1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቤተ- እስራኤላዉያን ሻናቶቫ

ሐሙስ፣ ጳጉሜን 4 2013

ሻናቶቫ እንኳን ለአዲስ ዓመት አደረሳችሁ።  በዚህ ሳምንት ሰኞ ማለትም ጳጉሜ 1፤ 2013 ዓም ይሁዳዉያን 5782 ኛዉን አዲስ ዓመት ተቀብለዋል። በዓሉ በኢትዮጵያ አይሁዳዉያን ዘንድ በድምቀት ነዉ የተከበረዉ። በደቡብ ትግራይ፤ በምዕራብ ወለጋ ምኩራብ. ተሰርቶአል።

https://p.dw.com/p/408Hy
Äthiopien | Rosch ha-Schana Feierlichkeiten
ምስል Privat

ይሁዳዉያን በሳምንቱ መጀመርያ 5782 ኛዉን አዲስ ዓመት ተቀብለዋል

«በመላዉ ዓለም ለሚገኙ ቤተ እስራኤላዉያን መልካም አዲስ ዓመት እመኛለሁ። ሻናቶቫ። » ያሉት በአዲስ አበባ ነዋሪ የሆኑት የኢትዮጵያ ቤተ እስራኤላዉያን የፅዮናዊነት አራማጅ የአፍሪቃ ይሁዳዉያን የምርምር እና ጥናት ማዕከል አባል አቶ መስፍን አሰፋ ናቸዉ።

ሻናቶቫ እንኳን ለአዲስ ዓመት አደረሳችሁ።  በዚህ ሳምንት ሰኞ ማለትም ጳጉሜ 1፤ 2013 ዓም ይሁዳዉያን 5782 ኛዉን አዲስ ዓመት ተቀብለዋል። በዓሉ በኢትዮጵያ ይሁዳዉያን ዘንድ በድምቀት ነዉ የተከበረዉ ። በይብራይስጥ ቋንቋ አዲስ ዓመት  ሮሻ ሻና ይባላል። ሮሻ ሻና፤ አዲስ ዓመት፤ ብርኃን ሰረቀ ፤አዉዳመት። በአዲስ አበባ ነዋሪ የሆኑት የኢትዮጵያ ቤተ-እስራኤላዉያን የፅዮናዊነት አራማጅ የአፍሪቃ አይሁዳዉያን የምርምር እና ጥናት ማዕከል አባል አቶ መስፍን አሰፋ አዲሱን ዓመት ዘመን የምንቀይርበት ብቻ ሳይሆን አዲስ ራዓይ ተስፋ ይዘን መልካም ነገር ለማድረግ ምኞታችን ለማሳካት አዲስ ጉዞ የምንጀምርበትም ነዉ ብለዋል። ይሁንና አዲሱ ዓመትን ለመቀበል ዝግጅቱ የሚጀምረዉ ሮሻ ሻና አልያም የይሁዳዉያን አዲስ አመት ከመግባቱ አንድ ወር በፊት ነሃሴ ወር ወይም በይብራይስጥ ኤሉል ወር ጀምሮ እንደሆነ ተናግረዋል። 

Äthiopien | Rosch ha-Schana Feierlichkeiten
ምስል Privat

እስራኤል እና ኢትዮጵያ ከሚጋሯቸው ብዙ ነገሮች በተጨማሪ በተመሳሳይ ወር ውስጥ አዲስ ዓመታቸዉን ያከብራሉ። በዚህ ዓመት ደግሞ በአንድ ሳምንት ልዩነት ነዉ ሁለቱም ሃገራት አዲስ ዓመትን የሚያከብሩት ። አቶ መስፍን እንደነገሩን የእስራኤላዉያን አዲስ ዓመት የጀመረዉ በዚህ ሳምንት ሰኞ ጳጉሜ አንድ እለት ምሽት ላይ ነዉ። 

Äthiopien | Rosch ha-Schana Feierlichkeiten
ምስል Privat

አዲስ ዓመት ወይም ሮሻ ሻና በእስራኤል ወይም ይሁዳዉያን በድምቀት የሚከበር በዓል ነዉ። ሮሻ ሻና «ሮሽ« ራስ «ሻና» ዓመት የሚል ፍችም አለዉ። በኢትዮጵያ ይሁዳዉያን ወይም ቤተ-እስራኤላዉያን፤ አዲስ ዓመት ብርሃነ ሰርቀ እንደሚባልም ተመልክቶአል።  በዓሉ በእስራኤል ሦስት ዋና ነገሮችን ያካተተ ነዉ ብለዋል አቶ መስፍን።

