አንጎላ ሐብት፤ ድሕነትና ምርጫ
ረቡዕ፣ ሐምሌ 25 2004
የአንጎላ ፖለቲከኞች ካንድ ወር ካንድ ወር በኋላ ለሚደረገዉ የምክር ቤት አባላት ምርጫ ትናት የምረጡኝ ዘመቻ ጀምረዋል።MPLA በሚል የፖርቱጋልኛ ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ ገዢ ፓርቲ ባሻሻለዉ ሕገ-መንግሥት መሠረት የሐገሪቱን መሪ የሚመረጠዉ አብላጫ የምክር ቤት መቀመጫዎች የሚኖረዉ ፓርቲ ነዉ።በአንጎላ የነፃነት ታሪክ ለሰወስተኛ ጊዜ በሚደረገዉ በዚሕ ምርጫም MPLA ማሸነፉ ብዙ አላጠራጠረም።ፓርቲዉ አሸነፈ ማለት ላለፉት 32 ዓመታት ሐገሪቱን የገዙት ፕሬዝዳት ሆሴ ኤድዋርዶ ዶስ ሳንቶስ በመሪነት ይቀጥላሉ ማለት ነዉ።የደሐዉና የሐብታሙ አንጎላዊ የኑሮ ልዩነት ግን፥ የዶቸ ቬለዉ ዮሐንስ ቤክ እንደታዘበዉ ከልክ እያለፈ ነዉ።የቤክን ዘገባ ነጋሽ መሐመድ ባጭሩ አጠናቅሮታል።
ለሱ ሙዚቃ ነዉ የብሶቱ መግለጫ።
«ይሕ ልዩነት ለከት አጣ።እኛ በዚሕ ወጥመድ ተይዘናል።----ለባርነት ተፈርዶብናል----ሁሉም የናንተ ነዉ፥ነዳጁ---አልማዙ ቤቱ ሁሉም የናንተ---ነዉ---» እያለ ያዜማል።ራፐር ነዉ-የሚባለዉ።ሙዚቀኛዉ MCK
የአንጎላ ወጣቶች የሰላሳ-ሁለት ዘመን ገዢያቸዉን አገዛዝ በመቃወም እንደ አረቦቹ አደባባይ መዉጣት ከጀመሩ ዋል-አደር አሉ።እስካሁን ግን ጠብ ያለላቸዉ ሊኖር ቀርቶ የመገናኛ ዘዴዎችንም ትኩረት አልሳቡም።ድሕነትን ለማቃለል አንጎላ ከገዢዎችዋ ፍላጎት በስተቀር ሁሉም አላት።ሠላም ናት።በነዳጅ ዘይት ላይ የተመሠረተዉ ምጣኔ ሐብቷ እስከ ሃያ በመቶ ያድግ ነበር።ከዓለም አንደኛ።
ሐብቱ ግን ሙዚቀኛዉ እንደሚለዉ የጥቂቶች መንደላቀቂያ ነዉ-የሆነዉ።
«ከድገቱ በደርዘን የሚቆጠሩ ጥቂት ሰዎች ምን ሐይል እንደከበሩ ማየት ችለናል።ወትሮም ሐብታም የነበሩት ጥቂት ቡድናት ይበልጥ ሲከብሩ የኛ የአብዛኞቹ መቃብር ተቆፍሯል።ትንሽ በግልፅ የሚታየዉ ጠንካራ እድገት የሚባለዉ (የመንገድ) የመሠረተ ልማት ግንባታ ነዉ።»
ርዕሠ ከተማ ሉዋንዳ ዉስጥ የብራዚል፥ የፖርቲጋልና የቻይና ኩባንዮች ለሐብታሞቹ የሚመቹ ዘመናይ መንደሮች፥ ያማሩና ያሸበረቁ የመኖሪያና የቢሮ ሕንጻዎች ይገነባሉ።አዉራ ጎዳኖች፥ የባቡር መስመሮችን ይሠራሉ ወይም ያድሳሉ።
ሁሉም ከከርሰ ምድር ከሚዛቀዉ ነዳጅ ዘይት ሸያጭ የሚከፈል ነዉ።አንጎላ ነዳጅ ዘይት በመሸጥ ከናጀሪያ ቀጥሎ ሁለተኛዋ አፍሪቃዊት ሐገር ናት።የዚያኑ ያክል የድሕነቱ መጠን አስከፊ ነዉ። በአንዳድ የሐገሪቱ ግዛቶች የኤሌክትሪክ መብራት፥ የቧምቧ ዉሐ ጨርሶ የለም።በቀላሉ በሚድኑ በሽታዎች ሚሊዮኖች ያልቃሉ።በተለይ ሕፃናት።ከየስድስቱ ሕፃን አንዱ አምስት ዓመት ሳይሞላዉ ይሞታል።አንጎላ ጎረቤት ናቢያ ከሚሞቱት በሰወስት እጥፍ ይበልጣል ማለት ነዉ።
«አንጎላ ዛሬ ምባልባት ከመላዉ ዓለም እጅግ የከፋ የሰዎች የኑሮ ተባለጥ የሚታይባት ሐገር ሳትሆን አትቀርም።እንደ አንጎላ ሐብታሞች ሐብታቸዉን አደባባይ የሚያሰጡበት ሐገር የለም።ይሕ ማሕበራዊ ፍንዳታ ሊያስከትል ይችላል።ይሕ አደጋ አለ።»
ይላሉ ደራሲ ሆሴ ኤድዋርዶ አጉዋሉስ።
ገዢዉ ፓርቲ MPLA «አንጎላን ይበልጥ ማሳደግ፥ ሐብቷን እኩል ማከፋፈል እያለ ለምርጫ ዘመቻዉ ይለፍፋል።በተጨባጭ የሚታየዉ ግን ተቃራኒዉ ነዉ።የዓለም የገንዘብ ድርጅት እንዳስታወቀዉ ባለፉት አምስት አመታት ከነዳጅ ዘይት ሺያጭ የተሰበሰበ አርባ-ሁለት ቢሊዮን ዶላር የገባበት በትክክል አይታወቅም።
አርባ-ሁለት ቢሊዮን ዶላር!!! ከኬንያ፥ ከኢትዮጵያ ወይም ከጋና አጠቃላይ አመታዊ ገቢ በእጅጉ ይበልጣል።የፕሬዝዳንት ዶሳን ቶስ መንገሥት ገንዘቡ መንገድን ለመሳሰሉት የመሠረተ ልማት አዉታሮች ወጪ ሆኗል ባይ ነዉ።የትኛዉ መንገድ ምን ያሕል ፈጀ-ለሚለዉ ጥያቄ ግን መልስ የለም።
ራፐር MCK እና ብጤዎቹ የአንጎላ ሕዝብን ከግፍ አገዛዝ ለማላቀቅ አብነቱ ፖለቲካዊ ለዉጥ ነዉ ባዮች ናቸዉ።በቅርቡ በሚደረገዉ ምርጫ ግን ገዢዉ ፓርቲ ከሁለት መቶ ሃያዎቹ መቀመጫዎች አብዛኞቹን መቆጣጠሩ አላጠራጠረም።ለዉጥ። ግን እንዴት?
ነጋሽ መሐመድ
ተክሌ የኋላ