኒስትር አሌክሲስ ሲፕራስ የገንዘብ እርዳታ ጥያቄ አለማቅረባቸውን ሩስያ አስታወቃለች ። የሩስያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን እንዳሉት ከሲፕራስ ጋር ዋነኛ የኃይል ምንጮችን ጨምሮ በተለያዩ የኤኮኖሚ ዘርፎች ስለሚደረጉ ትብብሮች እንጂ ስለ ገንዘብ እርዳታ አልተነጋገሩም ።

https://p.dw.com/p/1F5ZQ
Griechenland Blitz über der Akropolis
ምስል Colourbox

ትናንት ሞስኮ የሄዱት ሲፕራስ በእዳ የተዘፈቀችው የግሪክን ችግር ለማቃለል የሩስያን የገንዘብ ድጋፍ ለመጠየቅ ሳያስቡ አይቀርም የሚል ግምት በሰፊው ይነገር ነበር ።

የግሪኩ ጠቅላይ ሚኒስትር የአሌክሲስ ሲፕራስ የሩስያ ጉብኝት የብዙዎችን ትኩረት የሳበና ብዙ መላ ምቶችንም ያሰነዘረ ነበር ። ግምቶቹ ይበልጥ እንዲሰፉ ያደረገውም የብድርና ና እዳ አከፋፈልና አወሳሰድ ላይ ከዓለም ዓቀፍ አበዳሪዎችና ከአውሮፓ ህብረት ጋር አንድ እልባት ላይ መድረስ የተሳናት የግሪክ መሪ ሲፕራስ ጉዳዩ መፍትሄ ሳያገኝ ከአውሮፓ ህብረት ጋር ሆድና ጀርባ ወደ ሆነችው ።

ወደ ሩስያ መሄዳቸው ነው ። የጉዞአቸው ዓላማ ለሃገሪቱ የገንዘብ ቀውስ መፍትሄ የሚሆን መላ ከሩስያም በኩል ማፈላለግ ሊሆን ይችላል የሚለው ከሁሉም ጎልቶ የወጣው ግምት ነበር ። ሆኖም ሲፕራስ ም ሆነ አስተናጋጃቸው የሩስያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ይህ ጉዳይ በትናንቱ ውይይታቸው አለመነሳቱን ነው ያሳወቁት ።ትናንት በክሬምሊን ቤተ መንግሥት በበጋራ በሰጡት መግለጫ ላይ ሲፕራስ ግሪክ በየሃገሮች እየዞረች የኤኮኖሚ ችግሬን አቃሉልልኝ ብላ የምትጠይቅ ለማኝ አይደለችም ሲሉ ነበር በኃይለ ቃል የተናገሩት ።ሲፕራስ ችግሩ የግሪክ ብቻ ሳይሆን የአውሮፓውያንም ቀውስ መሆኑን አስታውቀዋል ። ፑቲንም ሲፕራስ የገንዘብ እርዳታ ፍለጋ አለመምጣታቸውን አረጋግጠዋል ። አንዳንድ የአውሮፓ ፖለቲከኞች አስተያየታቸውን እንደሰጡት የሲፕራስ የሞስኮ ጉብኝት ከመጠን በላይ እንዲጋነን ተደርጓል ። የጀርመኑ የክርስቲያን ዲሞክራት ፓርቲ የኤኮኖሚ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ኩርት ላውክ ይህን ከሚሉት አንዱ ናቸው ።

Russland Griechenland Tsipras bei Putin
ምስል picture-alliance/dpa/Zemlianichenko

«የሚስተር ሲፕራስ የሞስኮ ጉብኝት እንደሚመስለኝ በጣም የተጋነነ ግምት ነው የተሰጠው ። ይህ የመተዋወቂያ ጉብኝት ነው ።እናም ሩስያም አሁን በምትገኝበት አስቸጋሪ ሁኔታ ግሪክን በገንዘብ ትረዳለች ተብሎ የሚጠበቅ አይደለም ።»

ይሁንና በዚህ ጉብኝት ሲፕራስ በዩክሬን ጦርነት ምክንያት የአውሮፓ ህብረት ለጣለበት ማዕቀብ ሩስያ በወሰደችው የአፀፋ እርምጃ ምክንያት የተጎዳው የግሪክ የፍራፍሬ የውጭ ንግድ እንዲያንሰራራ ሩስያ እገዳውን እንድታላላ መጠየቃቸው አልቀረም ። የሩስያ የኤኮኖሚ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት እንዳስታወቀው የአፀፋውን እገዳ ለማርገብ የሚያስችሉ ሃሳቦችን ለግሪክና ለሩስያ ባለሥልጣናት ውይይት አቅርቦ ነበር ።ሲፕራስ ዛሬ እንደተናገሩት በጎርጎሮሳዊው 2014 ዓም ሩስያ ያገደችው የግሪክ የእርሻ ምርት ወደ ሩስያ ሊገባ የሚችልበትን መንገድ ፈልገዋል ።ከዚህ ሌላ ፑቲን ሞስኮ ከግሪክ ጋር በጋራ ለሚሰሩ ፕሮጀክቶች ማካሄጃ የሚውል ብድር እንደምትሰጥም ተናግረዋል ። ብድሩ ከታሰበላቸው ፕሮጀክቶች መካከል በቱርክ በኩል ከሩስያ ወደ አውሮፓ እንዲዘረጋ የታቀደው የጋዝ ማስተላለፊያ መስመር ስራ ይገኝበታል ። ሲፕራስ እንዳሉት ሁለቱ ሃገራት የሩስያን የጋዝ ማስተላለፊያ መስመር ወደ ግሪክም መዘርጋት የሚቻልበትን አማራጭ ለመፈለግ ተስማምተዋል ።እነዚህና ሌሎችም ግሪክና ሩስያ የደረሱባቸው የንግድ ስምምነቶች የረዥም ጊዜ እቅዶች በመሆናቸው የአሁኑን የሃገሪቱን የገንዘብ ችግር ሊፈቱ አይችሉም ። ሆኖም ለዶቼቬለ አስተያየታቸውን የሰጡ አንድ ግሪካዊ ይህን አጋጣሚ ተጠቅሞ ግንኙነቱን ማስፋቱ ጥቅም እንጂ ጉዳት የለውም ብለዋል ።

Symbolbild Hilfe für Griechenland
ምስል picture-alliance/dpa/Ohlenschläger

«በሃገሮች መካከል የሚደረጉ ግንኙነቶች ጠቃሚ ናቸው ።የንግድ ግንኑነቶችን የሚያጠናክሩና ለኤኮኖሚ እድገት የሚበጁ እስከሆኑ ድረስ እነዚህ እድሎች መጠቀም አለብን ።»

ይህ በእንዲህ እንዳለ የግሪክ መንግሥት እንዳስታወቀው ግሪክ ለዓለም የገንዘብ ድርጅት IMF በተቀመጠላት የጊዜ ገደብ ከእዳዋ የ450 ሚሊዮን ዩሮውን ወቅታዊ ክፍያ የመፈፀም ግዴታዋን ዛሬ ተወጣለች ። ያም ሆኖ ግሪክ ወደፊት የሚያስፈልጋትን ገንዘብ ከአበዳሪዎች ለማግኘት ግዴታ የገባችባቸውን የተሃድሶ እርምጃዎች ተግባራዊ እንድታደርግ አሁንም ግፊት እየተደረገባት ነው ።

ኂሩት መለሰ

ነጋሽ መሀመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