በእስራኤላዉያን አዲስ ዓመት አከባበር ላይ ከሚካሄዱ ሃይማኖታዊ ክንዉኖች አንዱ ቀንደ መለከትን ወይም ሾፋር ይሉታል መንፋት  ነዉ ። ቀንደ መለከት መንፋት ማለት፤ አብርሃም ልጁን ይሳቅን ለፈጣሪዉ ሊሰዋ ሲል፤ አምላክ ቀናነቱን አይቶ የላከለትን ቀንዱ የዞረ በግ ለማስታወስ ነዉ ተብሎአል። በበዓሉ ላይ ቀንደ መለከቱን የሚነፉ የተካኑ የሃይማኖት ሰዎች ናቸዉ። 

በሮሻሻና ወይም በአዲስ ዓመት ብርሃን ሰረቀ ዋዜማ የሚበሉ ምግቦች ማር፤ ፖም፤ የአሳራስ ፤ ቴምር ካሮት ከዋንኞቹ መካከል ናቸዉ። እነዚህ ምግቦች በአዉዳዓመት የሚበሉት ለምሳሌ የአሳ እራስ፤ ራስ እንጂ እግር አይደለንም ለማለት፤ ማር መጭዉ ህይወት ፈጣሪ እንደማር እንዲያጣጠዉ፤ ፖም ብዙ ፍሬዎች ስላዉ ፤ ሕይወታችን እንደ ፖም ፌሪ እንዲያበዛ እና እንደማር እንዲጣፍጥ፤ ቴምር ጠንካራ ስለሆነ ጥንካሬን ለመመኘት ፤ ካሮት ደግሞ አምላክ መልካም ፍርድን እንዲያስቀምጥ ለመመኘት እንደሁ ይነገራል። አቶ መስፍን አሰፋም ይህን ይገልፃሉ። 

Äthiopien | Rosch ha-Schana Feierlichkeiten
ምስል Privat

ኢትዮጵያዉስጥ የሚገኙ ቤተ- እስራኤላዉያንም የይሁሄዳዉያንን አዲስ ዓመት በዚህ መልኩ ነዉ የሚያከብሩት?

«አዎ አብዛኞቹ በጎንደር እና በደቡብ ትግራይ ይኖሩ የነበሩ እና አሁን ወደ እየሩሳሌም እየሄዱ ያሉት ዜጎች ወይም ማኅበረሰቦች ፤ እነዚህን በአላት በስርዓት እና ሃይማኖትን በጠበቀ መልኩ ያከብራሉ። አሁንም አዲስ አበባ ጎንደርም ምዕራብ ወለጋም ያሉት እንዲሁ በዓሉን ሲካብሩ ኖረዋል አሁንም በትክክል ጠብቀዉ ያከብራሉ።»

Äthiopien | Rosch ha-Schana Feierlichkeiten
ምስል Privat

መስፍን አሰፋ የኢትዮጵያ ቤተ እስራኤላዉያን የፅዮናዊነት አራማጅ የአፍሪቃ ይሁዳዉያን የምርምር እና ጥናት ማዕከል አባል ኖት እንደዉ በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ ዉስጥ ወደ እስራኤል ለመጓዝ የሚፈልጉ ቤተ እስራኤላዉያን ስንት ይሆናለሁ?  

«በተካሄደዉ ጥናት መሰረት ከአንድ መቶ ሃምሳ እስከ ሁለት መቶ ሺህ የሚሆኑ ይሁዳዉያን ይኖራሉ።…. »

መልካም አዲስ ዓመት ፤ በአዲሱ ዓመት ሰላም ሰፍኖ ኮሮና ጠፍቶ ጤና  ሰጥቶ የዓመት ሰዉ ይበለን። ቃለ መጠይቅ የሰጡንን፤ በኢትዮጵያ የቤተ እስራኤላዉያን የፅዮናዊነት አራማጅ የአፍሪቃ ይሁዳዉያን የምርምር እና ጥናት ማዕከል አባልን እያመሰገንን ሙሉዉን ዝግጅት እንድያደምጡ እንጋብዛለን።    

 

አዜብ ታደሰ

ነጋሽ መሐመድ