1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አለመረጋጋት ያጠላበት የኢትዮጵያ ቱሪዝም

ረቡዕ፣ ጳጉሜን 2 2008

በኢትዮጵያ የተቀሰቀሰው ፖለቲካዊ ተቃውሞ በአገሪቱ የቱሪዝም ዘርፍ ላይ ጫና ማሳደር ጀምሯል። በኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት በበኩሉ ተቃውሞው በበረታባቸው ያለፉት የክረምት ወራት ወደ አገሪቱ የመጓዝ እቅዳቸውን የሰረዙ የውጭ አገር ጎብኚዎች ቁጥር አነስተኛ እንደሆነ ገልጧል።

https://p.dw.com/p/1JxIk
Bet Giyorgi Felsenkirche von Lalibela in Äthiopien
ምስል picture alliance/Robert Harding World Imagery

አለመረጋጋት ያጠላበት የኢትዮጵያ ቱሪዝም

የብሪታኒያ መንግሥት ወደ ኢትዮጵያ ለሚጓዙ የሚጓዙ ዜጎቹ ሰዎች በብዛት በሚሰበሰቡባቸው አካባቢዎች እንዳይገኙ ከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲያደርጉም አሳስቧል። የብሪታኒያ የውጭ ግንኙነት እና ኮመንዌልዝ ቢሮ በዚህ ወር መጀመሪያ ባወጣው የጉዞ ማሳሰቢያ በአማራ እና የኦሮሚያ ክልሎች ያለ ምንም ማስጠንቀቂያ ተቃውሞ ሊቀሰቀስ፤ ወደ ኹከት ሊቀየር እንደሚችልም ጠቁሟል። የስልክ እና የኢንተርኔት አገልግሎቶች ሊቋረጡ አውራ ጎዳናዎች ሊዘጉ ይችላሉም ብሏል።
ባለፉት ወራት እንዲህ አይነት ማስጠንቀቂዎች ከብሪታኒያ ብቻ ሳይሆን ከካናዳ፤ አሜሪካ፤ አየርላንድ እና እስራኤልን ከመሳሰሉ አገሮች በተደጋጋሚ ተላልፈዋል። ዓለም አቀፍ የጉዞ ወኪሎችም አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የኢትዮጵያ ከተሞች የሚጓዙ አገር ጎብኚዎች ሕዝባዊ ተቃውሞ እና ኹከት ሊከሰት ስለሚችል ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ይመክራሉ። በኢትዮጵያ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ እና የምዕራባውያኑ የጉዞ ማስጠንቀቂያ ገና ካሁኑ በኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ላይ ጫናውን ማሳደር ጀምሯል። አዲስ ቱር እና ትራቭል የኢትዮጵያ ታሪካዊ ቦታዎችን፤ባህላዊ ክዋኔዎችን እና ብሔራዊ ፓርኮችን ያስጎበኛል። ድርጅቱ ባለፈው ወር ብቻ ዘጠኝ የውጭ አገር ጎብኚዎች በኢትዮጵያ ሊያደርጉት ያቀዱትን ጉዞ እንደሰረዙበት አቶ ቢኒያም ታዬ ይናገራሉ።
በኢትዮጵያ በተቀሰቀሰው ተቃውሞ በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፤የሳይንስ እና ባህል ድርጅት ወይም ዩኔስኮ በዓለም ቅርስነት ከተመዘገቡ ዘጠኝ ቅርሶች መካከል ሶስቱ የሚገኙት ተቃውሞ በተቀሰቀሰባቸው አካባቢዎች ነው።
Ausstellung Catherine Chamber
ምስል DW/H. Demissie
የአፄ ፋሲለደስ አብያተ-መንግስታት፤የላሊበላ ውቅር አብያተ-ክርስቲያናት እና የሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ። የአገር ጎብኚዎች በአንድ ጉዞ በአማራ እና ትግራይ ክልል የሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎችን ይጎበኛሉ። ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ ባለሙያ በኢትዮጵያ የተከሰተው አለመረጋጋት የሚያውከው ግጭቶች በተከሰቱባቸው አካባቢዎች የሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎችን ብቻ ሳይሆን ችግሮች የሌሉባቸውን ጭምር እንደሚሆን ተናግረዋል። ባለሙያው የኢትዮጵያ ነባራዊ የፖለቲካ ምሥቅልቅል አፋጣኝ መፍትሔ ካላገኘ በሁለት እግሩ ላልቆመው የኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ዘላቂ ፈተና እንደሚሆንም ተናግረዋል። አቶ ሚርከና ሑንዴሳ በኢትዮጵያ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የቱሪዝም ፕሮሞሽን ባለሙያ ሆነው አገልግለዋል። ነዋሪነታቸውን በብሪታኒያ ያደረጉት አቶ ሚርከና የምዕራባውያን አገራት ኤምባሲዎች ያሰራጩት መልዕክት የአገር ጎብኚዎችን ሃሳብ ሊያስለውጥ ይችላል ይላሉ።
እሸቴ በቀለ
ነጋሽ መሀመድ