1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኦጋዴን: የነዳጅ ፍለጋው እና የጸጥታው ሁኔታ

ማክሰኞ፣ የካቲት 18 2006

በኦጋዴን አካባቢ የሚካሄደውን የነዳጅ ዘይት ቁፋሮ ኣጥብቆ እንደሚቃወም ኣማጺው የኦጋዴን ነጻ ኣውጪ ግንባር በምህጻሩ « ኦ ኤን ኤል ኤፍ » ኣስታወቀ። ኣንድ ኣንጋፋ የግንባሩ መሪ ለ« አይ ፒ ኤስ » የዜና አገልግሎት እንደገለጹት በኦጋዴን የሚገኘው የነዳጅ ዘይት ከለማ የኢትዮጵያን መንግስት ባለጸጋ ያደርገዋል።

https://p.dw.com/p/1BFEC
Kenia Rinderhüter und Rinder in Kajiado
ምስል dapd

የኦጋዴንን ህዝብ ደግሞ በድህነት እና ጭቆና ስር ያቆየናል ብሏል። ተንታኞች እንደሚሉት ከሆነ ለጊዜው በሚስጢር ቢያዝም፤ በኣሁኑ ጊዜ፤ በኦጋዴን አካባቢ የማይናቅ የነዳጅ ዘይት መጠን ለመገኘቱ በቂ መረጃዎች ኣሉ።

ኢትዮጵያ ለነዳጅ ዘይት ፍለጋ የኦጋዴን በረኃን ማሰስ ከጀመረች ዓስርተ ዓመታት ተቆጥሯል። ኣለ ተብሎ ተስፋ ባያጭርም የለም ተብሎም ግን ተስፋ ኣላስቆረጠም። እናም ፍለጋው በተለይም ኣሁን ያለው የኢትዮጵያ መንግስት ወደ ስልጣን ከመጣ ወዲህ ተጠናክሮ መቀጠሉ ይታወቃል። ሌላው ችግር የክልሉ ምናልባትም ከሶማሊያው ቀውስ ጋርም በተያያዘ በአካባቢው ኣስተማማኝ ሰላም የመታጣቱ ግዳይ ነው። በአካባቢው የተገኘው የተፈጥሮ ጋዝም ሆነ እየተፈለገ ያለው የነዳጅ ዘይት ይላሉ የኣማጺው የኦጋዴን ነጻ ኣውጪ ግንባር « ኦ ኤን ኤል ኤፍ » መስራች አብዱረህማን መሓዲ ኢንተር ፕረስ ሰርቪስ (« አይ ፒ ኤስ ») ለተሰኘው የዜና አገልግሎት ሲናገሩ ኢትዮጵያን ሀብታም ሊያደርጋት ይችላል። ነገር ግን እኛን በድህነት እና በጭቆና ውስጥ ያቆየናል። ለዚህም ነው በአካባቢው የሚካሄደውን የማዕድን ልማት ኣጥብቀን የምንቃወመው ሲሉም ያስረዳሉ። በ 2007 ዓም ለምሳሌ እአኣ ማለት ነው የ « ኦ ኤን ኤል ኤፍ » ሸማቂዎች ዘጠኝ ቻይናውያንን ጨምሮ በመቶዎች የሚቆጠሩ የመንግስት ወታደሮችን ከፈጁ በኃላ የነዳጅ ቁፋሮ ጣቢያውንም ማጋየታቸው የሚታወስ ሲሆን ከዚያ ወዲህ በኦጋዴን የሚሰማሩ የቻይና የነዳጅ ቁፋሮ ባለሙያዎች የኢትዮጵያን ወታደሮች የደንብ ልብስ እየለበሱ ለመሳሰል መገደዳቸው ኣይዘነጋም።

Bildergalerie Somalia Sicherheitslage Baido 2012
ምስል JENNY VAUGHAN/AFP/Getty Images

