1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሊቢያ ፀጥታና ጠቅላይ ሚንስትሯ

ሐሙስ፣ መስከረም 30 2006

አጋቾች ኋላ ላይ እንዳስታወቁት ጠቅላይ ሚንስትሩን ያገቱት፥ ዩናይትድ ስቴትስ በ1990 የናይሮቢና የዳሬ-ሰላም ኤምባሲዎቿን ካጋዩ «አሸባሪዎች አንዱ» ያለችዉን አቡ አነስ አል ሊቢን ባለፈዉ ሳምንት ከሊቢያ አፍና ስትወስድ ጠቅላይ ሚንስትሩ ተባብረዋል በሚል ለመበቀል ነዉ።

https://p.dw.com/p/19xfc
Libyan security gather in the capital Tripoli on September 21, 2013, as they prepare to secure neighborhoods and the headquarters of government departments following a decision by the National Congress to clamp down on crime and criminal groups around the capital. AFP PHOTO/MAHMUD TURKIA (Photo credit should read MAHMUD TURKIA/AFP/Getty Images)
ሚሊሻዎች እንደ አሸን ፈልተዋልምስል M.Turkia/AFP/GettyImages


የሊቢያዉ ጠቅላይ ሚንስትር አሊ ዚዳን ዛሬ ሲነጋጋ በታጣቂዎች ከታገቱ በሕዋላ ማርፈጃዉ ላይ ጉዳት ሳይደርስባቸዉ ተለቅቀዋል።የሊቢያ ባለሥልጣናት እንዳስታወቁት ጠቅላይ ሚንስትሩን ያገቱት የሊቢያ አብዮታዊ ኮሚቴ የተሰኘዉ የቀድሞ አማፂ ቡድን ታጣቂዎች ሲሆኑ፥ ያስለቀቋቸዉ ደግሞ የሌላ ታጣቂ ሐይል ባልደረቦች ናቸዉ።ጠቅላይ ሚንስትር ዚዳን ለሥድስት ሰዓት ያሕል ከታገቱ በሕዋላ ምንም ጉዳት ሳይደርስባቸዉ ቢለቀቁም የማገቱ እርምጃ ብዙዎችን ያስነደቀ፥ አነጋጋሪም ነዉ። በነዳጅ ዘይት የበለፀገችዉን ሰሜን አፍሪቃዊት ሐገር ፀጥታም ብዙ እያሳሰበ ነዉ።ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።


መፈንቅለ-መንግሥት ለአፍሪቃም፥ ለአረበብም እንግዳ እንዳይደለ፥ከአፍሪቃዊቷ፥ አረባዊቷ ሊቢያ በላይ እማኝ በርግጥ የለም።የመሪዎች መገደል፥ ለአፍሪቃም፥ ለአረብም አዲስ እንዳልሆነም ከሊቢያ የተሻለ የቅርብ ጊዜ-ምሳሌ አይገኝም።ከትልቅ ከተማ፥ ምናልባት በጥብቅ ከሚጠበቅ ትልቅ ሆቴል ትልቅ መሪ ሲታገት ግን ጀርመናዊዉ የፖለቲካ አጥኚ ጊዶ ሽታይበርግ እንደሚሉት የዛሬዉ የመጀመሪያዉ ሳይሆን አይቀርም።

አፍሪቃ አረብ-ጉድ፥ አጃኢብ ሲል የፖለቲካ ተንታኝ ሽታይንበርግ አስደናቂ አሉት።

«ሁኔታዉ በርግጥ አስደናቂ ነዉ።በአካባቢዉ ጠቅላይ ሚንስትር የታገተበትን ጊዜ አላስታዉስም። (በመሪዎች ላይ) የግድያ ጥቃት ተሰንዝሮ ያዉቃል።አንድ ሁለት መሪዎች ተገድለዉም ነበር። በሥልጣን ላይ ያለ ጠቅላይ ሚንስትር ከትልቅ ሆቴል፥ ያዉም ርዕሠ-ከተማይቱ ዉስጥ ከሚገኝ ያን እሚያሕል ሆቴል፥ በቂ ጥበቃ ሳይደረግላቸዉ መታገታቸዉ፥ ለማመን ፍፁም የሚከብድ ነዉ።»

ግን ሆነ።የ63 ዓመቱ ጠቅላይ ሚንስትር ዓሊ ዚዳን በርግጥ የተደገሰላቸዉን አያዉቁም። ኮሪንታል ከተሰኘዉ ግዙፍ፥ ምቹ ሆቴል ምናልባት ጭልጥ ያለ እንቅልፍ ላይ-ይሆኑ ይሆናል።ጎሕ መቅደዱ ነዉ።ዚዳን፥ የሙዓመር ቃዛፊን አገዛዝ በመቃወም እንደ ዲፕሎማት፥ እንደ ሰብአዊ መብት ጠበቃ፥ ከጄኔቭ ብራስልስ በሚመላሱበት ወቅት ፈረንሳይ፥ ብሪታንያና ዩናይትድ ስቴትስ በመሩና ባስተባበሩት ዓለም እየተረዱ የጋዛፊን ጦር የወጉት አማፂያን አንድ መቶ ሐምሳ መኪኖች እያርመሰመሱ ከትልቁ ሆቴል ደረሱ።ጊዜ አላጠፉም።የጎደለዉን የኮሪታል ሆቴል ሥራ አስኪያጅ አብድል አል-ረዛቅ፥ ሞሉት።

