1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሃይድሮጂን ባትሪ ለተሽከርካሪዎች

ረቡዕ፣ ሐምሌ 11 2004

በጀርመን ሀገር በተለያዩ የምርምር ተቋማት የሚገኙ ተመራማሪዎች፣ ለዘመኑ ችግር ዘመናዊ መፍትኄ ለማግኘት መላ ከመሻት የቦዘኑበት ጊዜ የለም። ጀርመን ውስጥ በሰሜናዊው ምሥራቅ የአገሪቱ ከፊል፣ በተለይም በሮሽቶክ ከተማ፣ የሳይንስና ሥነ-ቴክኒክ ተመራማሪዎች፣ የዓለምን

https://p.dw.com/p/15Zq2
ምስል picture alliance / dpa

ህዝብ ከሚያሳስቡት ችግሮች መካከል ፣ በተለይ የኃይል ምንጭን ችግር ለመፍታት ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ። ታዲያ ተመራማሪዎቹ፣ ወሳኝነት ያለው መፍትኄ ፣ ሃይድሮጂን እንጂ ሌላው አይታሰብም ባዮች ናቸው።

Brennstoffzelle
ምስል BMU / Rupert Oberhäuser

የሮሽቶክ የሥነ ቅመማ ጠበብት፣ አሁን፤ አንድ እመርታ ወደፊት ሳይጓዙ አልቀሩም። እነዚሁ ሊቃውንት፣ በሎዛን ፣ እስዊትስዘርላንድ፣ ከሚገኙ ሌሎች፣ ባልደረቦቻቸው ጋር በመተባበር የ«ሃይድሮጅን -ፎርሚክ አሲድ» ወይም «ሃይድሮጂን-ሜታኖይክ አሲድ» ባትሪ ሠርተዋል። ይህ ባትሪ እንደማንኛውም የአውቶሞቢል ባትሪ አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን፣ ልዩነቱ የላይብኒትዝ ተቋም የሥነ ቅመማ ጉዳዮች ኀላፊ ማትያስ ቤለር እንደሚሉት፣ መደበኛው በኤሌክትሮን የሚሞላ ሲሆን፣ ይኸኛው ሃድሮጂን የሚጠቀጠቅበት መሆኑ ነው። ለመጀመሪያም ጊዜ፣ ሃይድሮጂን እየሞሉም ሆነ እየጫኑ በአንድ ዝግ የማብላሊያ ጋን ፣ ደጋጋሞ ያንኑ ተመሳሳይ ድርጊት ማከናወን እንደሚቻል በተጋባር መታየቱ ተመሥክሯል ነው የተባለው። እርግጥ ይህ ሁሉ ሙከራ፤ የተሣካም ድርጊት የተከናወነው በቤተ ሙከራ ውስጥ እንጂ ከዚያ ውጭ አይደለም።

Focus FCV Hybrid Wasserstofftank
ምስል picture-alliance/ dpa/dpaweb

የሥነ ቴክኒክ ግሥጋሴ ሲታሰብ ፤ በአሁኑ ዘመን፤ በተለይ በኃይል ምንጭ ረገድ ላቅ ያለ ግምት የሚሰጠው ፣ ለተፈጥሮ አካባቢ የሚበጀው ዓይነት መሆኑ የሚታበል አይደለም። በአስዊትስዘርላንድና በቤልጅግ ትብብር የተሠራ በፀሐይ ኃይል የሚበር የህዝብ ማመላለሻ አኤሮፕላን ፤ በቅርቡ፣ ለሙከራ ከእስዊትስዘርላንድ እስፓኝ ከዚያም ራባት፣ ሞሮኮ ደርሶ መመለሱ የሚታወስ ነው። እ ጎ አ በ 2014 ፣ በኤሌክትሪክ የሚሠሩ የህዝብ ማመላለሻ አኤሮፕላኖች፣ ከአትላንቲክ ውቅያኖስ ወዲህና ወዲያ ማዶ በሰሜን አሜሪካና በአውሮፓ መካከል በረረራ ከመጀመሩ በፊት፤ ባትሪ ለመሙላት አብራሪ- የለሽ ፣ ንዑሳን አኤሮፕላኖችን (DRONES)እንደ በራሪ ባትሪ ለመጠቀም መታቀዱ ታውቋል።

