1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አነጋጋሪው የደቡብ ሱዳን የሰላም ውል

ዓርብ፣ ሚያዝያ 14 2008

በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ታቅዶ የነበረው የደቡብ ሱዳን የብሔራዊ የአንድነት መንግስት አለመምሠረት በሃገሪቱ ሰላም ለማውረድ የሚደረገውን ጥረት እንዳያደናቅፍ እያሰጋ ነው ። የደቡብ ሱዳን አማፅያን መሪ ሪክ ማቸር በሳምንቱ መጀመሪያ ጁባ ይገባሉ ተብለው ሲጠበቁ መቅረታቸው ብዙ የተለፋበትን የሰላሙን ተስፋ አደብዝዞታል ።

https://p.dw.com/p/1Ib3S
Bildkombo Südsudan Riek Machar und Salva Kiir
ምስል Getty Images/Zacharias Abubeker/Ashraf Shazly/Montage

[No title]

ዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ሁለቱም ወገኖች የሽሽግሩን መንግሥት ምሥረታ እንዲያፋጥኑ ጥሪ አቅርቧል ። የደቡብ ሱዳንን የሰላም ስምምነት ተግባራዊነት የሚቆጣጠርና የሚገመግመው ዓለም አቀፍ ኮሚሽን ሁለቱ ወገኖች እስከ ነገ እንዲስማሙና ማቻርም ጁባ እንዲሄዱ ቀነ ገደብ አስቀምጧል ።
ሰኞ ሚያዚያ 10 ፣ 2008 ዓም ነበር የደቡብ ሱዳንን የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ቀጠሮ የተያዘው ። የአማፅያኑ መሪ የቀድሞ ምክትል ፕሬዝዳንት ሪክ ማቻር በቃለ መሃላው ስነስርዓት ላይ ለመገኘት ባለፈዉ ሳምንት አርብ ነበር ደቡብ ሱዳን ገቡ የተባለው ። ይሁንና በዚህ ሳምንት ሰኞ የጁባ ጉዞአቸው ለማክሰኞ መተላለፉ ተነገረ ። እንደተባለው ግን ማቸር ማክሰኞም ጁባ አልሄዱም ፤እንዲያውም የጁባ ጉዞአቸውን ላልተወሰነ ጊዜ መሰረዛቸው ተሰማ ። አማፅያኑ እንዳሉት ማቻር ጁባ ያልሄዱት ዓለም ዓቀፍ የጉዞ እገዳ የተጣለባቸው ከፍተኛ ጀነራላቸው ሲሞን ጋትዌች ከኢትዮጵያ ወደ ጁባ መብረር በመከልከላቸው ነው ። የደቡብ ሱዳን መንግሥት ደግሞ ጋትዌች ከሰላም ስምምነቱ ውጭ ከባድ የጦር መሣሪያዎችና ተጨማሪ 260 ወታደሮቻቸውን ይዘው ርዕሠ-ከተማ ጁባ ለመግባት በመፈለጋቸው ምክንያት የማቻርን ጉዞ መከልከሉን አስታውቋል ። \በውዝግቡ ሰበብ የደቡብ ሱዳን የሽግግር መንግሥት ምሥረታ መዘግየት በሃገሪቱ ሰላም ለማውረድ በሚደረገው ጥረት ላይ ጥላአጥልቷል ። አቶ አበበ አይንቴ፣በኢትዮጵያ የሰላም እና ልማት ዓለም አቀፍ ተቋም ከፍተኛ ተመራማሪ እንደሚሉት የመንግሥት ምሥረታው መዘግየት የሰላሙን ጥረት አውኳል ፤ የህዝቡንም ስቃይ እያራዘመው ነው ።
በደቡብ ሱዳን የሰላም ስምምነት መሠረት የሚመሰረተው መንግሥት እድሜ 30 ወራት ነው ። ከዚያ በኋላም ምርጫ ለመጥራት ነው የታሰበው ። ማቻር ጁባ አለመሄዳቸው ለሰላም ስምምነቱ አደጋ ነው ሲል የስምምነቱን ተግባራዊነት የሚቆጣጠረው ኮሚሽን አሳስቧል ። በተቻለ ፍጥነት ወደ ጁባ ካልተመለሱም የሰላም ስምምነቱ ተግባራዊነትን ማጓተቱ እንደማይቀር ነው የተገለፀው ።ዩናይትድ ስቴትስ ማቻር ጁባ ባለመሄዳቸው ቅሬታዋን ገልፃለች ። የተመድ የጸጥታ ጥበቃ ምክር ቤት በበኩሉ ሁለቱም ወገኖች በአፋጣኝ የሽግግሩን መንግሥት እንዲመሰርቱና የሰላም ስምምነቱን ተግባራዊ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል ። ኪርና ማቻር የፈረሙትን የሰላም ስምምነት በተግባር እንዲተረጉሙ የዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ጥረት ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ይላሉ አቶ አበበ ።
የደቡብ ሱዳን የሰላሙ ጥረት ለመጓተቱ ፣ የሰላም ስምምነቱ ተግባራዊ እንዳይሆን በሚያውኩ ወገኖች ላይ ጠንከር ያለ እርምጃ አለመወሰዱን አንደ ምክንያት የሚያነሱ ወገኖች አሉ ። አቶ አበበ እንደሚሉት ግን ከነዚህ እርምጃዎች ይልቅ ውጤት ሊያመጣ የሚችለው ሳልቫ ኪርና ማቻር ለህዝባቸው ሲቆሙ ብቻ ነው ።

Südsudan Flüchtlingscamp Flüchtlinge in Yida
ምስል Getty Images/AFP/A. G. Farran

ኂሩት መለሰ

ነጋሽ መሀመድ