1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የበጎ ፍቃደኞች አስተባባሪው መላኩ ኃይሉ

ዓርብ፣ መጋቢት 20 2011

ወጣቶች በምን መልኩ እና እንዴት በበጎ ፍቃደኛ ስራዎች መሳተፍ ይችላሉ? በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችን አስተባብሬያለሁ ከሚለው ወጣት መላኩ ኃይሉ ምላሽ ይኖረናል።

https://p.dw.com/p/3FrbL
Melaku Hailu Äthiopien
ምስል privat

የበጎ ፍቃደኞች አስተባባሪ መላኩ ኃይሉ

ላለፉት ስምንት አመታት በተለያዩ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ስር በጎ ፍቃደኞችን እያስተባበረ የሚገኘው መላኩ ኃይሉ የማህበረሰብ ጥናት ምሩቅ ነው። «ለኔ በጎ ፍቃደኝነት ማለት አንድ ሰው አቅም ችሎታውን እና ያለውን ለሌሎች አሳልፎ ሲሰጥ ነው።» በጎ ፈቃደኞች ለሀገራቸው የሚያበረክቱት አስተዋፅዎ በገንዘብ ቢለካ እጅግ ከፍተኛ ሊሆን እንደሚችል ነው መላኩ ዩናይትድ ስቴትስን በምሳሌነት በመጥቀስ የሚያስረዳው። ለዚህም ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ የበጎ አድራጎት ማዕከላት መቋቋም እንዳለባቸው ወጣቱ ያሳስባል። በግሉ የመገናኛ ብዙኃንን በተለይም የማህበራዊ የመገናኛ ዘዴዎችን ተጠቅሞ ሰዎች ስለ በጎ ፈቃደኝነት ያላቸውን አመለካከት እንዲለውጡ ወይም እንዲያዳብሩ ብዙ ሚና በመጫወት ላይ እንደሚገኝ ይናገራል።«ሴቶች፣ ጡረተኞች፣ ነጮች ብቻ ናቸው በጎ ፈቃደኞች የሚሆኑት ብለው የሚያምኑ አሉ። ስለዚህ ወጣቶች ስለ በጎ ፈቃደኝነት ግንዛቤ እንዲኖራቸው አደርጋለሁ። በጣም በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ጊዜዬን እውቀቴን እና ገንዘቤን አፍስሼበታለሁ። ይህም ነገ የተሻሉ ወጣቶች ይመጣሉ ብዬ ስለማምን ነው።»

በጎ ፍቃደኝነት ያለ ክፍያ የሚደረግ ስራ ስለሆነ ብዙ የማሳመን ሥራ ይጠይቃል። ይህ ብቻ አይደለም። መላኩ እንደሚለው ሌሎች ፈተናዎችም አሉት። «በጎ ፍቃደኛ ሲኮን በጣም ትግስተኛ መሆን ያስፈልጋል። ብዙ ነገሮች ተፈጥሮብኛል። ያ ግን የበለጠ እራሴን አጠንክሬ ችግሮችን እንዲቋቋም አድርጎኛል።»

 

Melaku Hailu Äthiopien
ምስል DW/H. Tiruneh

የ25 ዓመቱ የዩንቨርስቲ ምሩቅ ቋሚ ስራ እስከሚያገኝ ድረስ በአሁኑ ሰዓት ሙሉ ሰዓቱን በጎ ፍቃደኞችን በማስተባበር ላይ እንደሚያውል ገልፆልናል።  ምንም እንኳን በጎ ፍቃደኝነት ዋና አላማው ሌሎችን ያለ ክፍያ ማገልገል ቢሆንም በጎ አድራጊዎቹም በሌላ ጎን ተጠቃሚ መሆን እንደሚችሉ በኢንተርኔት ገፆቹ  ያመላክታል መላኩ። «ለምንድን ነው ሳይከፈልህ የምትሰራው ለምንድነው ጊዜህን የምታቃጥለው የሚሉ አሉ። ስለዚህ በጎ ፍቃደኝነትን ማበረታታት ስለምፈልግ የራሴ ገፅ አለኝ። ከ 4000 በላይ ተከታዮች አሉኝ። እኔ የምሰራቸውን ነገሮች፣ ቪዲዮም ሆነ ቃለ መጠይቅ እዛ ላይ አጋራቸዋለሁ። ያ ለሌሎቹ ትምህርት እንዲሆን።»የበጎ ፈቃደኝነት ስራን በተመለከተ ለረዥም ዓመታት በነፃ ካገለገለው እና ሌሎችንም ከሚያስተባብረው መላኩ ኃይሉ ጋር የነበረን ሙሉ ቆይታ በድምፅ መከታተል ይችላሉ።

ልደት አበበ

ሂሩት መለሰ