1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አዲሱ የጀርመን የስደተኞች ጉዳይ ረቂቅ ሕግ

ዓርብ፣ ሚያዝያ 7 2008

የጀርመን ተጣማሪ መንግሥት በአዲስ የስደተኞች ረቂቅ ሕግ ጉዳይ ትናንት ስምምነት ላይ ደርሷል። ረቂቅ ሕጉ፣ የስደተኞችን ሥራ የማግኘት ዕድል እንደሚያሰፋና እንደሚያፋጥን ተገልጿል።

https://p.dw.com/p/1IWi0
Pressekonferenz Angela Merkel Horst Seehofer Siegmar Gabriel Thomas de Maiziere
ምስል Reuters/F. Bensch

[No title]

በሌላ በኩል በረቂቁ ጀርመን ተገን የተሰጣቸው ስደተኞች ከኅብረተሰቡ ጋር ተዋሕደው እንዲኖሩ በተቀረጸው መርሃ ግብር የተካተቱትን መስፈርቶች ካላሟሉ መንግሥት የሚሰጣቸው ድጋፍ እንደሚቀንስም ተጠቅሷል። ቀጣዩ ዘገባ የረቂቅ ህጉን ምንነትና አላማ ይቃኛል።
የጀርመን ተጣማሪ መንግሥት ትናንት ስምምነት ላይ የደረሰው ባለፈው ዓመት ጀርመን የገቡ 1.1 ሚሊዮን የሚሆኑ ስደተኞች ከኅብረተሰቡ ጋር ተዋሕደው ለመኖር ያግዟቸዋል በተባሉ ልዩ ልዩ እርምጃዎች ላይ ነው። ተጣማሪው መንግሥት የተስማማበት በረቂቅ ደረጃ የቀረበው ይኽው ሕግ የሕግ ባለሙያና የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር ዶክተር ይልማ ይፍራሸዋ እንዳሉት በመጀመሪያ ደረጃ ከቀድሞው በተለየ የተገን ጠያቂዎችን መኖሪያ የሚገድብ ነው።
መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ግጭትና ግድያን ሸሽተው ጀርመን የመጡ ስደተኞች የተገን ጥያቄያቸው አፋጣኝ መልስ እንዲያገኝ፣ የኤኮኖሚ ስደተኞች የሚሏቸው ደግሞ በተቻለ ፍጥነት ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ይፈልጋሉ። እዚህ መኖር የተፈቀደላቸው ደግሞ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሳይሠሩ የመንግሥት ድጎማ ተቀባይ እንዲሆኑ አይፈለግም።
ስደተኞች የቋንቋ ትምህርት ለመጀመር እንደ ከዚህ በፊቱ ሶስት ወር መጠበቅ የለባቸውም። አዲሱ ሕግ ጊዜውን ወደ 6 ሳምንት አሳጥሮታል። ሕጉ ታሪካዊ ሊባል የሚችል ለውጥም ተካቶበታል። ዶክተር ለማ እንደሚያስረዱት ረቂቁ ከዚህ ቀደም የተመናመነ የነበረውን፣ ለስደተኞች ክፍት የሥራ ቦታ የማግኘት እድልንም ያሰፋል።
የስደተኞችን መብት እና ግዴታዎች የተዘረዘሩበት ይኽው ሕግ ይላሉ ዶክተር ለማ በዋነኛነት ወደ ጀርመን የሚመጣውን ስደተኛ ቁጥር ለመቀነስ ያለመመም ነው።
ረቂቅ ሕጉ ለሀገሪቱ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከመቅረቡ በፊት ከጀርመን ፌደራዊ ክፍላተ ሃገራት መሪዎች ጋር ውይይት ይደረግበታል።

Integrationskurs "Deutsch als Fremdsprache"
ምስል picture alliance / dpa

ኂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