1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አይቮሪ ኮስትና የዕርቀ-ሰላሙ ጠንቅ፣

ሐሙስ፣ የካቲት 21 2005

የአይቮሪ ኮስት ወታደሮችና ተጓዳኝ ሚሊሺያ ጦረኞች፤ ከሥልጣን የተወገዱትን የፕሬዚዳንት ሎራ ባግቦን ደጋፊዎች፤ እያያዙ ቁምስቅል በማሳየትና በመግደል ፤ በተፈናቀሉ ሰዎች መጠለያ ጣቢያም አሠቃቂ ጥቃት መፈጸማቸውን ፣ ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋቹ

https://p.dw.com/p/17oLV
ምስል AP

ድርጅት (አምነስቲ ኢንተርናሽናል)አጋለጠ። AI ፣ ይህን የመሰለው ድርጊት ለዕርቀ ሰላም መሰናክል መሆኑን አስገንዝቧል።

ሰፊ የኮኮዋ ምርት በማቅረብ  በዓለም  የመጀመሪያውን ደረጃ በያዘችው ሀገር፤ ያልተቋረጠው የበቀል እርምጃና ፤ መንግሥትም ይህን ለማስቆም ጥረት አለማድረጉ፣ከ 2 ዓመት በፊት ያከተመው የእርስ በርስ ጦርነት ቁስል እንዳይሽር ሰበብ ሆኗል።

Laurent Gbagbo Anhörung Internationaler Gerichtshof in Den Haag
ምስል Reuters

A I ባወጣው መግለጫ  ላይ፣ «የአይቮሪኮስት ጦር ሠራዊት፣ ዶዞስ  በመባል  ከታወቁ በአደን ከሚኖሩ ሚሊሺያ ጦረኞች  ጋር በመተባበር ፣ በፖለቲካ ዓላማ ተነሳስተው ሰዎችን እንዳሻቸው እየያዙ  ያሥራሉ ፤ ቁም ስቅል ያሳያሉ » ብሏል።

እ ጎ አ ሐምሌ 20 ቀን  2012 ጧት 2 ሰዓት ላይ« የታጠቁ 12 ገደማ ዶዞስ በመጠለያ ጣቢያው በር በኩል ለመግባት ሲሞክሩ የተባበሩት መንግሥታት  ሰላም አስከባሪዎች ከለከሏቸው። ተመልሰው በጣቢያው አካባቢ ሲጠባበቁ 1,000 ያህል ጠብመንጃ ፣ ገጀራ፣ ቆመጥና መጥረቢያ የያዙ ሰዎች ወደ መጠለያው አጥር ጥሰው ገቡ።  ዶዞስ ፣ ድንኳኖቹን መቅደድ ጀመሩ፣ ጨርቅ በጋዝ እያራሱና እያቀጣጣሉ ወደ ድንኳኖች ወረወሩ ፤ መለዮ የለበሱ ወታደሮችም ወደ ህዝቡ ይተኩሱ ነበር » ሲል አንድ ከጥቃቱ የተረፈ ሰው አስረድቷል።

የ AI የምዕራብ አፍሪቃ ጉዳዮች ተመራማሪ ጌታን ሙቶ እንዳሉት፣ እስካሁን ድረስ የፕሬዚዳንት አላሳን ዋታራ ደጋፊዎች ለፈጸሙት በደል አንድ ሰው እንኳ ተጠያቂ ሲሆን አልታየም።

«በአሁኑ ጊዜ የሎራ ባግቦ  ደጋፊዎች መሆናቸው በትክክልየታወቀና ሊሆኑ ይችላሉ ተብለው የተጠረጠሩ ሰዎች፤ እየተያዙ ይታሠራሉ። በተለያዩ ወህኒ ቤቶች የሚማቅቁት የባግቦ አስተዳደር አባላት የነበሩ ሰዎች ናቸው። ከዚያም በተረፈ ሌሎች በዛ ያሉ ሰዎች ተይዘው  ታሥረዋል የታሠሩበት ቦታም፣ ህገ ወጥ በሆነ አሠራር የተመደበ ነው። እሥረኞች፣ ይደበደባሉ በግፍ እርምጃ ቁምስቅል እንዲያዩ ይደረጋል። በሳን ፔድሮም፣ በዛ ያሉ ሰዎች፤ ተይዘው ከመታሠራቸውም በኤሌክትሪክ ዘግናኝ ተግባር ይፈጸምባቸዋል። »

Bürgekrieg in Elfenbeinküste in 2011
ምስል dapd

በተባበሩት መንግሥታት ሰላም አስከባሪዎችና በፖሊስ ይጠበቅ የነበረው በአመዛኙ የባግቦ ጭፍን ደጋፊዎች የተሰኙትን     የ «ገር» ጎሳ አባላት ያስጠለለው 5,000 ያህል ሰዎች ይገኙበት የነበረው ናሂብሊ ጣቢያ፣ ባለፈው ሐምሌ 20 የበቀል እርምጃ እንደተወሰደበት

የካናዳ A I ዋና ፀሀፊ አሌክስ ነቭ ያደረጉት ምርመራ ያስረዳል። እርሳቸው አንዳሉት በጣቢያው ላይ የተወሰደው እርምጃ፤ በአቅድ የተደረገ እንጂ እንዲሁ በደም ፍላት የተፈጸመ ድርጊት አልነበረም።

ስለሆነም፤ A I በናሂብሊ መጠለያ ጣቢያ ላይ የተወሰደው የማጥቃት እርምጃ በዘፈቀደ ሰዎች እየተያዙ የታሠሩበት ድርጊትና ደብዛቸው የጠፋበት ሁኔታ በዓለም አቀፍ ኮሚሽን እንዲመረመር አሳስቧል።

የአይቮሪኮስት ባለስልጣናት ፤ በበኩላቸው፣ በመጠለያ ጣቢያው ላይ ወረራ የተፈጸመው ባካባቢው በምትገኝ ዶኩ በተባለችው ከተማ 4 ሰዎች በመገደላቸው ለመበቀል ታስቦ ነው፤ ባዮች ናቸው። ለ A I ምርመራ ውጤት ይፋ ምላሽ ከመስጠት በመቆጠብም፤ ዐቃቤ ህግ ጉዳዩን ገና በማጣራት ላይ ነው የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።

ተክሌ የኋላ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