የምዕተ-ዓመቱ በረራ (Flight of the Century) የተሰኘው ድርጅት መሥራችና ዋናሥራአስኪያጅCHIP YATES ፤ «የረጅም ርቀት በረራን ለማሣካት፣ የግድ በሚሞላ ባትሪ መተማመንም ሆነ ያንኑ መጠበቅ አያሻንም » ይላሉ። እርሳቸው፤ በኤሌክትሪክ የሚሠሩ፣ እጅግ ከፍ ብለውም የሚበሩ ፈጣን አኤሮፕላኖች፣ በፍጥነትም ፣ በከፍታ በረራም፣ በሁለቱም ፣ እ ጎ አ በ 2014 ክብረ ወሰን እንዲይዙ ነው እቅዳቸው። በኤሌክትሪክ የሚሠሩ አኤሮፕላኖች በሥነ ቴክኒክ ረገድ አሁንም በጉጉት የሚጠበቁ ሲሆን፤ ተግባራዊነቱ ሲመረመር ግን፤ የባትሪ መሙያው ሁኔታና የባትሪዎቹ ክብደት እንዳሳሰበ መሆኑ አልታበለም። ታዳሽ የኃይል ምንጭ ፣ እዚህም ላይ የፀሐይ ኃይል፤ በበረራ መካከል የአይሮፕላኑን ባትሪ መሙላት ይችላል፣ ግን ለመለስተኛና ኃይል መቆጠብ ለሚችሉ አኤሮፕላኖች ነው የሚበጀው!የጦር አኤሮፕላኖች በአየር ላይ ነዳጅ፣ የሚሞሉበት ቴክኒክ ተግባራዊ ከሆነ 10 ተ- ዓመታት አልፈዋል።

Wasserstoffauto
Wasserstoffautoምስል AP

ወደፊት በኤልክትሪክ ኃይል ስለሚበሩ አኤሮፕላኖች፤ ካነሳን አይቀር፤ በአኤሮፕላኑ የውስጥ አካል ብቻ ሳይሆን በውጭም እንከን እንዳያጋጥም ፤ ከሆነም አስከፊ ሁኔታ ሳይደርስ አስቀድሞ መጠቆም ስለሚቻልበት ሁኔታ ከአንድ የጀርመን የምርምር ተቋም የተገኘውን የምርምር ውጤት ፤ ከዚህ ቀደም አውስተን ነበረ ፣ እንደገና እናስታውሳችሁ።

ማንኛውንም የሙቀት መጠን የሚቆጣጠሩ ረቂቅ መሣሪያዎች፣ በአኤሮፕላን ዋና አካል፣ በትንሹም ቢሆን፣ የመሰርጎድም ሆነ የመሰንጠቅ አደጋ ሲያጋጥም ወዲያው ወደ አንድ ማዕከላዊ የቁጥጥር ክፍል፣ የራዲዮ መልእክት ማስተላፍ የሚችል መሣሪያ፣ የጀርመኑ Fraunhofer የምርምርተቋምጠበብት ሠርተው በተሣካ ሁኔታ መሞከራቸውን፣ ከ ፍራይቡርግ አስታወቁ። አንዳች የኤሌክትሪክ ኅይል ማስተላለፊያ ሽቦም ሆነ ባትሪ የማያስፈልጋቸውና በአኤሮፕላን አካል የሚጣበቁት እጅግ የረቀቁ መሣሪያዎች፣ ጉልበት የሚያገኙት በአኤሮፕላኑ ውስጥና ውጭ ባለው የሙቀት ልዩነት ነው። በውጭ ከዜሮ በታች ከ 20 እስከ 50 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ሲሆን ቅዝቃዜው፣ በአኤሮፕላን ውስጥ ተሣፋሪዎች በሚቀመጡበት ክፍል ደግሞ ሙቀቱ፣ 20 ዲግሪ መሆኑ የታወቀ ነው።

