ትኩረት በአፍሪቃ
ቅዳሜ፣ ነሐሴ 19 2004በሙስና የተዘፈቀው እና ድጋፍ ያጣው የሶማሊያ የሽግግር መንግስት ያለፈው ሰኞ ያከትማል ተብሎ ነበር። በዕለቱም የታቀደዉየሶማሊያፕሬዝደንትምርጫ ሳይካሄድ ቀርቷል። በሶማሊያ ጉዳዮች ላይ ጥናትና ምርምር የሚያካሂድ ተቋም ሃላፊ ጅብሪል አብዱል ምርጫው ከሚካሄድበት ቀን በፊት በሰጡት አስተያየት ምርጫው እንደሚዘገይ ነበር ለዶይቸ ቬለ የገለፁት። የምክርቤትአባላትምርጫውየተቀመጡትንመስፈርቶችያሟላአልነበረም ነው ያሉት።
ምክር ቤቱ ከሰኞ ጀምሮ ስብሰባ ጀምሯል። የመንግስት አመሰራረቱ የተወሰኑ ሳምንታት እንደሚፈጅ ነው የሚነገረው። መቼ ከሚለው ጥያቄ ውጪ አነጋጋሪው ማን ፕሬዚደንት ይሆናል የሚለው ነው።
ኤርፉርት ጀርመን በሚገኘዉ በማክስ-ፕላንክ የጥናት ተቋም የሶማሊያ ጉዳይ ተንታኝ ማርኩስ ሆነ እንደሚሉት መቼም ይሁን መቼ በፕረዚዳንትነት የሚመረጡት ሰው አሁንም በስልጣን ላይ የሚገኙ እንደሚሆን ነው። ሼክ ሸሪፍ አህመድ አንዱ እጩ ናቸው።
« ብዙ ምንጮች ስላሏቸው እድላቸው ሰፊ ነው። ሌላም ሊሆን ይችላል ውድድሩን የሚፈፅመው ይሁንና አዲስ ሰው ውድድሩን ይፈፅማል ብዬ አላስብም። ምናልባት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር፣ ሌሎች ባለፉት አመታት የተለዋወጡ በርካታ ሰዎች አሉ። ብቻ አዲስ ንፁህ የሆነ እና በዚህ በሙስና ወቀሳ ውስጥ ያልተካተተ ሰው ይመረጣል ብዬ አልገምትም። ይህ ቢሆን በጣም ነው የሚገርመኝ። ምናልባት ይህ አንድ ጥሩ ዜና ነበር። »
ግን ምንም እንኳን አዲስ ሰው ቢመረጥ ተመልሶ ሙስና ከተዋኃዳቸው ጋ ስለሚቀላቀል የሶማሊያ የወደፊት እጣ ቀላል እንደማይሆን ነው። ተንታኙ የገለፁት።
አዲሱ ህገ መንግስት በሸሪያ ህግ ላይ የተመረኮዘ ነው። ግብፅ፣ ቱርክ ፣ ካታር በሶማሊያ ላይ ተፅዕኖ እንደሚያደርጉም ይነገራል። አገሪቷ ወግ አጥባቂ የሙስሊም አገር ከሆነች የምዕራቡን አገር የሚያሳስበው ጉዳይ ነው የሚል ትንታኔ ወቶ ነበር። በዚህ ላይ ማርኩስ ሆነ ተጠይቀው ሲመልሱ፤
« እንደኔ አመለካከት ፤ ሙስና ውስጥ ሰርገው ያልገቡ እና እንብዛም በሰብዓዊ መብት ጥሰት ውስጥ ያልተካተቱት እነሱ ለዘብተኛ ሙስሊሞች ናቸው። እዚህ ላይ አሸባብን ወይም የነሱን አጋሮች ማለቴ አይደለም፤ ሌሎች አሉ በርካታ ወግ አጥባቂ ሙስሊሞች ጥቃትን የሚቃወሙ፤ ለምሳሌ አሊ ፍላህ፤ ከግብፅ ሙስሊም ወንድማማቾች ጋ ጥብቅ ግንኙነት አላቸው፤ ሆኖም ሶማሊያ ውስጥ ለውጥ ካሳዩት ቡድኖች አንዱ ናቸው። በተለይ በትምህርት እና ወላጅ አልባ ልጆች በመርዳቱ ረገድ ለውጥ ያመጡ! እኔ በበኬሌ አሊ ፍላህ ወይንም የሆነ ይህንን መንገድ የሚራመድ ሰው ኃይል ቢይዝ - ለምዕብራባዊያን ርግጥም ሙስሊም ነው። ሆኖም ለሶማሊያ ጥሩ ዜና ነበር። ማጋነን አያስፈልግም። ሶማሊያ 100 ከመቶ የሙስሊም ሀገር ናት!
