1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኖርዌይና የኢትዮጵያ ስደተኞች

ማክሰኞ፣ ጥር 22 2004

ኖርዌይ ስደተኞች ወደ አገራቸው የሚመለሱበት ስምምነት ከኢትዮጵያ ጋ መፈፀሟን እና 400 ስደተኞችን ልትመልስ እንደሆነ አሳወቀች።

https://p.dw.com/p/13tFi
ምስል dapd

ኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የሐገሪቱ  መንግስት የጥገኝነት ጥያቄያቸውን ውድቅ ማድረጉን በመቃወም  በተደጋጋሚ በአደባባይ ተቃውሞ ማድረጋቸው ይታወሳል። አሁን ደግሞ ኖርዌይ  ስደተኞች ወደ አገራቸው የሚመለሱበት ስምምነት ከኢትዮጵያ ጋ መፈፀሟን እና 400 ስደተኞችን ልትመልስ እንደሆነ ተናግራለች።

የኢትዮጵያ ስደት ጠያቂዎች ማህበር በኖርዌይ  አባል፤ አቶ ልኡል አለማየሁ፤ኖርዌይ ውስጥ 11 ዓመት ሆኗቸዋል። ከዚህ በፊት ስደተኞች ያደረጉትን የርሀብ አድማ በቅርብ ሆነው ሲያስተናብሩ ቆይተዋል።

እኢአ ከ መጋቢት 15 በፊት ወደ አገሩ ለመመለስ ፍቃደኛ ለሆነ ኢትዮጵያዊ ኖርዌይ 40 000 ክሮነር እንደምትሰጥ ገልፃለች። ለመሆኑ ገንዘቡ አዲስ ህይወት በኢትዮጵያ ለመመስረት በቂ ነው? ስደተኞቹስ ፍቃደኛ ናቸው? አቶ ልኡል አለመሆናቸውን ገልፀውልናል። 

Puzzlebild Triptychon Italien Flüchtlinge aus Nordafrika auf Lampedusa Dossierbild 2
ምስል picture-alliance/Milestone Media

ስደተኞቹ ለሳምንታት የርሀብ አድማ በማድረግ እና በተለያዩ መንገዶች በኖርዌይ የመኖሪያ ፍቃድ እንዲያገኙ ጠይቀዋል። ጉዳዩ የሚመለከተው የኖርዌይ የፍትህ ሚኒስቴር ነው። ኖርዌይ ከኢትዮጵያ ጋ ስምምነት ስላደረገች ብቻ በርግጥ ስደተኞቹ አገር ለቀው ይወጣሉ ብላ ኖርዌይ ታምናለች?   «አንዳንዶቹ በፍቃደኝነት ይመለሳሉ ብዬ አምናለው። ምክንያቱም ዛሬ ራሱ በፍቃደኝነት ከኖርዌይ ወደ ኤርትራ እና ኢትዮጵያ የሚመለሱ ስደረኞች ገጥመውናል። ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ግን ፍቃደኛ አይሆኑም!» ይላሉ ምክትል ሚንስትሩ ፖል ሎንሴት። 

እንደ አቶ ልኡል ብዙ ኢትዮጵያውያን በኖርዌይ በርካታ አመታት አስቆጥረዋል። ከነሱም ውስጥ የፖለቲካ ተገን ጠያቂዎች ይኖራሉ። እነዚህን ስደተኞች ወደ አገራቸው መመለስ አደጋ ሊጥልባቸው አይችልም? ፖል ሎንሴት ሲመልሱ « ከለላ ለሚያስፈልጋቸው ከለላ መስጠት ለኖርዌይ አስፈላጊ ነው። ለዛም ነው የእያንዳንዱን ስደተኛ ማመልከቻ የምንመለከተው። ከለላ የሚያስፈልጋቸው ኖርዌይ የሚቆዩበት ፍቃድ ያገኛሉ። ስምምነቱ የተደረገው ከለላ መስጠት ለማያስፈልጋቸው ነው። የፖለቲካ እንቅስቃሴን በተመለከተ ለነበሩ ጥያቄዎች ተቀባይነት አግኝተው የኖርዌይ ባለስልጣናት መልስ ሰጥተውበዋል። »

ኖርዌይ ወደ አገራቸው ልትመልስ ያለችው 400 የኢትዮጵያ ስደተኞች ጨርሶ ከለላ እንደማያስፈልጋቸው የተረጋገጠ ሲሆን። የተቀሩት ስደተኞች ተቀባይነት ያገኛሉ ማለት ነው ወይ ለሚለው ጥያቄ የተቀሩትም በፍቃደኝነት ይመለሳሉ ከማለት በስተቀር ከመልስ ተቆጥበዋል። 

ልደት አበበ

ተክሌ የኋላ