1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

    የመምሕራን ቀን፤ የካሜሩን ምሳሌ

ነጋሽ መሐመድ
ሐሙስ፣ መስከረም 26 2009

ቦኮ ሐራም ሰሜናዊ ካሜሩን ዉስጥ ጥቃት ማድረስ ከጀመረ ስድስተኛ ዓመቱ ነዉ።በዚሕ ጊዜ ዉስጥ ቡድኑ የተለያዩ ትምሕርት ቤቶችን አጥቅቷል። የኮሴሬይ አንደኛ ደረጃ ትምሕርት ቤትም አልቀረለትም።

https://p.dw.com/p/2QyRI
Karte Kamerun deutsch

Teachers day- Cameroon - MP3-Stereo

ዓለም አቀፉ የመምሕራን ቀን ትናንት በመላዉ ዓለም ታስቦ ዉሏል።ግጭት፤ ጦርነት፤ እና የአሸባሪዎች ጥቃት ባየለባቸዉ አካባቢዎች ግን ዕለቱ በመምሕራንና በተማሪዎች ላይ የሚደርስ ፈተናን በማሰብ ነዉ የተዘከረዉ።የናጄሪያዉ አሸባሪ ቡድን ቦኮ ሐራም በሚንቀሳቀስና አደጋ በሚጥልባቸዉ የሰሜናዊ ካሜሩን አካባቢ የሚገኙ በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ተማሪዎች ደግሞ ዕለቱን ያለ አስተማሪ ነዉ ያሰቡት።በአካባቢዉ ያስተምሩ የነበሩ አምስት መቶ አስተማሪዎች ቦኮ ሐራም የሚያደርሰዉን ጥቃት ፍራቻ ካካባቢዉ ሸሽተዋል። 

ካሜሩንን ከናጄሪያ ጋር በሚያገናኘዉ የሐገሪቱ ሰሜናዊ ግዛት የሚገኘዉ የኮሴሪይ አንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ናቸዉ።በአካባቢያቸዉ ሥለሚደረግ፤ ሥለሚሆነዉ ምን ያዉቃሉ?ልጆች ናቸዉ።ይዘምራሉ። ብሔራዊ መዝሙር።ከአምስቱ አስተማሪዎቻቸዉ ሰወስቱ ግን የዚሕ ትምሕርት ዘመን ከተጀመረ ጀምሮ የሉም።ምክንያታቸዉ የቦኮ ሐራምን ጥቃት ፍራቻ።ርዕሠ መምሕርት ኩይንታ አሶንግዌ እንደሚሉት ሰወስቱ አስተማሪዎች የመጀመሪያዎቹ አይደሉም።ብዙዎች ሥራ-ቀዬቸዉን ለቅቀዉ ሸሽተዋል።እሳቸዉ ግን አላደርገዉም ይላሉ።ምክንያታቸዉ «የሕፃናቱ የወደፊት ዕድል በእኔ እጅ ነዉ።» ይላሉ።በዚያ ላይ ሞያ በፍቅር ጥሏቸዋል።

          

«ማስተማር (ለኔ)ጥበብ ነዉ።አጥንት ዉስጥ ያለ ነገር ነዉ።ልጅ ሆኜ አስተማሪ ተመስዬ መጫወት እዉድ ነበር።ያደግሁት እንደዚያ ነዉ።ኋላም ሕልሜን እዉን ለማድረግ ወሰንኩ።ለአስተማሪዎች ልዩ አድናቆት አለኝ። እናቴም እስካሁን ድረስ የሙአለ ሕፃናት መምሕር ስለሆነች ለሙያዉ ፍቅሬ ለየት ያለ ነዉ።»

Afrika Kamerun - Geschäft an Bahnstation
ምስል picture-alliance/Bildagentur-online/AGF/M. Charles

ቦኮ ሐራም ሰሜናዊ ካሜሩን ዉስጥ ጥቃት ማድረስ ከጀመረ ስድስተኛ ዓመቱ ነዉ።በዚሕ ጊዜ ዉስጥ ቡድኑ የተለያዩ ትምሕርት ቤቶችን አጥቅቷል። የኮሴሬይ አንደኛ ደረጃ ትምሕርት ቤትም አልቀረለትም።መምሕር ንጌዉናግ ቲሞቲ ጥቃቱ የደረሰ ዕለት እዚያ ነበሩ።

 «በጣም ተሸማቀን ነበር።የመጡ ዕለት ከቶሬ ሞኮሎ ድረስ በእግራችን ነበር የተጓዝ ነዉ።አሁን ቶሬ ተመልሰናል።መንግሥትም በትምሕርት ቤታችን ላይ ዳግም አደጋ እንዳይጣል እና ሥራችን እንዳይስተጓጎል ጠንካራ እርምጃ የወሰደ መስሎኛል።»

ይሁንና ቦኮ ሐራም ያደርሰዋል ተብሎ የሚፈራዉን ጥቃትና ሥጋት ለመቋቋም ሁሉም አስተማሪ አልቆረጠም።ባያማክ አሊያ ወደሚያስተምሩበት ትምሕርት ቤት ለመመለስ ፈቃደኛ አይደሉም።መንግስት ግጭት ባለባቸዉ አካባቢዎች ለሚሰሩ ሰዎች የሚሰጠዉን አበል መጨመር አለበት ባይ ናቸዉ።«አስተማሪዎች ብዙ ቅሬታዎች እያቀረቡ፤ ቀጣሪዎቻቸዉ ለግማሹ እንኳን መልስ ሳይሰጡ ያስተምሩ ማለት አይቻልም።ካሜሩን ዉስጥ ላለፉት 16 ዓመታት የክፍያና የሥራ-ሁኔታዉ ያልተሻሻለለት የመንግስት ሠራተኛ ቢኖር አስተማሪ ብቻ ነዉ።ይሕ አበረታች አይደለም።እንዲያዉም ያርቃል እንጂ።»

መምሕራኑ አቤት ቢሉም የሐገሪቱ መምሕራን ማሕበር ሳይቀር ወደ ሥራ ገበታቸዉ እንዲመለሱ እያሳሰበ ነዉ።የማሕበሩ ባለሥልጣናት እንደሚሉት አስተማሪዎቹ ቅድሚያ መስጠት ያለባቸዉ ለተማሪዎቻቸዉ እንጂ ለራሳቸዉ አይደለም።

Kamerun Flüchtlingslager Minawao
ምስል AFP/Getty Images/R. Kaze

ሰሜናዊ ካሜሩን የሸመቀዉን የቦኮ ሐራም አሸባሪ ቡድን የሚወጋዉ የሐገሪቱ ጦር አዛዥ ጄኔራል ያቆብ ኮድጂ በበኩላቸዉ መምሕራኑም ሆኑ የአካባቢዉ ማሕበረሰብ ከጦሩ ጋር እንዲተባበሩ ጠይቀዋል።በርካታ መምሕራን ግን የማሕበራቸዉን ጥሪ፤ የጦሩን ጥያቄም ሆነ የተወሰኑ ባልደረቦቻቸዉን አቋም አልተቀበሉትም። እስካሁን ድረስ በአካባቢዉ ከሚያስትምሩ ከአምስት መቶ የሚበልጡ መምሕራን ለሕይወታቸዉ በመስጋት ስራቸዉን ለቀዋል።

ነጋሽ መሐመድ

አዜብ ታደሰ