ያለፈው ሳምንት መጀመሪያ አዲስ የአንድነት መንግስት የመሰረተችው ምዕራብ አፍሪቃዊት ሀገር ማሊ፤ ከአዲሱ መንግስት ብዙ ትጠብቃለች። አዲሱ የማሊ የአንድነት መንግሥት ዋነኛው ተግባሩ በአክራሪ ሙስሊሞች እጅ የወደቀውን ሰሜን ማሊን መልሶ መያዝ መሆኑን አዲሱ የማሊ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቲማን ኮሊባሊ ማክሰኞ ዕለት ተናግረዋል። « ሰሜን ማሊን ከገባችበች ጭለማ ማውጣት ቅድሚያ የሚሰጠው ነው» ነው ያሉት ። በመጋቢት ወር በማሊ ከነበረው መፈንቅለ መንግስት በኋላ ከአልቃይዳ ጋ ግንኙነት አለው የሚባለው አክራሪ ሸማቂ እና የቱዓሬግ አማፂያን ፤ሰሜን ማሊን ተቆጣጥረው ሐገሪቱን ከፋፍለዋል።
የመጀመሪያው የሽግግር መንግስት በአገሪቱ አብዛኛ ክፍል ተቀባይነት አልነበረውም። የቱዓሬግ አማፂያን እና ሙስሊም ተዋጊዎች በአገሪቱ ያለውን አለመረጋጋት ተጠቅመውበታል። ይህም ለመጀመሪያው የሽግግር መንግስት አመፁ ከአቅሙ በላይ ሆኖበት ቆይቷል።
በምእራብ አፍሪቃ የምጣኔ ሃብት ማህበረሰብ ፤ በምህፃሩ ECOWAS አሳሳቢነት የተመሰረተው የማሊ አዲስ መንግሥት 31 ሚኒስትሮች አሉት። ከነዚህ ውስጥ ግማሹ በመጀመሪያው የሽግግር መንግስት ያገለግሉ ናቸው። ከዚህ መንግስት አዲስ ነገር ቢኖር ከሁሉም የሀገሪቷ ትላላቅ የፖለቲካ ፓርቲዎች የተወከሉ ፖለቲከኞች የካቢኔ መቀመጫ (የሚንስትርነት ስልጣን) ማግኘታቸው ነው። በቡርኪናፋሶ ዮንቨርሲቲ የፖለቲካ ተንታኝ የሆኑት ሉክ ኢብሪጋ -መፈንቅለ መንግስት ካካሄዱት አራቱ አሁን የሚንስትርነት ቦታን በመያዛቸው የአገር ውስጥ መረጋጋት ሊፈጠር ይችላል የሚል እምነት አላቸው።
« ወሳኝ የሆኑት ሚኒስትሮች አሏቸው። ሰሜናዊውን ክፍል ማስመለስ መቻላቸውን እናያለን። ሌላው ደግሞ የኤክዋስን እርዳታ ይጠይቁ ይሆን ወይስ ማሊያውያን ብቻቸውን ችግራቸውን ይፈቱ እንደው ነው።»
የቱአሬግ ህዝብን የወከሉት የቱሪዝም ሚኒስትሩ ኦስማኔ አግ ሪሳ ናቸው። እሳቸውም በሰሜናዊ ማሊ በርካታ ወሳኝ ሰዎችን እንደሚያውቁ እና ከአማፂዎቹ ጋ መደራደር እንደሚችሉ በቅርብ የሚያውቋቸው ሰዎች ለዶይቸ ቬለ ገልፀዋል።
በአዲሱ የብሔራዊ አንድነት መንግስት ውስጥ ግን ዋና ዋና የሙስሊሙ ቡድን ተጠሪዎች አልተካተቱም። ይህ ደካማ ጎናቸው ይሆናል ይላሉ ቻርለት ሄይል- በጀርመን GIGA ተቋም የምዕራብ አፍሪቃ ጉዳይ ተንታኝ፤ « በአካባቢው አንድነት እስኪመለስ እና መረጋጋት እስኪሰፍን ለማሊ ረዥም ጎዳና ነው። ፈጣን ስኬቶችን በርግጥ በቶሎ መጠበቅ አይቻልም። ከመጀመሪያው ከሽግግር መንግስት የተሻለ የመደራደር ብቃት ያለው ተስፋ የሚጣልበት መንግስት መመስረቱ ራሱ የመጀመሪያው ርምጃ ነው።»
