1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በፋሲካ ፆም ግጥምና በገና

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 5 2009

«ዉኃ ማለት ሰዉ ነዉ፤ ሰዉ ማለትም ዉኃ፤ ንጹህ ሆኖ መጥቶ ጅረት የሚገባ፤ የሔደበት መንገድ መልኩን የሚቀርፀዉ፤ ያለፈበት ምድር የኔ ነዉ የሚለዉ፤ ሰዉ ማለት፤ ሰዉ ማለት፤ ሰዉ ማለት ዉኃ ነዉ።» አዲስ አበባ ላይ ዘንድሮ ለሦስተኛ ጊዜ «ግጥምና በገና» በተሰኘ መድረክ ከቀረበ ግጥም የተቀነጨበ ነዉ።

https://p.dw.com/p/2bDBY
Äthiopien Addis Abeba Begena Poetry
ምስል DW/Yitagesu Getenet

Kultur_13.04.17_ The begena an Eritrean and Ethiopian string instrument - MP3-Stereo

 

«ጅረት ነን፤ ጅረት ነን፤ ጅረት ነን ሥረ ምንጭ ፤የምንም መነሻ፤ የመድረክ እርጥባን፤ የባዶ መካሻ፤ የአፍላ ጋት ህላዌ፤ የሃያል ነፍስ ወንዝ ነፍሱ፤ እኛ ነን ቀለሙ የመዋብያ ቅርሱ። ከጠራ ምንጭ ፈልቀን፤ ከተዋበ አፈር ተዳቅለን የመጣን፤ አንድ ቤት አንድ ዘር፤ የመጋመድ አሃድ የጣዕሞች ልኬት ፤ የዉህዶች ህብር የመቃረብ ስሌት፤ ጅረት ነን፤ ጅረት ነን ሥረ ምንም ፤ የምንም መነሻ የመድረክ እርጥባን፤ የባዶ መካሻ»

የኢጋ ሚዲያ ድርጅት አዲስ አበባ ላይ ዓመታዊዉን ግጥምና በገና ዝግጅት ለሦስተኛ ጊዜ ሲያካሂድ ከነበረዉ ዝግጅት ላይ የተወሰደዉን ነዉ።  የየኢጋ ሚዲያ ድርጅት በባህላችን  ዉስጥ  የነበሩ መልካም እሴቶችን በዘመናዊ አኗኗራችን ዉስጥ በመተግበር የተሻለ ማንነታችን በሚገልፅ ሁኔታ አኗኗራችን መቃኘት የሚል ሃሳብ ያለዉ ድርጅት በመሆኑ ከጥንታዊ የጥበብ የባህል ቅርሶቻችን ዉስጥ በዘመናዊ አኗኗራችን ዉስጥ ምን ፋይዳ ይኖራቸዋል? የሚለዉን ማሳየት እግረ መንገዱንም መጠበቅ ወደፊትም የሚያድግበትን ሁኔታ ማመቻቸት ከሚሰራቸዉ ስራዎች መካከል መሆኑን፤ የድርጅቱ መስራች ገልፀዉልናል።  በእለቱ ዝግጅታችን የፋሲካል በዓል መዳረስን ይዘን የበገናን ምንነት እያየን፤ አዲስ አበባ ላይ ለሦስተኛ ጊዜ የተዘጋጀዉን «ግጥምና በገና» እናያለን ።

Äthiopien - 55 days of Ethiopian fasting
ምስል DW/J. Jeffrey

ባለፈዉ ሳምንት አዲስ አባባ ዋቤ ሸበሌ የተካሄደዉ ግጥምና በገና ዝግጅት አስተባባሪ አቶ ታደሰ ሺበሺ እንደገለፁልን በገናን ከሃይማኖታዊ ተግዳሮቱ በተጨማሪ በዓለማዊዉ መድረክ በተለይ ስንግጥምን በማጀብ መድረክ ላይ ሲቀርብ  ይህ ለሦስተኛ ጊዜ መሆኑን ገልፀዉልናል ።   

