1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያ ለደብብ ሱዳን ተጨማሪ ወታደሮችን ታዋጣለች

ሐሙስ፣ የካቲት 9 2009

በደብቡ ሱዳን እየተባባሰ የመጣዉ ጦርነት የሃገሪቱን ዜጎች ኑሮ እጅግ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መጣሉን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዘገባ አመለከተ። የአካባቢ ሃገራት በደቡብ ሱዳን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሥር ተጨማሪ ሰላም አስከባሪ እንዲያሰማሩ በተደረሰዉ ስምምነት መሰረት ኢትዮጵያ ወታደሮችን ልታዘምት ነዉ።

https://p.dw.com/p/2XgQr
Südsudan Kämpfer
ምስል picture alliance/AP Photo/J. Lynch

UNSC-Warnung von Gutuerres vor Katastrophe im Südsudan /MMT - MP3-Stereo

የአካባቢ ሃገራት በደቡብ ሱዳን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሥር ተጨማሪ ሰላም አስከባሪ እንዲያሰማሩ በተደረሰዉ ስምምነት መሰረት፣  ኢትዮጵያ ወታደሮችን  ለመላክ ዝግጅት ላይ መሆንዋን የውጭ ጉዳይ ሚኒሰቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል። በሺዎች የሚቆጠሩ ደቡብ ሱዳናዉያን ከታጣቂ ኃይላት በመሸሽ ወደ ጎረቤት ሃገራት መሰደድ መቀጠላቸዉም ተነግሮአል።  

Sudan Bürgerkrieg John Garang 1997
ምስል picture-alliance/dpa/Rosenthal

በደቡብ ሱዳን የቀጠለዉ የእርስ በርስ ጦርነት የሲቪሉን ነዋሪ ሕይወት ከቀን ወደቀን ወደ አሳሳቢ ደረጃ ላይ እንዳደረሰዉ የተመድ አስታዉቋል። በሃገሪቱ የሚታየዉን ይህንኑ አሳሳቢ ጦርነት ተከትሎ ከተለያዩ ከተሞችና ገጠር የሚፈልሰዉ ሰላማዊ ሕዝብ ቁጥርም በአህጉሪቱ እስከዛሬ ያልታየና ከምንም ጊዜ በላይ መሆኑን  የተመድ ዋና ፀኃፊ አንቶንዮ ጉተሪሽን ዋቢ ያደረገዉ መግለጫ ያመለክታል።  ጠንካራ ማሳሰብያን የያዘዉ ይህ የመንግስታቱ ድርጅት መግለጫ ይፋ የሆነዉ በደቡብ ሱዳን ለሦስት ዓመታት የዘለቀዉን ጦርነት ለማብቃት የተመ ዋና ፀሐፊ አንቶንዮ ጉተሪሽ ከደቡብ ሱዳን አካባቢ ሃገራት ባለሥልጣናትና ከደቡብ ሱዳኑ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ጋር ባለፈዉ ወር ዉይይት ካደረጉ በኋላ ነዉ። የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒሰቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ እንደገለፁትም የአካባቢዉ ሃገራት ተጨማሪ ወታደሮችን ለማዋጣት መግባባት ላይ ደርሰዋል።    

በቅርቡ አፍሪቃን የጎበኙት አዲሱ የተመድ ዋና ፀሐፊ አንቶንዮ ጉተሪሽ  ከፕሬዚዳንት ሳልቫኪር ጋር ከተወያዩ በኋላ በተለይ በመዲና ጁባ የደኅንነት ሁኔታ ለማጠናከር በመንግስታቱ ድርጅት ሥር የአካባቢ ሃገራት ኃይላትን ለማስፈር በሥራ ላይ መሆኑ ተመልክቶአል። በዚሁ ስምምነት መሰረትም ሩዋንዳ የፊታችን መጋቢት አልያም ሚያዝያ ወር ወታደሮችንና የጦር ሄሌኮፕተሮችን ወደ ደቡብ ሱዳን በመላክ የመጀመርያዋ ሃገር ትሆናለች። ኢትዮጵያም ወታደሮችን ለማሰማራት ዝግጅት ላይ መሆንዋም በመግለጫዉ ተካትዋል። ይህንኑ ለዶይቼ ቬለ ያረጋገጡት የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒሰቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ መቼና እና ስንት ወታደሮች እንደሚዘምቱ ግን አልገለፁም።

Symbolbild Frauen Opfer Konflikt Südsudan
ምስል GetttyImages/AFP/C. Lomodon

የተመድ በደቡብ ሱዳን 13 ሺህ የሰላም አስከባሪ ኃይላትን ያሰማራ ቢሆንም የፀጥታ ኃይላቱ በሃገሪቱ ጦርነትና ግጭት ወደሚታይባቸዉ አካባቢዎች ሰርገዉ እንዳይገቡ ለተደጋጋሚ ጊዜ መታገዳቸዉ ተመልክቷል። የተመድ ዋና ፀሐፊ አንቶንዮ ጉተሪሽ ከደቡብ ሱዳን ፕሪዚደንት ከሳልቫኪር ጋር ቅርበት ያላቸዉን ልክ እንደ ዩጋንዳዉ ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒን አይነት የአካባቢ ሃገር መንግስታት በማስተባበር ፕሪዚዳንት ኪር ወታደሮቻቸዉን ጦርነቱ ከተጋጋመበት ቦታ እንዲያፈገፍጉ ለማድረግ ጥረት አድርገዉም ነበር። ይህኑ ጦርነት በመሸሽ በርካታ ነዋሪዎች ወደ ጎረቤት ሃገራት መሰደዳቸዉን የገለፁት አቶ ተወልደ ሙሉጌታ ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳናዉያን በርዋን መክፈትዋንም ተናግረዋል።    
የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶንዮ ጉተሪሽ የፀጥታዉ ምክር ቤት በደቡብ ሱዳን አማፅያን ዉግያ እንዲያቆሙ በማሳመን የፖለቲካ ዉይይት እንዲያካያሂዱ እንዲያደርግ ተማጽነዋል። ከዚህ ሌላ ለመንግሥቱ እዉቅና በመስጠት ዓለም አቀፍ ርዳታ እንዲደርስ ሲሉ አሳስበዋል።      

አዜብ ታደሰ

አርያም ተክሌ