1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ውይይት፦ የልዩ ፖሊስ ውንጀላዎች እና ውዝግቦች

እሑድ፣ ግንቦት 18 2011

በኢትዮጵያ በተለያዩ ቦታዎች ከሚስተዋሉ ግጭቶች ጋር ስማቸው ተያይዞ ከሚነሳ አካላት መካከል በየክልሎቹ የተደራጀው የልዩ ፖሊስ የጸጥታ መዋቅር ይገኘበታል። የልዩ ፖሊስ አባላት በሰብዓዊ መብት ጥሰት ከመወቀስ ባሻገር በግጭቶች ውስጥ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ይሳተፋሉ የሚል ውንጀላ ይቀርብባቸዋል።

https://p.dw.com/p/3J7sD
Karte von Äthiopien
ምስል DW/E.B. Tekle

ውይይት፦ የልዩ ፖሊስ ውንጀላዎች እና ውዝግቦች

ልዩ ፖሊስ ተብሎ የሚጠራው በክልሎች ያለው የጸጥታ አስከባሪ ኃይል አባላት የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እንደሚፈጽሙ አምንስቲ ኢንተርናሽናልን ጨምሮ በርካታ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ሲገልጹ ቆይተዋል። በተለይ በሶማሌ ክልል በቀድሞ ፕሬዝዳንት አብዲ መሀመድ ኡመር የስልጣን ዘመን የልዩ ፖሊስ አባላት ከፍ ያሉ የሰብዓዊ መብት ወንጀሎች እንደተፈጸሙ ይነገራል።

የሶማሌ ክልል ልዩ ፖሊስ አሁንም ከእነዚህ መሰል ድርጊቶች እንዳልታቀበ የሚጠቅሱ አሉ። ለዚህም በቅርቡ በአፋር እና በሶማሌ ክልሎች አዋሳኝ ቦታዎች የነበሩ ግጭቶችን እና የክልሉን ልዩ ፖሊስ አባላት ተሳትፎ ያነሳሉ። በሌሎች ክልሎች ያሉ የልዩ ፖሊስ አባላትም በተመሳሳይ መልኩ በተወሰኑ ቦታዎች በተነሱ ግጭቶች ላይ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ተሳትፎ ነበራቸው የሚሉ ውንጀላዎች ይደመጣሉ።

ልዩ ፖሊስ አወቃቀሩ ግልፅ አይደለም የሚል ትችት ይቀርብበታል። የጸጥታ ኃይሉ ተጠሪነቱ ለማን ነው የሚለውም እንደዚሁ ያከራክራል።  የልዩ ፖሊስ ከሌሎች የጸጥታ አካላት ጋር ያላቸው ግንኙነት ላይም ጥያቄ የሚያነሱ በርካቶች ናቸው። ይሄው ጥያቄ በቅርቡ በጠቅላይ ሚኒስቴር ጽህፈት ቤት በተካሄደው የአዲስ ወግ የውይይት መድረክ ላይም ተነስቶ ነበር። ለዚህ ጥያቄ ምላሽ የሰጡት የሰላም ሚኒስትሯ ሙፈሪያት ከሚል “በክልሎች እና በፌደራል የጸጥታ አካላት መካከል ያለው ግንኙነት ምን መሆን አለበት የሚለውን ስርዓት የማስያዝ ስራ ጀምረናል” ብለዋል።

እርሳቸውም ሆነ የሶማሌ ክልል ባለስልጣናት የልዩ ፖሊስ  ጉዳይ በኢትዮጵያ እየተተገበረ ነው የሚባለው “ሪፎርም” ስር ተካትቶ ማሻሻያዎች እየተደረጉ እንደሆነ ቢናገሩም  አንድ አካል እንደሆነ የልዩ ፖሊስ አወቃቀር ፈርሶ በመደበኛ ፖሊስ እንዲተካ የሚጠይቁ ወገኖች ግን አሁንም አሉ። እነዚህ እና ሌሎችም ሀሳቦች በተነሱበት የእንወያይ ዝግጅታችን የሶማሌ ክልል ፕሬዝዳንት የሰብዓዊ መብት አማካሪ ላይ አቶ ጀማል ድሪዬ እና በኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ስትራቴጂካዊ ጥናት ኢንስቲትዩት ከፍተኛ ተመራማሪ አቶ አበበ አይነቴ ተወያይተዋል። 


ሙሉ ውይይቱን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ።

ተስፋለም ወልደየስ

ልደት አበበ