« ባህላዊ መሳርያ ነዉ ብለን የምናምነዉን የሙዚቃ መሳርያ በገናን፤ ከሃይማኖታዊ መልኩ በተጨማሪ በምን አይነት መልኩ ባህላዊ እሴትነቱን ማጉላት ይቻላል ፤ ብለን በማሰብ ዓለማዊ በሆነዉ መድረክ ላይ መቶ በተለያዩ ሥነ-ጽሑፍና የኪነ-ጥበብ መልኮች ላይ በመቀናበር ለሕዝብ የሚደርስበትን መንገድ ለማመመቻቸት የተካሄደ ነዉ። ሦስቱንም ጊዜ የተዘጋጀዉ ከዋቤ ሸበሌ ሆቴል ጋር በመተባበር ሲሆን በመድረኩ የማኅበረ ቅዱሳን የጎርጎርዮስ ተማሪዎች ጋር በመተባበር ዓመታዊ ዝግጅት ነዉ የተካሄደዉ። ሁለት ዓይነት መልክ ነዉ ያለዉ አንደኛዉ የበገና ድርደራዉን ስናይ፤ በሁለት መልክ ነዉ የቀረበዉ። የግል የበገና ድርደራ አለ የቡድን የበገና ድርደራ አለ። በገና በባህሪዉ ከሃይማኖት አንፃር ለመመሰጥ ለማመስገን ህመምን ለማሰብ ነዉ የሚሆነዉ። የምናመጣቸዉም ግጥሞችም በተቻለ መጠን ጮሙን ሃሳብ ዉስጥ የከተቱ፤ የይቅርታ የመቻቻል የፍቅር ሃሳቦችን በተለይ ከርግማንና ከመወቃቀስ በመጠኑም ቢሆን ይቅር መባባልን ስሜት ወደሚያመጡ ያዘነበለ ነዉ። ስለዚህm ገጣሚዎቹ ግጥሞቻቸዉን ከአጠቃላይ ጭብጡ ባልወጣ መንገድ ነዉ የሚያቀርቡት።»    

የዝግጅቱ አስተባባሪ የነበሩትና በኢትዮጵያ የደራስያን ማኅበር የቦርድ አባል ገጣሚና ደራሲ ይታገሱ ጌትነት፤ አዲስ አበባ ላይ ለሦስተኛ ጊዜ በተካሄደዉ ግጥምና በገና ዝግጅት ላይም ተካፍለዋል። 

«በመድረኩ ይቀርባሉ ብለን አስበናቸዉ የነበሩ ፕሮግራሞች በሙሉ ተከናዉነዉልናል። ከባህል ሙዚቃ ጋር ተያይዘዉ የቀረቡ ሥነ-ጽሑፎች ነበሩ። ታዋቂ ገጣምያን ስራዎቻቸዉን አቅርበዉበታል። ከዚህም ጋር ተያይዞ የማኅበረ ቅዱሳን የበገና እና የዘለሰኛ የመሰንቆ ጨዋታዎች ቀርበዋል። ወደ 24 የሚጠጉ የቡድን በገና ደርዳሪዎች ሥራቸዉን አርበዋል። ወደ 10 የሚጠጉ መሰንቆ ተጫዋቾችም በጋራ የመሰንቆ ጨዋታን አሳይተዋል። ይን ያህል ቁጥር የመሰንቆ ተጫዋች በመድረኩ ላይ ሲቀርብ የዘንድሮዉ የመጀመርያ ነዉ።

በዝግጅቱ ላይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊ ቤተ ክርስትያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምርያ ማኅበረ ቅዱሳን የጎርጎርዮስ የመሰንቆ ዘማሪዎች በግጥምና በገና መድረክ ላይ ካቀረቡት የተወሰደ ነበር። በዚህ መድረክ ላይ እንደሙከራ የቀረበ ዉሃ የተሰኘ ግጥምን እንጉርጉሮን ሙዚቃን አንድ ላይ የቀላቀለ ረዘም ያለ ለየት ያለ ግጥም ቀርቦአል።»  