ኣማጺው የኦጋዴን ነጻ ኣውጪ ግንባር ኦጋዴኒያ እያለ በሚጠራው የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የራስን እድል በራስ የመወሰን መብትን ለማስከበር እንደሚታገል መግለጹ የሚታወቅ ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ የኤርትራ መንግስትን ጨምሮ በሶማሊያ ኃይሎች የውጪ ድጋፍ የሚንቀሳቀስ ኣሸባሪ ቡድን ነው ሲል እንቅስቃሴውን በወታደራዊ ጡንቻ ሲመክት ቆይቷል። በዚህ ሁሉ መካከል ታዲያ በአካባቢው የልማት ስራዎች ከመሰናከላቸውም በላይ የመብት ተሟጋቾች እንደሚሉት ሰብዓዊ መብቶች ተጥሷል። ሌላው ቀርቶ የኣስቸኩዋይ ጊዜ እርዳታዎችን ለህብረተሰቡ ማድረስ እየተቻለ ኣይደለም ተብሏል።

በኦጋዴን አካባቢ የሚገኘው የማዕድን ኃብት ለኣገሪቱ በተለይም ለራሱ ለኦዴን ክልል ይበልጥ ጠቃሚ ነው የሚሉት የኢትዮጵያ መንግስት ቃ/ኣቀባይ፤ የማስታወቂያ ሚኒስትር ዲዔታው አቶ ሺመልስ ከማል ለ« አይ ፒ ኤስ » እንዳስረዱት በክልሉ ይፈጸማል የተባለውን የመብት ጥሰት እና ሰላማዊ ሰዎችን ኢላማ ያደረገ ነው የተባለለትን ወታደራዊ ጥቃት ኣስተባብሏል።

በኦጋዴን ይገኛል የተባለውን የነዳጅ ዘይት ኣስመልክቶ ከመንግስት በኩል እስከኣሁን በይፋ የተገለጸ ነገር ባይኖርም በኬኒያ ናይሮቢ የቀውስ ኣስወጋጅ ግብረ ኃይል ተንታኝ የሆኑት ሚ/ር አብዲ ረሺድ ለዶቸቬሌ እንዳስረዱት ነዳጅ በኦጋዴን አካባቢ ለመገኘቱ በርካታ መረጃዎች ኣሉ።

«እስከሚገባኝ ድረስ ያ የኢትዮጵያ ክልል ጥሩ የነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ ውጤት እንዳለው የሚያመለክቱ በቂ መረጃዎች ኣሉ። ምናልባትም ለገበያ በቂ የሆነ መጠንም ኣለው። ነገር ግን አብዛኞቹ በዚያ የፍለጋ ስራ ለይ የተሰማሩ ኩባኒያዎች፤ ኣየህ፤ ይህንን የንግድ ሚስጢር ይጠብቃሉ።»

የሰብኣዊ መብት ይዞታው ግን ገና ኣለመሻሻሉን የጠቀሱት ተንታኙ የኢትዮጵያ መንግስት ከኦጋዴን ነጻ ኣውጪ ግንባር ጋር የጀመረው ድርድር በራሱ የዚህ ኣመላካች ነው ይላሉ።

Somalia Kämpfe in Mogadishu Hawiye-Clan
ምስል AP

«እንደሚታወቀው የአዲስ አበባው መንግስት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከ« ኦ ኤን ኤል ኤፍ » ጋር የሰላም ንግግር ጀምሯል። እንደማስበው የኢትሾጵያ መንግስት እና « ኦ ኤን ኤል ኤፍ »ን ኣሁን ወደ እርቅ እንዲያዘነብሉ ከሚያደርጉዋችው ምክኒያቶች ኣንዱ ሁለቱም ወገኖች ተጠቃሚ ስለሚሆኑ ነው። ሰላም ከሰፈነ የኢትዮጵያ መንግስትም ይጠቀማል። የኦጋዴን ህዝብም ተጠቃሚ ይሆናል። ስለዚህ የኣሁኑ የድርድር አዝማሚያ ሰላማዊ ኦጋዴን የሁለቱም ወገኖች ፍላጎት ነው ከሚል ስሌት የመነጨ ነው ብዬ ኣስባለሁ።»

በኢትዮጵያ ከኦሮሚያ ቀጥሎ በቆዳ ስፋቱ 2ኛው ትልቁ አካባቢ የሆነው የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በረኃማነት ቢያጠቃውም በተፈጥሮ ኃብት ይዞታው ግን የበለጸገ መሆኑ ይታወቃል።

ጃፈር ዓሊ

ሸዋዬ ለገሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