የበጎ ፍቃደኞች አስተባባሪው መላኩ ኃይሉ
ዓርብ፣ መጋቢት 20 2011ላለፉት ስምንት አመታት በተለያዩ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ስር በጎ ፍቃደኞችን እያስተባበረ የሚገኘው መላኩ ኃይሉ የማህበረሰብ ጥናት ምሩቅ ነው። «ለኔ በጎ ፍቃደኝነት ማለት አንድ ሰው አቅም ችሎታውን እና ያለውን ለሌሎች አሳልፎ ሲሰጥ ነው።» በጎ ፈቃደኞች ለሀገራቸው የሚያበረክቱት አስተዋፅዎ በገንዘብ ቢለካ እጅግ ከፍተኛ ሊሆን እንደሚችል ነው መላኩ ዩናይትድ ስቴትስን በምሳሌነት በመጥቀስ የሚያስረዳው። ለዚህም ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ የበጎ አድራጎት ማዕከላት መቋቋም እንዳለባቸው ወጣቱ ያሳስባል። በግሉ የመገናኛ ብዙኃንን በተለይም የማህበራዊ የመገናኛ ዘዴዎችን ተጠቅሞ ሰዎች ስለ በጎ ፈቃደኝነት ያላቸውን አመለካከት እንዲለውጡ ወይም እንዲያዳብሩ ብዙ ሚና በመጫወት ላይ እንደሚገኝ ይናገራል።«ሴቶች፣ ጡረተኞች፣ ነጮች ብቻ ናቸው በጎ ፈቃደኞች የሚሆኑት ብለው የሚያምኑ አሉ። ስለዚህ ወጣቶች ስለ በጎ ፈቃደኝነት ግንዛቤ እንዲኖራቸው አደርጋለሁ። በጣም በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ጊዜዬን እውቀቴን እና ገንዘቤን አፍስሼበታለሁ። ይህም ነገ የተሻሉ ወጣቶች ይመጣሉ ብዬ ስለማምን ነው።»
በጎ ፍቃደኝነት ያለ ክፍያ የሚደረግ ስራ ስለሆነ ብዙ የማሳመን ሥራ ይጠይቃል። ይህ ብቻ አይደለም። መላኩ እንደሚለው ሌሎች ፈተናዎችም አሉት። «በጎ ፍቃደኛ ሲኮን በጣም ትግስተኛ መሆን ያስፈልጋል። ብዙ ነገሮች ተፈጥሮብኛል። ያ ግን የበለጠ እራሴን አጠንክሬ ችግሮችን እንዲቋቋም አድርጎኛል።»
የ25 ዓመቱ የዩንቨርስቲ ምሩቅ ቋሚ ስራ እስከሚያገኝ ድረስ በአሁኑ ሰዓት ሙሉ ሰዓቱን በጎ ፍቃደኞችን በማስተባበር ላይ እንደሚያውል ገልፆልናል። ምንም እንኳን በጎ ፍቃደኝነት ዋና አላማው ሌሎችን ያለ ክፍያ ማገልገል ቢሆንም በጎ አድራጊዎቹም በሌላ ጎን ተጠቃሚ መሆን እንደሚችሉ በኢንተርኔት ገፆቹ ያመላክታል መላኩ። «ለምንድን ነው ሳይከፈልህ የምትሰራው ለምንድነው ጊዜህን የምታቃጥለው የሚሉ አሉ። ስለዚህ በጎ ፍቃደኝነትን ማበረታታት ስለምፈልግ የራሴ ገፅ አለኝ። ከ 4000 በላይ ተከታዮች አሉኝ። እኔ የምሰራቸውን ነገሮች፣ ቪዲዮም ሆነ ቃለ መጠይቅ እዛ ላይ አጋራቸዋለሁ። ያ ለሌሎቹ ትምህርት እንዲሆን።»የበጎ ፈቃደኝነት ስራን በተመለከተ ለረዥም ዓመታት በነፃ ካገለገለው እና ሌሎችንም ከሚያስተባብረው መላኩ ኃይሉ ጋር የነበረን ሙሉ ቆይታ በድምፅ መከታተል ይችላሉ።
ልደት አበበ
ሂሩት መለሰ