በሰሜናዊ የማሊ ክፍል አሁንም ሁኔታው አልተረጋጋም። አክራሪው የሙስሊም ቡድን ከሮቡ ጀምሮ፤ የምዕራባዊያን ሙዚቃ በሬዲዮ እንዳይተላለፍ ከልክሏል። የቡድኑ ቃል አቀባይ ኦሳማ ኦልድ አብደል ቃድር ለፈረንሳይ ዜና አገልግሎት እንደገለፀው « ሰይጣናዊ» ሙዚቃ ማብቃት አለበት ፤ በዚህ ፋንታ የቁራን ጥቅሶች ይደመጣሉ ሲል አስታውቋል።
ደቡብ አፍሪቃ ዛሬም በድንጋጤ ላይ ትገኛለች። የደቡብ አፍሪቃ ፖሊስ ባለፈው ሳምንት አድማ በመቱ ሎንማይን በተሰኘው የብሪታንያ የማዕድን ኩባንያ ሠራተኞች ላይ
ተኩስ ከፍቶ 34 ሠራተኞች በጥይት መገደላቸው ይታወሳል። በዚህም ሳምንት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍል ለሞቱት የመታሰቢያ ሀዘን ሲካሄድ ቆይቷል።
በመታሰበያ ስነ ስርዓቱ ተገኝተው ንግግር ያደረጉ፤ ባለስልጣናት፣ የሐይማኖት አባቶችም ይሁኑ የቤተሰቡ አባላት ችግሩ በሰላም እንዲፈታ ጥሪ አቅርበዋል። ከሳምንቱ መጀመሪያ አንስቶ በማዕድን ማውጫው የተገኙት የሚኒስትር መስሪያ ቤቶች የጋራ ኮሚቴ ሊቀመንበር ኃላፊ ኮሊንስ ቻባኔ ችግሩ መፍትሄ እንዲያገኝ ጥሪ ሲያቀርቡ፤« ይህ ለደቡብ አፍሪቃ አሳዛኝ ቀን ነው። በአንድ ላይ በመሆን ቀሪ ቤተሰቦችን እና በህክምና ላይ የሚገኙትን እንተባበራቸው እና ለሰላም እንስራ።»
ፖሊስ በማዕድን አውጪ ሰራተኞች ላይ በተከፈተው ተኩስ ከሞቱት ሌላ 78 የሚደርሱ ሰዎች ቆስለዋል። ከሟቾቹ 28ቱ የኢምታታ ነዋሪዎች ነበሩ። በዚህ እና በጆሀንስበርግ እንዲሁም በሺዎች የሚቆጠሩ በተገኙበት ማሪካና፤ ሰዎች በሀዘን ተሞልተው ነበር።
ከማዕድን አውጪ ቤተሰብ ፤ ኖንታማዞ ምቴምቡ የሎንማይን ኩባንያ ለቤተሰቡ አስተዳዳሪ ለነበሩት ቀሪ ቤተሰቦች ካሳ እንዲከፍል ጠይቀዋል። «ፀሎቴ የተጠቂ ቤተሰብ አባላት በሙሉ ከማዕድን ኩባንያው እና ከባለስልጣናቱ ድጋፍ እንዲያገኙ ነው። እነዚህን ቤተሰቦች መመልከት የሚያሳዝን ነው።»
የካሳ ጥያቄ ብቻ አይደለም የደቡብ አፍሪቃን ህዝብ እያነጋገረ ያለው። የማዕድን ቆፋሪዎቹ ለምን ተገደሉ? ዋናው ርዕስ ነው። የደቡብ አፍሪቃው ፕሬዚዳንት ጄኮብ ዙማ ጉዳዩን የሚከታተል የገለልተኛ ኮሚቴ ስም ዝርዝር ይፋ አድርገዋል። «ኮሚቴው መስሪያ ቤቱ በቀጥታም ይሁን ቀጥታ ባልሆነ መንገድ የሰው ህይወት የጠፋበትን ወይንም ንብረት የወደመበትን ምክንያት ስለመሆኑ ይመረምራል።»
ሲሉ ነው ዙማ ያለፈው ሀሙስ ያስታወቁት። ይህ በእንዲህ እንዳለ የሎንማይን ማዕድን ቆፋሪዎች ፤ አስተዳደሩ የደሞዝ ጭማሬ ጥያቄያቸውን ከተቀበለ፣ የተሻሻለ የስራ ሁኔታ ከፈጠረ እና ለማቾቹ የቀብር ስነስርዓት ሙሉ ድጋፍ ካደረገ፤ ሰኞ ወደ ስራ ገበታቸው እንደሚመለሱ አሳውቀዋል።
ልደት አበበ
ነጋሽ መሐመድ
መስፍን መኮንን