1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሐረር ነዋሪዎች የተቀሙ ቤቶቻቸው ቢመለሱላቸውም ሥጋት አለብን አሉ

ማክሰኞ፣ ግንቦት 13 2011

በሐረር ቤቶቻቸውን የተቀሙ ዜጎች ቢመለሱላቸውም በዚያው ለመኖር ሥጋት እንደተጫናቸው አስታወቁ። የሐረርን የመኖሪያ ቤት እጥረት ለመቅረፍ ከተገነቡት የጋራ መኖሪያ ቤቶች ውስጥ 135 ያህሉ "ሕገ-ወጥ" በተባሉ ሰዎች በኃይል የተወሰዱት ከወራት በፊት ነበር። የመኖሪያ ቤቶቹ ለባለቤቶቻቸው መመለሳቸውን የሐረሪ ክልል የቤቶች ልማት ፅህፈት ቤት አረጋግጧል

https://p.dw.com/p/3IqSq
Straßenszene in Harar, Äthiopien
ምስል Z. Abubeker/AFP/Getty Images

የሐረር ነዋሪዎች የተቀሙ ቤቶቻቸው ቢመለሱላቸውም ሥጋት አለብን አሉ

በሀገሪቱ ለለውጥ የተደረገውን ጥረት ተከትሎ የመጣው ውጤትበአብዛኞቹ አካባቢዎች ያስከተለው ስርዓት አልበኝነት መገለጫ የሆኑ ድርጊቶች በሀረሪ ክልል በስፋት ተስተውለዋል። ከእነዚህ ድርጊቶች መካከል የኮንዶሚንየም፣ የቀበሌ እና የግል ቤቶች ጭምር ህገወጥ በተባሉ ሰዎች መያዝ ይገኝበታል። በሀረሪ ክልል ከአንድ አመት ቀደም ባለው ጊዜ በክልሉ የመኖርያ ቤት ችግርን ለመቅረፍ ተሰርተውና ለባለቤቶች ተላልፈው ከነበሩ የጋራ መኖርያ ቤቶች (ኮንዶሚንየም) ውስጥ 135 ያህሉ በህገወጦች ተወስደዋል።  
የሀረሪ ክልል ፍትህ ቢሮ ሰሞኑን ገለፀ በተባለው መረጃ መሰረት ቤቶቹን ማንነታቸው በውል ካልተገለፁ አካላት በመውሰድ ለባለቤቶች እንዲሰጥ ተደርጓል። የክልሉ ቤቶች ልማት ፅህፈት ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ ኢሊ አብዱረሂም  135 ያህል ቤቶችን በህገወጥ ይዘው ከነበሩ አካላት በመረከብ ለባለቤቶች እንዲሰጥ መደረጉን ለዶይቼ ቬሌ (DW) አረጋግጠዋል።
የመኖሪያ ቤቶቹ ባለቤት ከሆኑ ግለሰቦች አንዷ የሆኑት ወ/ሮ ሀያት ቤታቸውን ለመረከብ ሄደው ከህገወጦቹ መለቀቃቸውን መመልከታቸውን ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ በሄዱበት ወቅት ካለቀቁ ሰዎች ተቃውሞ እንደገጠማቸው ገልጸዋል። እርሳቸው አንደሚሉት አሁንም ሁኔታው ጥሩ ክትትል ይፈልጋል። 
ከመኖሪያ ቤቶቹ ባለቤት አንዱ የሆኑት አቶ ጀምበሬ ኃይለ ማርያም በበኩላቸው ቤቶቹን ከህገወጦች በማስለቀቅ እንዲረከቡ ቢደረግም ቤቶቹን ለመኖሪያ ምቹ ለማድረግ መጠገን ይኖርባቸዋል። አሁንም ተመሳሳይ ችግር እንዳይፈጠር ያላቸውንም ስጋት ገልጸዋል። "በፍጥነት ወደ ቤቶቹ እንድንገባ መገለፁ ሌላ ፈተና እና ስጋት ነው" ብለዋል። 
የክልሉ ቤቶች ልማት ፅህፈት ቤት ስራ አስኪያጅ በነዋሪው የተነሳውን ስጋት በሚመለከት ምላሽ ሰጥተዋል። በሀረሪ ክልላዊ መስተዳድር በህገወጦች ተወስደው ከነበሩት የጋራ መኖርያ ቤቶች በተጨማሪ የቀበሌ እና ሌሎች የግለሰብ መኖርያ ቤቶች ተለቀቅው ለባለቤቶች መሰጠታቸውን የክልሉ ፍትህ ቢሮ ሀላፊ መግለፃቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
መሳይ ተክሉ
ተስፋለም ወልደየስ