የመተከልዋ የቡለን ወጣቶች መልካም ተግባር
ዓርብ፣ መስከረም 9 2012ጌታቸው ደሳለኝ እና ገዛኸን ሻምበል ይባላሉ።በቤንሻንጉል ጉምዝ መተከል ዞን የምትገኘው የቡለን ወረዳ ነዋሪዎች ናቸው። « እየዞርን አረጋውያንን እናያለን ፣ ቤት የፈረሰባቸው ካለ በወጣቶች ጉልበት ቤት እንሰራለን። ሌሎች የቁሳቁስ እና የአልባሳትን ድጋፍም እናደርጋለን። ይላል በንግድ ስራ የሚተዳደረው ገዛኸኝ። ይህ የበጎ አድራጎት ስራቸው በጣም ስላስደሰታቸው ወጣቶቹ ተሰባስበው ሰሞኑን «የቡለን ወጣቶች በጎ አድራጎት ማህበርን» ለመመስረት እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ጌታቸው ይናገራል። ጌታቸው የባዮሎጂ መምህር ሲሆን በምስረታ ላይ የሚገኘው ማህበር ምክትል ሊቀመንበርም ሆኖ ተመርጧል። « ሁላችንም በዛ ደስተኛ ሆንና ለምን ማህበር አንመስርትም እና የተሻለ ፕሮጀክት እየቀረፅን በተሻለ መንገድ አንረዳም ብለን ወሰንን።»
ወጣቶቹ ከግል ኪሳቸው በሚያወጡት ገንዘብ ሰዎችን እንደሚረዱ ነግረውናል። ይህ ገንዘብ ግን ጌታቸው እንደሚለው በቂ አይደለም። ደጀኔ ማሞ በሳውዲ አረቢያ የሚኖሩ እና ወጣቶቹን የሚተባበሩ ጎልማሳ ናቸው። « የአካባቢው ተወላጅ ስለሆንኩ ያለውን ነገር በቅርብ እከታተላለሁ። እኔ እነሱ የጀመሩትን ስራ ነው የማበረታታው። በሳውዲ ዓረቢያ የሚኖሩት ጎልማሳ የቡለን በጎ አድራጊ ወጣቶቹን «የሰላም አምባሳደሮች» ሲሉም ይገልጹዋቸዋል።
ቤት ከተሰራላቸው ሰዎች አንዷ እናት ገኒ ናቸው።ወይዘሮዋ ባለፈው ዓመት በወጣቶቹ ትብብር ከተጎሳቆለ የሳር ቤት ወደ ቆርቆሮ ቤት መዘዋወራቸውን ገልፀውልናል። « ትንሹም ትልቁም ተባበሩኝ። በሁለት ሳምንት ውስጥ ክንውንው አድርገውከደረቅ ቤት » በማለት ያመሰግናሉ።የወጣቶቹ ድጋፍ ባይኖር ኖሮ ይህ ለእናት ገኒ ፍፁም የማይታሰብ ነበር።
ወጣቶቹ ማን ምን አይነት ድጋፍ እንደሚያስፈልገውም ሆነ ፣የትኞቹን ሰዎች እንደሚረዱ የሚወስኑት ከሌሎች የመንግስት ተቋማት ጋር እየተማከሩ ነው።ወጣቶቹን የወረዳው አስተዳደርም ያውቃቸዋል። የቡለን ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ፀሀይ ጉዬ ወጣቶቹ እንዴት ከወረዳው ጋር ተቀናጅተው እንደሚሰሩ ለ DW አብራርተዋል። « እነሱ በጉልበት ሲሸፍኑ መንግሥት ደግሞ እነሱ የሚፈልጉትን በተለይ አቅመ ደካሞችን በመለየት፣ በገንዘብ ፣ በጉልበት የሚያስፈልጉ ነገሮችን በጋራ የምንወያይበት መንገድ ነው ያለው።»
አሁን በማህበር ምስረታ ላይ የሚገኙት ወጣቶች ቁጥር አናሳ ቢሆንም በበጎ ፍቃደኝነት ስራው የሚተባበሩት ግን ወደ 60 ይጠጋሉ ይላል ገዛኸኝ። ስራ ሲኖር በስልክ እና በማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ተጠራርተው ይሰባሰባሉ።
የወረዳዋ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ፀሀይ ጉዬ ለ DW እንደገለፁት በአሁን ሰዓት አካባቢው ተረጋግቷል። አዲስ የሚፈናቀሉም ሰዎች የሉም።
ልደት አበበ
ሂሩት መለሰ