Äthiopien - 55 days of Ethiopian fasting
ምስል DW/J. Jeffrey

«ምንጭ፤ ጅረት፤ ወንዝ፤ ባህር፤ ቁልቁል የምትነጥር፤ አንዲትዋ ዘለላ፤ የምትመነጭ ዉኃ አለትን ፈንቅላ፤ ንጹህ ናት፤ ድንቅ ናት ምድርን ታፀናለች፤ ሰዉና አፈሩን በአንድ ትገምዳለች። ዉኃ ማለት ሰዉ ነዉ፤ ሰዉ ማለትም ዉኃ፤ ንጹህ ሆኖ መጥቶ ጅረት የሚገባ፤ የሔደበት መንገድ መልኩን የሚቀርፀዉ፤ ያለፈበት ምድር የኔ ነዉ የሚለዉ፤ ሰዉ ማለት፤ ሰዉ ማለት፤ ሰዉ ማለት ዉኃ ነዉ። የአደሱ ሽታ የአፈሩ ቀለም፤ መዋብያዉ ነዉ እንጂ ተፈጥሮዉ አይደለም። ሺ፤ ሺ አፍላጋድ፤ አንድ ሺ አፍላጋድ፤ አንድ ሺህ ጅረቶች፤ አንድ ሽ ወንዛ ወንዝ ሚሊየን ፈሳሾች ሃያል የሚባሉት የሚባሉት ታላቅ፤ ወደታች ወርደዉ ነዉ አይደለም በመላቅ።»  ግጥምና በገና መድረክ ላይ ዉኃ ከተሰኘዉ ሙዚቃን እንጉርጉሮን ካካተተዉ ግጥም የተወሰደ ነዉ።

በመድረኩ በገና ሲቀርብ መንፈሳዊነቱን ለማሳየት ሳይሆን ባህላዊ እሴቱ ተጠብቆ መዝለቁን ለማሳየት ነዉ ያሉን አቶ ይታገሱ በአሁኑ ጊዜ ከሁለት ሺህ በላይ በገና ደርዳሪዎች እንዳሉ ተናግረዋል።

« መድረኩ በፍጹም መንፈሳዊ መድረክ አይደለም። ይህ መድረክ ሲዘጋጅ የተፈለገዉ ነገር፤ በሃገራችን ትልልቅ እና ረጅም ዘመናት የኖሩ ሃብቶቻችን እንደቀልድ እያጣናቸዉ ነዉ ለምሳሌ በገናን ወደኋላ ስድስት ዓመት ወይም አስር ዓመት በፊት አንድ ሰዉ ወይም አስር ሰዎች ብቻ ቀሩ ከዚህ በኋላ ምንም ተስፋ የለንም የሚሉ ሃሳቦች ነበሩ። ግን ከዝያ በኋላ በነበረዉ እንቅስቃሴ አሁን ከሁለት ሺህ በላይ የበገና ደርዳሪዎች መፈጠር ችለዋል። ስለዚህ ምንጊዜም ተስፋ መቁረጥ እንደሌለብን ከሰራንባቸዉ የሚሞቱ እሴቶች እንደሌሉን ልንታደጋቸዉ እንደምንችል የምናስተምርበት መድረክ ነዉ። ከእነዚህ ፕሮግራም የተመረጠዉና በዚህ ፕሮግራም የምናቅፈዉ እንደማሳያ የምንጠቀመዉ አንዱ በገናን ነዉ። ስለዚህ ግጥምና በጋና የሚለዉ እነዚህ ሁለቱን በማጣመር ለባህል ለአስተሳሰቦቻችን ትንሳኤዎች እንዳሉ የሚያመላክት መድረክ ነዉ መፍጠር የፈለግለዉ። በገናዉስጥ ያሉ አዳዲስ ዝማሪዎች መንፈሳዊም ሊሆኑ ይችላሉ፤ ሊቀርቡ ይችላሉ። ዋናዉ የኛ ጉዳይ የበገናን ትንሳኤ ማሳየት እንጂ የበገናን መንፈሳዊነት ማሳየት አይደለም። ግን መንፈሳዊ ሃብትነቱን ጠብቆ ለሱ የሚያስፈልጉት ክብሮችና ስርዓቶች እንደተጠበቁ ሆነዉ ለምሳሌ የፆም ወራት በመሆኑ በገና ሲደረደር ከበሮ አይመታም ፤ ለበገናዉ ክብር ሲባል። አለማዊ የሆኑ ግጥሞችም ሆነ ዓለማዊ የሆኑ ሃሳቦች ቀርበዋል፤ ግን እነዚህ ሃሳቦች ዓለማዊ እንበላቸዉ እንጂ ሥለ-አንድነት ሥለ-ሕብረት፤ ሥለ-መተጋገዝ ስለፍቅር ሥለ-ሃገር የሚሰብኩ ናቸዉ»  በሰሜን አሜሪካ ነዋሪ የሆኑት አቶ ይርጋላም ጎበዜ በኢትዮጵያ ኃሪክ እና እና የኢትዮጵያ ቅርስ ላይ በግል ምርምር ያደርጋሉ። በገና ይላሉ፤

