1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሞቃዲሾ የፀጥታ ችግር

ረቡዕ፣ የካቲት 7 1999

የሶማሊያ ወታደር በመቅዲሾ ጎዳና

https://p.dw.com/p/E0Yi
ምስል AP

በሶማሊያ ዋና ከተማ ሞቃዲሾ ያልታወቁ ታጣቂዎች የሚያደርሱት ጥቃት እንደደቀጠለ ነው ። በዚሁ ጥቃት መንስኤም ባለፉት ሁለት ሳምንታት ብቻ ሀያ አምስት ሰዎች ተገድለዋል ። የመዲናይቱ የፀጥታ ሁኔታ ከቀድሞው ወደ ባሰ ደረጃ እየተሸጋገረ በመሄዱም ነዋሪዎች ከተማይቱን ለቀው መሸሽ ከጀመሩ ቀናት ተቆጥረዋል ። ሸበሌ ኔት የተባለው ድረ ገፅ እንደዘገበው በኢትዮጵያ መንግስት በሚደገፉት የሶማሊያ ወታደሮችና ባልታወቁት ታጣቂዎች መካከል የሚካሄደውን የአዳፍኔ ና የሞርታር ጥቃት ሰለባ እንዳይሆኑ የሰጉ ነዋሪዎች ወደ ከተማይቱ ደቡባዊ ክፍል እየሸሹ ነው ። ማንነታቸው ያልታወቀ የሶማሊያ ታጣቂዎች ሞቃዲሾ ውስጥ የሚያደርሱትን ጥቃት በመቀጠላቸው ሸበሌ ኔት ጸተባለው ድረ ገፅ ዛሬ ባወጣው ዘገባ እንዳመለከተው መዲናይቱን ለቀው የሚሸሹት ነዋሪዎች ቁጥር እየተበራከተ ነው ። መርካ የወደብ ከተማ ስትሆን ከዋና ከተማይቱ ከመቅዲሾ አንድ መቶ ኪሎ ሜት ርቀት ላይ ነው የምትገኘው ። አስር ያህል የሚሆኑ ቤተሰቦች ወደዚህች ከተማ ሸሽተዋል ። እነዚሁ የመቅዲሾ ነዋሪዎች እንደተናገሩት ባልታወቁ ታጣቂዎችና በሶማሊያ ኀይሎች መካከል በሚካሄደው የከባድ መሳሪያ ጥቃት ምክንያት እዚያ መቆየት አልቻሉም ። እነዚሁ ሰዎች እንዳሉት የሶማሌያና የኢትዮጵያ ወታደሮች ዒላማ ውስጥ በገቡ ቁጥር በአፀፋው የሞርታር ጥቃት ይፈፅማሉ ። ድረ ገፁ እንዳስነበበው ትናንት ለሊት ምንም ዓይነት የሞርታር ጥቃት አልደረሰም ። ይሁንና ዛሬ በርካታ የመዲናይቱ ነዋሪዎች ከሞቃዲሾ እየወጡ ወደሌሎች ክፍላተ ሀገራት እየሸሹ ነው ። ከተማይቱን እየለቀቁ ከሚወጡት ውስጥ ሴቶችና ህፃናትም ይገኙበታል ። ሰሞኑን እየተባባሰ የመጣው ጥቃት ያፈናቀለው የቀድሞዎቹን ነዋሪዎች ብቻ አይደለም ። ከሌሎች ከተማዎች ወደ ሞቃዲ̎ሾ የተሰደዱትንም ጭምር እንጂ ። ከተለያዩ የሶማሊያ ክልሎች ሸሽተው ሞቃዲሾ ውስጥ በሚገኙት ከስድስት በላይ የሚሆኑ የመጠለያ ሰፈሮች ይኖሩ የነበሩት በመቶዎች የሚቆጠሩ ተፈናቃዮችም የሞርታርና የሮኬት ጥቃቶች ይደርስብናል ከሚል ስጋት ጊዜያዊውን መጠለያቸውን ትተው መውጣት ጀምረዋል ። ደቡብ ሞቃዲሾ ውስጥ የሚገኘው ጂፈር የተባለው አንድ የቀድሞ ሆስፒታል ቅፅር ግቢ አሁን የስደተኞች መጠለያ ነው ። ቅፅር ግቢው የኢትዮጵያ ወታደሮች የጦር ሰፈር ሆኖም ያገለግላል ። በዚህ ግቢ ውስጥ የተጠለሉት ተፈናቃዮች የኢትዮጵያ ወታደሮች የጥቃት ዒላማ ከሆኑ እኛም አጣብቂኝ ውስጥ መግባታችን አይቀርም በሚል ስፍራውን ለቀው እየወጡ ነው ። ይህን ስፍራ ከለቀቁት አንዷ የአምስት ልጆት እናት የሆነችው ፋዱማ አሊ ናት ። እርስዋና ቤተሰቦችዋ ከሞቃዲሾ በስተደቡብ ሁለት መቶ ሀምሳ ኪሎሜትር ርቀት ላይ ወደሚገኘው ወደባይዶዋ ነው የሚሸሹት ። ፋዱሞ እንዳለችው በስደተኞቹ መጠለያ ውስጥ የሰፈሩት የኢትዮጵያ ወታደሮች የጥቃት ዒላማ መሆናቸው አይቀርም ። እናም እንደ ፋዱሞ እነርሱ ተፈናቃዮቹ ማለትዋ ነው በዚሁ ግቢ ስላሉ ከጥቃቱ ሰለባነት አያመልጡም ። ከመሞት መሰንበት ይበጃል ብለው ሞቃዲሾን ለቀው ከሚወጡት ስደተኞች አብዛኛዎቹ በተደጋጋሚ በድርቅ ወደ ተመቱትና እአአ በሺህ ዘጠኝ መቶ ዘጠናዎቹ የሶማሊያ ጦርነት ትተዋቸው ወደ መጡት ደቡባዊ ና ማዕከላዊ ሶማሊያ ነው የሚመለሱት። ይህ በእንዲህ እንዳለ በሶማሊያ ሁሉንም ወገኖች ያሳተፈ ውይይት እንዲካሄድ ምዕራባውያን መንግስታት በሶማሊያ መንግስት ላይ ግፊት እያደረጉ ነው ። ምዕራባውያኑ በውይይቱ መለትም በዕርቀ ጉባኤው መካፈላቸው ወሳን ነው የሚሏቸው ለዘብተና የተባሉት የፍርድ ቤቶቹ ህብረት መሪ ሼክ ሸሪፍ ሼክ አህመድ ናቸው የሶማሊያ የሽግግር መንግስት ጠቅላይ ሚኒስትር አሊ ሞሀመድ ጌዲ ግን ከኬንያ ጥበቃ ወጥተው ወደ የመን ከገቡት ከሼክ ሸሪፍ አህመድ ጋር እስካሁን ምንም ዓይነት ውይይት አለመደረጉን ነው የገለፁት ።