ኢትዮጵያ ለደብብ ሱዳን ተጨማሪ ወታደሮችን ታዋጣለች
ሐሙስ፣ የካቲት 9 2009የአካባቢ ሃገራት በደቡብ ሱዳን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሥር ተጨማሪ ሰላም አስከባሪ እንዲያሰማሩ በተደረሰዉ ስምምነት መሰረት፣ ኢትዮጵያ ወታደሮችን ለመላክ ዝግጅት ላይ መሆንዋን የውጭ ጉዳይ ሚኒሰቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል። በሺዎች የሚቆጠሩ ደቡብ ሱዳናዉያን ከታጣቂ ኃይላት በመሸሽ ወደ ጎረቤት ሃገራት መሰደድ መቀጠላቸዉም ተነግሮአል።
በደቡብ ሱዳን የቀጠለዉ የእርስ በርስ ጦርነት የሲቪሉን ነዋሪ ሕይወት ከቀን ወደቀን ወደ አሳሳቢ ደረጃ ላይ እንዳደረሰዉ የተመድ አስታዉቋል። በሃገሪቱ የሚታየዉን ይህንኑ አሳሳቢ ጦርነት ተከትሎ ከተለያዩ ከተሞችና ገጠር የሚፈልሰዉ ሰላማዊ ሕዝብ ቁጥርም በአህጉሪቱ እስከዛሬ ያልታየና ከምንም ጊዜ በላይ መሆኑን የተመድ ዋና ፀኃፊ አንቶንዮ ጉተሪሽን ዋቢ ያደረገዉ መግለጫ ያመለክታል። ጠንካራ ማሳሰብያን የያዘዉ ይህ የመንግስታቱ ድርጅት መግለጫ ይፋ የሆነዉ በደቡብ ሱዳን ለሦስት ዓመታት የዘለቀዉን ጦርነት ለማብቃት የተመ ዋና ፀሐፊ አንቶንዮ ጉተሪሽ ከደቡብ ሱዳን አካባቢ ሃገራት ባለሥልጣናትና ከደቡብ ሱዳኑ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ጋር ባለፈዉ ወር ዉይይት ካደረጉ በኋላ ነዉ። የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒሰቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ እንደገለፁትም የአካባቢዉ ሃገራት ተጨማሪ ወታደሮችን ለማዋጣት መግባባት ላይ ደርሰዋል።
በቅርቡ አፍሪቃን የጎበኙት አዲሱ የተመድ ዋና ፀሐፊ አንቶንዮ ጉተሪሽ ከፕሬዚዳንት ሳልቫኪር ጋር ከተወያዩ በኋላ በተለይ በመዲና ጁባ የደኅንነት ሁኔታ ለማጠናከር በመንግስታቱ ድርጅት ሥር የአካባቢ ሃገራት ኃይላትን ለማስፈር በሥራ ላይ መሆኑ ተመልክቶአል። በዚሁ ስምምነት መሰረትም ሩዋንዳ የፊታችን መጋቢት አልያም ሚያዝያ ወር ወታደሮችንና የጦር ሄሌኮፕተሮችን ወደ ደቡብ ሱዳን በመላክ የመጀመርያዋ ሃገር ትሆናለች። ኢትዮጵያም ወታደሮችን ለማሰማራት ዝግጅት ላይ መሆንዋም በመግለጫዉ ተካትዋል። ይህንኑ ለዶይቼ ቬለ ያረጋገጡት የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒሰቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ መቼና እና ስንት ወታደሮች እንደሚዘምቱ ግን አልገለፁም።
የተመድ በደቡብ ሱዳን 13 ሺህ የሰላም አስከባሪ ኃይላትን ያሰማራ ቢሆንም የፀጥታ ኃይላቱ በሃገሪቱ ጦርነትና ግጭት ወደሚታይባቸዉ አካባቢዎች ሰርገዉ እንዳይገቡ ለተደጋጋሚ ጊዜ መታገዳቸዉ ተመልክቷል። የተመድ ዋና ፀሐፊ አንቶንዮ ጉተሪሽ ከደቡብ ሱዳን ፕሪዚደንት ከሳልቫኪር ጋር ቅርበት ያላቸዉን ልክ እንደ ዩጋንዳዉ ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒን አይነት የአካባቢ ሃገር መንግስታት በማስተባበር ፕሪዚዳንት ኪር ወታደሮቻቸዉን ጦርነቱ ከተጋጋመበት ቦታ እንዲያፈገፍጉ ለማድረግ ጥረት አድርገዉም ነበር። ይህኑ ጦርነት በመሸሽ በርካታ ነዋሪዎች ወደ ጎረቤት ሃገራት መሰደዳቸዉን የገለፁት አቶ ተወልደ ሙሉጌታ ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳናዉያን በርዋን መክፈትዋንም ተናግረዋል።
የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶንዮ ጉተሪሽ የፀጥታዉ ምክር ቤት በደቡብ ሱዳን አማፅያን ዉግያ እንዲያቆሙ በማሳመን የፖለቲካ ዉይይት እንዲያካያሂዱ እንዲያደርግ ተማጽነዋል። ከዚህ ሌላ ለመንግሥቱ እዉቅና በመስጠት ዓለም አቀፍ ርዳታ እንዲደርስ ሲሉ አሳስበዋል።
አዜብ ታደሰ
አርያም ተክሌ