የሲፒጄይና የአፍሪቃ የመ/ብዙሃን ድጋፍ ሰጭ ድርጅት ጥሪ
ሐሙስ፣ ሰኔ 7 2004
በኢትዮጰያ የፀረ ሽብር ህግ ተከሰው የታሰሩት ጋዜጠኞች እንዲለቀቁ ለጋዜጠኞች መብትና ለመገናኛ ዘዴዎች ነፃነት የሚታገሉ ሁለት ድርጅቶች ጠየቁ ። ዓለም ዓቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት በእንግሊዘኛው ምህፃር CPJ ና በአፍሪቃ ለግልና ለነፃ ሚድያ ባለቤቶች እገዛ የሚያደርገው Africa Media initiative የተባለው ተቋም በጋራ ባወጡት መግለጫ የኢትዮጵያ መንግሥት ጋዜጠኞችን እንዲፈታ ጠይቀዋል ። የየፀረ ሽብር ህግ ደግሞ የንግግር ነፃነትን የሚቃረን በመሆኑ እንዲሻሻል ጥሪ አቅርበዋል ። የሁለቱ ድርጅቶች ባለሥልጣናት አዲስ አበባ ሄደው ጉዳዩን ላነጋገሯቸው የኢትዮጵያ የኮምኒክሽን ሚኒስትር ማንሳታቸውንም አስታውቀዋል ። ስለዚሁ የኢትዮጵያ ጉብኝታቸው የCPJ ምክትል ሃላፊ ን አነጋግሬያቸዋለሁ ።
ባለፈው ሳምንት አርብ አዲስ አባባ ውስጥ ከኢትዮጵያ የኮሚኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር አቶ በረከት ስምዖን ጋር የተነጋገሩት የ CPJ የቦርድ አባል ቻርሌይን ሃንተር ጋውልት የCPJ ምክትል ሃላፊ ሮበርት ማሆኒና የ Africa Media initiative የቦርድ አባል ዴሌ ኦሎጄ ናቸው ። የCPJ ምክትል ሃላፊ ሮበርት ማሆኒ አዲስ አበባ ውስጥ የተካሄደው ውይይት ዓላማ የሁለቱን ድርጅቶች ስጋት ማሳወቅ እንደነበረ ለዶቼቬለ ተናግረዋል
« የውይይቱ ዓላማ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በመገናኘት በኢትዮጵያ የጋዜጠኞች መታሰር እንዲሁም የፀረ ሽብርን ህግ ጋዜጠኞችን ለማሰር መጠቀም ያሳደረብንን ስጋት መግለፅ ነበር ። እናም የኢትዮጵያ መንግሥት በአሁኑ ሰዓት የታሰሩትን ጋዜጠኞች እንዲፈታና የንግግር ነፃነትን የሚጎዳውን የፀረ ሽብር ህግ አጠቃቀም እንደገና እንዲያጤነው ጥሪ አቅርበናል ።»
በ CPJ መግለጫ መሠረት ኢትዮጵያ ውስጥ 7 ጋዜጠኞች ታስረዋል ። ኢትዮጵያ በአፍሪቃ ጋዜጠኞችን በማሰር ከኤርትራ ቀጥሎ 2 ተኛነቱን ደረጃ እንደምትይዝ ድርጅቱ በመግለጫው አመልክቷል ። በእስር ላይ ከሚገኙት ጋዜጠኞችም 3 ት ኢትዮጵያውንና 2 ስዊድናውያን ጋዜጠኞች በፀረ ሽብር ህግ ተከሰው መታሰራችውንም ድርጅቱ አስታውቋል ።
የCPJ ና የ Africa Media initiative ሃላፊዎች በአዲስ አበባ ቆይታቸው የጋዜጠኞች መታሰር ያሳደረባቸውን ስጋትና መሻሻል አለባቸው ያሉትን ሲያቀርቡ ከመንግስት በኩል የተሰጣቸው መልስ ግን ከዚህ ቀደም ከሚያውቁት የተለየ እንዳልነበረ ነው ማሆኒ የተናገሩት ።
« ከሚኒስትር በረከት ጋር ከ2 ሰዓት በላይ የወሰደ ውይይት አካሂደናል ። ባለሥልጣኑ መንግሥት ከዚህ ቀደም ያለውን ነው የደገሙት ። ጋዜጠኞች የተያዙት በፅሁፎቻቸው ህጉን ጥሰው ሳይሆን በፀረ መንግሥት ሴራ በመካፈልና ከፀጥታ ጋር በተያያዙ አንዳንድ ጥፋቶች መሆኑን ነው የነገሩን »
እንደ ማሆኒ የ የCPJ ና የ Africa Media initiative ሃላፊዎች በአዲስ አበባ ቆይታቸው የታሰሩትን ጋዜጠኞች ለመጎብኘት እንዲፈቀድላቸው የኢትዮጵያ የኮምኒኬሽን ሚኒስትርን ጠይቀው ነበር ። ይሁንና ጋዜጠኞቹን ሳያዩ ነው ከኢትዮጵያ የተመለሱት ።
«የኮምኒኬሽን ሚኒስትሩ ባለሥልጣን ጥያቄአችንን ጉዳዩ ለሚመለከታቸው የእስር ቤት ባለሥልጣናት እንደሚያስተላልፉ ነግረውን ነበር ። ሆኖም ከዚያ በኋላ ከእስር ቤቱ ሃላፊዎችም ሆነ ከኮሚኒኬሽን ሚኒስቴር መስሪያ ቤት የሰማነው ነገር የለም ። በቀጥታ አይቻልም አላሉንም ። ሆኖም እዚያ በቆየንበት ጊዜ ከታሰሩት ጋዜጠኞች አንዳቸውንም መጎብኘት አልቻልንም ። »
ከቡድኑ አንዱ እቅድ ጋዜጠኞችን መጎብኘት ነበርና ባለመሳካቱ ማሆኒ እንዳሉት ቢያዝኑም በቀጥታ መንግሥት ዘንድ በመሄድ ስጋታቸውን በመግለጻቸው ተደስተዋል ። የታሰሩትን ጋዜጠኞች ማየት ያልቻሉት የቡድኑ አባላት ሥራ ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞችን ግን አነጋግረዋል ።በዚሁ ወቅት በመንግሥት ማተሚያ ቤቶች ተረቆ በቀረበ ውል ውስጥ የተካተቱት ለውጦች ጋዜጠኞችን እንደሚያሳስቧቸውም ሰምተዋል ። ልዑካኑ የሰጡትን አስተያየትና የጋዜጠኞቹንም ስጋት መንግሥት በጥሞና ያጤነዋል የሚል ተሳፋ እንዳላቸው ማሆኒ አስረድተዋል ።
«የታሰሩትን ጋዜጠኞች ጉዳይ እንደገና ፈትሸው ይለቋቸዋል ብዮ ለማሰብ እፈልጋለሁ ። ማናቸውም ጋዜጠኛ ባቀረበው ወይም ባቀረበችው ፅሁፍ ምክንያት መታሰር የለባቸውም ። የኢትዮጵያ የግል ጋዜጦች ስጋቶች በመንግሥት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እንዲታይ እፈልጋለሁ ይህን መልዕክት ለመንግሥት አስተላልፈናል ። እኛ ከሰጠነው አስተያየት ጋር የሚጣጣም ቀና እርምጃ ይወስዳል ብለን ተስፋ እናደርጋለን ኳሷ ሜዳ ነው ያለችው ። »
ሂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