Flugzeug am Himmel
ምስል Fotolia/dell

የ ፍራውንሆፈር የምርምር ተቋም ባልደረባ የሆኑት ዲርክ ኤብሊንግ እንዳስረዱት፣ በአኤሮፕላን አካል የሚያጋጥም እንከንን የሚጠቁሙት መሣሪያዎች የሚገለገሉት «ማይክሮፔልት » ከተባለው ኩባንያ ጋር በመተባበር በተሠሩ በሙቀት ልዩነት ኃይል በሚያገኙ ጉልበት አመንጪዎች ነው። ሙከራው አመርቂ ቢሆንም፣ በሙቀት ልዩነት የማይቋረጥ ኃይል በማመንጨት በማጠራቀም ፣ እንዲሁም እንከን በመጠቆም፤ አገልግሎት የሚሰጥ የተሟላ ረቂቅ መሣሪያ በተጨባጭ ሁኔታ ጥቅም እንዲሰጥ ገበያ ላይ መዋል የሚችለው በአንድ ዓመት ገደማ ውስጥ እንደሚሆን ነው የተገለጠው። በተጠቀሰው ዘዴ የሚሠሩ ረቂቅ መሣሪያዎች፣ ለበረራ አገልግሎት ብቻ ሳይሆን፣ ለህንጻዎች ግንባታ፣ እንዲሁም ለህክምና አገልግሎት ሰፊ ጠቀሜታ እንደሚኖራቸው ነው የሚታመንበት። ረቂቅ የሆነ፣ ይህን መሰል ተቆጣጣሪ መሣሪያ በአንድ አትሌት ሸሚዝም ተጣብቆ አትሌቱ ልምምድ ሲያደርግ የልብ ትርታውን እንደሚለካ፣ የመስማት ችግር ያለባቸውን ሰዎች የሚረዱ ረቂቅ መሣሪያዎችም ወደፊት ከተጠቃሚው ሰው አካል በሚያገኙት የሙቀት ኃይል ሊሠሩ እንደሚችሉ የሚያጠራጥር አልሆነም።

Deutsches Museum Rheintochter
ምስል DW

ከዚህን በተረፈ፣ ፣ ህዝብ አመላላሽ አኤሮፕላኖች፣ ሞተራቸው በሚቃጠል ቤንዚን መሆኑ ቀርቶ በኤልክትሪክ ኀይል እንዲንቀሳቀስ ማድረጉ ይበልጥ አስተማማኝነት እንዳለው ነው የሚነገረው። በዩናይትድ እስቴትስ የተደረገ ሙከራ እንደሚያረጋግጠው፣ የአኤሮፕላንን ቀዛፊ ሞተር (ፕሮፔለር) ያለሳንክ ለማንቀሳቀስ፣ በነዳጅ ከሚንቀሳቀስ ሞተር ይልቅ፣ የኤሌክትሪክ ሞተር ምናልባት 10 ፣ ብሎም 20 እጥፍ ያህል ይበልጥ አስተማማኝ ነው፣ ነው የተባለው። በኤሌክትሪክ ኃይል የሚንቀሳቀስ ሞተር 95 ከመቶ ያህል እጅግ አስተማማኝ መሆኑ ሲነገርለት፣ ፣ በነዳጅ ኃይል የሚሠራው፣ አስተማማኝነቱ ፣ ከ 18 እስከ 23 ከመቶ መሆኑ ነው የተገለጠው።

ከዚህም ሌላ፣ በኤሌክትሪክ ኃይል የሚበሩ አኤሮፕላኖች የድምፃቸው መጠን እጅግ ዝቅ ያለ በመሆኑ ፣ በአኤሮፕላን ማረፊያ ጣቢያዎች አሠራር ረገድም ለውጥ ሊያስከትል እንደሚችል ነው የሚታሰበው።

ተክሌ የኋላ

ነጋሽ መሐመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