«ሰዎቹ ከጠቅላይ አቃቤ ሕግ ተሰጠን ያሉትን ወረቅት ይዘዉ መጡ።ጠቅላይ ሚንስትሩን የማሠሪያ ትዕዛዝ ይዘዉ ነበር።አማፂዎች ናቸዉ።መጡ ጠቅላይ ሚንስትሩን ያዙ ሔዱ።»

አመፂያኑ ከሆቴሉ ከመሔዳቸዉ በፊት ያጎሳቆሏቸዉን ጠቅላይ ሚንስትር መንፅራቸዉ እንደወለቀ፥ ሸሚዛቸዉ ሳይቆለፍ፥ ፂማቸዉ ሳይላጭ ከቴሌቪዥን ካሜራ ፊት ገተሯቸዉ።ጠቅላይ ሚንስትሩን ያገተዉ የሊቢያ አብዮታዊ ኮሚቴ የተሰኘዉ የሚሊሺያዎች ቡድን እንደ ብዙዎቹ የሚሊሺያ ሐይላት ሁሉ ከሊቢያ መንግሥት ካዝና በጀት የሚቆረጥለት፥ከሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስቴር ጋር በቅርብ ተባብሮ የሚሠራ ነዉ።

ጠቅላይ ሚንስትሩ የተያዙት በሙስና ሥለሚፈለጉ ከሐገሪቱ ጠቅላይ አቃቤ-ሕግ በተሰጠ ትዕዛዝ ነዉ-የሚለዉን መግለጫ ግን የርዕሠ-ከተማ ትሪፖሊ የፀጥታ አስከባሪ አዛዥ ሐሺም በሽር አስተባብለዋል።

«ለዓቃቤ ሕጉ ስልክ ደውዬ ነበር፣ በአሊ ዜይዳ ላይ የእሥር ማዘዣ አለማውጣታቸውን በመግለፅ ዜናውን አስተባብለዋል። ይህን አድርጌ ቢሆን ኖሮ፣ እኔም ወንጀለኛ ሆኜ ነበር ሲሉ ነበር ቃል በቃል የነገሩኝ። ጠቅላይ ሚንስትሩን ለማሰር ሕጋዊ ርምጃዎች ሊወሰዱ ይግባል።»

አጋቾች ኋላ ላይ እንዳስታወቁት ጠቅላይ ሚንስትሩን ያገቱት፥ ዩናይትድ ስቴትስ በ1990 የናይሮቢና የዳሬ-ሰላም ኤምባሲዎቿን ካጋዩ «አሸባሪዎች አንዱ» ያለችዉን አቡ አነስ አል ሊቢን ባለፈዉ ሳምንት ከሊቢያ አፍና ስትወስድ ጠቅላይ ሚንስትሩ ተባብረዋል በሚል ለመበቀል ነዉ።ሰበብ ምክንያቱ ምንም ሆነ ምን ታዛቢዎች እንደሚሉት የቀድሞዉ የሊቢያ አምባገገን ገዢ ኮሎኔል ሙዓመር ቃዛፊ ከተገደሉ ወዲሕ ሊቢያ ማንም ታጣቂ በፈለገበት ጊዜ ያሻዉን የሚያደርግባት የሥርዓተ-አልበኞች ሐገር መሆናን መስካሪ ነዉ።

Libyan Prime Minister Ali Zeidan speaks during a press conference in the capital Tripoli on July 29, 2013. Zeidan said he would carry out a reshuffle of his government in the coming days, a move aimed at ending the country's current political crisis. AFP PHOTO/MAHMUD TURKIA (Photo credit should read MAHMUD TURKIA/AFP/Getty Images)
ምስል MAHMUD TURKIA/AFP/Getty Images
Libya's Prime Minister Ali Zeidan places his hand on his forehead as he addresses a news conference after his release and arrival at the headquarters of the Prime Minister's Office in Tripoli October 10, 2013. Zeidan was seized and held for several hours on Thursday by former rebel militiamen angry at the weekend capture by U.S. special forces of a Libyan al Qaeda suspect in Tripoli. REUTERS/Ismail Zitouny (LIBYA - Tags: POLITICS CIVIL UNREST TPX IMAGES OF THE DAY)
ጠ.ሚ ዓሊ ዚይዳንምስል Reuters

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ






ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