Äthiopien Addis Abeba Begena Poetry
ምስል DW/Yitagesu Getenet

«የሰዉ ልጆች ወደ ፈጣሪ ፀሎትና ምስጋና ማድረግ የጀመሩት፤ የአዳም የልጅጅ ልጅ ከሆነዉ ከሴም ልጅ ከሄኖክ ጀምሮ በመፀሐፍ ቅዱስ ኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ 4፤ ቁጥር 26 የተጠቀሰ ሲሆን፤ በገና የሚለዉ ቃልም ለመጀመርያ ጊዜ ተጽፎ የሚገኘዉ፤ በዚሁ በኦሪት ዘፍጥረት ፤ ምዕራፍ 4፤ ቁጥር 21 ላይ ነዉ። በገና እጅግ ይጠቀም የነበረዉ ቅዱስ ዳቂት እንደነበር ታሪክ ያስረዳል። በዚህም መሰረት በገና አገልግሎት ላይ መዋል ከጀመረ ከክርስቶስ ልደት በፊት፤ ወደ 3 ሺህ ዓመት ሲሆነዉ ከክርስቶስ ልደት በኋላ 2017 በድምሩ ወደ 5 ሺህ ዘመን ይደርሳል። በገና ወደ ኢትዮጵያ የገባዉ በንግሥተ ሳባ ዘመን እንደነበር ታሪክ ያሳያል የንግሥተ ሳባ ልጅ ቀዳማዊ ምኒሊክ አባቱ ንጉስ ሰለሞን ዘንድ ሄዶ ወደ ሃገሩ ወደ ኢትዮጵያ ሲመለስ አብረዉት ወደ እስራኤል ከመጡ ጠበብትና ልዩ ልዩ ቁሳቁሶችና ስጦታዎች አንዱ እንደሆነ ነዉ የሚታወቀዉ።      

ስለቤተ ክህነት ጉዳዮች በቅርበት የሚያዉቀዉ ጋዜጠኛ ንጉሴ አክሊሉ በገናን ወዲህም የፋሲካን ፆም በዓል አያይዘህ ስለበገና የምትለን ካለ አልነዉ። በክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ ዛሬ ፀሎተ ሃሙስ ነዉ ሲል ቃለ ምልልሱን የጀመረዉ ጋዜጠኛ ንጉሴ አክሊሉ  

በኢትዮጵያ ስቅለትም ሆነ የትንሳዔ የፋሲካ በዓል የሚከበረዉ በሁሉም የክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ መሆኑን ገልፆአል። ሙሉ ቃለ ምልልሱን የድምጽ ማዕቀፉን በመጫን እንዲከታተሉ እንጋብዛለን።

አዜብ ታደሰ

ኂሩት መለሰ