1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዉይይት፤ የጠ/ሚ ዐብይና የፕሬዚዳንት ኢሳያስ ወዳጅነት ለኢትዮጵያ ቱሩፋት ወይስ መዘዝ?

ሰኞ፣ ግንቦት 30 2013

«የጠ/ሚ ዐብይና የፕሬዚዳንት ኢሳያስ የወዳጅነት ግንኙነት ቱሩፋት ነዉ። ይሁንና የትግራዩ ጦርነትና፤ ደረሰ የሚባለዉ ኢ-ሰብዓዊ ድርጊቶች የሁለቱን ባለስልጣናት ተጠያቂ ያደርጋል። የምዕራባዉያን ዉትወታ እና የአሜሪካ ማዕቀብ፤ የጎረቤት ሃገራት ሽሽት አንዱ ምክንያትም ነዉ። ኢትዮጵያን በአፍሪቃዉ ቀንድ የነበራትን ቁልፍ ሚናም አሳስቶታል»ተወያዮች

https://p.dw.com/p/3uUp9
Eritrea - Der äthiopische Ministerpräsident Abiy und der eritreischen Staatschef Afewerki
ምስል Reuters/G. Musa Aron Visafric

ዉይይት፤ የጠ/ሚ ዐብይና የፕሬዚዳንት ኢሳያስ ወዳጅነት ለኢትዮጵያ ቱሩፋት ወይስ መዘዝ?

የኢትዮጵያ እና የኤርትራን የ 20 ዓመታት ፍጥጫና ኩርፊያ አስወግደዉ፤ ወዳጅነት የመሰረቱት የጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አሕመድ እና የፕሬዚዳት ኢሳያስ አፈወርቂ ግንኙነት፤ ከወዳህጅነት አልፎ ቤተሰባዊ መሆኑ ተነግሮ ነበር። የሁለቱ መሪዎች ግንኙነት ቤተሰባዊ፤ ይባልለት እንጂ ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ወዳጅነት ግንኙነት በምን መርህ ላይ እንደተመሰረተ በይፋ የተነገረ ነገር የለም። የሁለቱ ሃገራት ግንኙነት መዋቅራዊ አይደለም ሲሉም ዜጎች በተደጋጋሚ ሲወተዉቱ ይሰማል።  ለ20 ዓመታት ሳይገናኝ የነበረዉ የሁለቱ ሃገራት ህዝብ ዳግም መገናኘት ግን በደስታ አስፈንድቆአል።  ጠቅላይ ሚኒስር ዶክተር ዐብይ አሕመድንንም የዓለም የሰላም ሎሬት አስብሎ አሸልሞአል። የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ወዳጅነት መሰረቱ ሳይቋጭ መንግሥት በትግራይ ህወሓት ላይ የጀመረዉ ሕግ ማስከበር ያለዉ ዘመቻ ለወራት መዝለቁ እና የኤርትራ ወታደሮች ድንበር ዘልቀዉ መግባታቸዉ በሃገር ዉስጥ ካሳደረዉ ጫና አልፎ  ኢትዮጵያ ላይ የምዕራቡ ሃገራት ዉትወታ እየበዛ ዉስጥ እንድትገባ ዳርጎታል አል። ዩናይትድ ስቴትስም በሁለቱ ሃገራት ባለስልጣናት እንዲሁም አንዳንድ የኢኮኖሚ ማዕቀብ ኢትዮጵያ ላይ አሳርፋለች። የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ግንኙነት በሃገሪቱም ሆነ በቃጣናዉ ሃገራት በመጥፎም ይሁን በጥሩ ጎኑ ምን አስተዋፅኦ አድርጎአል? ኢትዮጵያ  ሰላም  ብሎም ከቀጠናው ሀገራት ጋር ያላትን ግንኙነት እና ነባር የሆነዉ ቁልፍ ሚናዋ እንዴት ይገመገማል? በዛሬዉ ዉይይታችን የጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐብይ አሕመድ እና የፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ  ወዳጅነት ቱሩፋት ወይስ መዘዝ? ስንል ሃሳብ ተለዋዉጠናል። በዚህ ዉይይት ላይ እንዲሳተፉ የጋበዝናቸዉ፤

ዶክተር ብርሃኑ ሌንጄሶ ፤ የምስራቅ አፍሪቃ የፖሊሲ ጥናት ምክትል ዳይሬክተር እና የብልፅግና ፓርቲ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ዕጩ ተወዳዳሪ

ኢንጂነር ጌታነህ ባልቻ ፤  የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ የፖለቲካ ጉዳዮች የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ዕጩ ተወዳዳሪ

ዶክተር ለማ ይፍራሸዋ ፤  የሕግ እና የፌደራላዊ ሥርዓት ምሁር

ቻላቸዉ ታደሰ ፤ ጋዜጠኛ እና የፖለቲካ ጉዳይ ተንታኝ ናቸዉ።

ወዳጅነቱ በኢትዮጵያ እና ኤርትራ ግንኙነት ላይ ምን ትሩፋት እና ውጤት አስገኘ?

ስምምነቱ ኢትዮጵያ በቀጠናው ባላት ዲፕሎማሲያዊ ሚና ላይ ያስከተለው በጎ ወይም አሉታዊ ተጽዕኖ አለ?

ኢትዮጵያ አሁን በቀጠናው ያላት ዲፕሎማሲያዊ ሚና እና አሁን በቀጠናው ያላት አሰላለፍ ምን ይመስላል?

ሙሉ ዉይይቱን የድምጽ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን እንድትከታተሉ እንጋብዛለን።

የጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ እና የፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ግንኙነት  ምንም እንኳ መዋቅራዊ አይደለም ቢባልም፤ ለሁለቱ ሃገራት ህዝቦች ዳግም መገናኘት ቱሩፋት እንደሆነ ተወያዮች ተናግረዋል። ይሁንና የትግራዩ ጦርነት እና በትግራይ፤ ደረሰ ለሚባለዉ ኢ-ሰብዓዊ ድርጊቶች የሁለቱን ባለስልጣናት ተጠያቂ ያደርጋሉ። ባለስልጣናቱ ከጎረቤት ሃገራት ጋር የሚያደርጉት ወዳጅነት በግልጽ እንዳልተነገረ ብሎም ኢትዮጵያ የቀደሙት ጎረቤት ወዳጆችዋን እያሳጣት ነዉም ብለዋል። የሁለቱ ሃገራት መሪዎች መወዳጀት ኢትዮጵያ በአፍሪቃዉ ቀንድ የነበራትን ቁልፍ ሚና አሳጥቶአልም ተብሎአል። ሌላዉ አሜሪካ አፍሪቃዉ ቀንድ ላይ ባላት ፍላጎት ሱዳንን ከፍ አድርጋ ለመዉጣት ያሰበች ይመስላል ሲሉ ተወያዮች አንስተዋል።

አዜብ ታደሰ

እሸቴ በቀለ