1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በካማሺ ዞን የጸጥታው ሁኔታ እየተሻሻለ ነው ተባለ

ቅዳሜ፣ መጋቢት 10 2014

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ካማሺ ዞን ለረዥም ጊዜ የቆየውን  የጸጥታ ችግር ለመፍታት የሀገር ሽግሌዎችና ሀይማኖት አባቶች ባደረጉት ጥረት  በዞኑ ባለፉት 2 ወራት አንጻራዊ ሰላም መስፈኑን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡

https://p.dw.com/p/48jH5
Karte Äthiopien AM

የካማሺ ዞን የጸጥታ ሁኔታ መሻሻሉን ተከትሎ በርካቶች ከእስር ተፈተዋል

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ካማሺ ዞን ለረዥም ጊዜ የቆየውን  የጸጥታ ችግር ለመፍታት የሀገር ሽግሌዎችና ሀይማኖት አባቶች ባደረጉት ጥረት  በዞኑ ባለፉት 2 ወራት አንጻራዊ ሰላም መስፈኑን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ በዞኑ ታጥቀው ወደ ጫቃ ሸሽተው የነበሩ ወጣቶችን  ወደ ሰላማዊ መንገድ ለመመለስ ካቀረቡት ጥያቄዎች መካከል የጉሙዝ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ(ጉህደን) የተባለ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች እንዲፈቱ የሚል ሲሆን ፖለቲከኞቹም በአሁኑ ጊዜ ከእስር ተፈተው በዞኑ በቅርቡ ለማካሄድ በታቀደው የሰላምና የእርቅ ጉባኤ ላይ ለመሳተፍ በዝግጅ ላይ እንደሚገኙ የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ኢንስፐክተር ምስጋናው እንጅፋታ ተናግረዋል፡፡ በቅርብ ከግልገል በለስ ማረሚያ ቤት የተፈቱት የጉሙዝ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ሊቀመንበር አቶ ግራኝ ጉዴታ በበኩላቸው የፓርቲአቸው አባላትን ጨምሮ በካማሺ ዞን 300 በላይ ሰዎች ከእስር መፈታታቸውን ገልጸዋል፡፡

በካማሺ  ዞን አምስት ወረዳዎች ውስጥ ተፈጥሮ በነበረው የጸጥታ ችግር ከዚህ በፊት በአካባቢው ለተፈናቀሉ ዜጎች እርዳታ ለማድረስም ሆነ ማህበራዊ አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ አዳጋች እንደነበር የአካባቢው ነዋሪዎችና የክልሉ መንግስት ሲገልጹ ቆይቷል፡፡ ከወር በፊት በዞኑ የሀገር ሽማግለዎችና የሀይማኖት አባቶች አማካኝነት በተለያዩ ወረዳዎች ውስጥ ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ ወጣቶችን የማግባባት እና ወደ ሰላማዊ መንገድ የመመለስ ስራ መጀመራቸውን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ኢነስፐክተር ምስጋናው ኢንጅፋታ ለዲዳቢሊው ተናግረዋል፡፡ በዞኑ የታጠቁ ሐይሎች ታስረው የነበሩ  የጉሙዝ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ፓርቲ ሊቀመንበርና ሌሎችም እንዲፈቱ የሚልና የመሰረተ ልማት ጥያቄዎችን ማቅረባቸውንም አብራርተዋል፡፡ መንግስት ሰላም ለማስፈን  ወጣቶችን ጥያቄ እንደሚመልስና ታስረው የነበሩ የፖለቲካ ፓርቲዎችም መፈታታቸውን ኢንስፐክተር ምስጋናው ገልጸዋል፡፡

ሰሞኑን ከእስር የተፈቱት የጉሙዝ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ሊቀመንበር አቶ ግራኝ ጉዴታ "ህገ መንግስትን በሀይል ለመናድ" ሞክረዋል ተብሎ ተጠርጥረው ከአንድ ዓመት በላይ በግልገል በለስ ማረሚያ ቤቶት መቆታቸውን ለዲዳቢሊው አብራርተዋል፡፡ በፓርቲአቸው ስም የታሰሩ በርካታ ሰዎች አሁንም እንዳልተፈቱ ገልጸው መንግስት በካማሺ ባቀደው የሰላም ጉባኤ ላይ እንዲሳተፉ በፖለቲካ የታሰሩ ግለሰቦችም እንዲፈቱ ሀሳብ አቅርቧል፡፡  በካማሺ ዞን የሀገር ሽማግለዎች እና የሐይማኖት አባቶች የጀመሩት የእርቅና ሰላም ጉባኤ  መሰረት በማድረግ ያሶ በተባለ አንድ የዞኑ ወረዳ ውስጥ ህብረተሰቡን የማወያየት ስራ መጀመሩንም ተናግረዋል፡፡

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከሚንቀሳቀሱት ሰባት የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል በአቶ ግራኝ ጉደታ የሚመራው የጉሙዝ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ አንዱ ሲሆን በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በመሰረዙ በአሶሳ ዞን ሰኔ 14/2013 ተካሂዶ በነበረው በምርጫ ሳይሳተፍ መቅረቱንም ከፓርቲው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ በክልሉ የተለያዩ ስፍራች በተለይም በመተከል እና ካማሺ  በተፈጠሩ ጥቃቶች ጋር በተያያዘ ክስ ሲቀርብበት ይስተዋላል፡፡ ከታጣቂዎቹ ጋር ግንኙነት እንደለለው ፓርቲውም በተለያዩ ጊዜያት ሲያስተባብል ቆይቷል፡፡

ነጋሳ ደሳለኝ

ታምራት ዲንሳ