1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በሰሜን ወሎ የፀጥታ ሁኔታ መባባሱ

Merga Yonas Bula
ሰኞ፣ ጥር 21 2010

በአማራ ክልል በሴሜን ወሎ ዞን በወልድያ ከተማ የጀመረዉ የፀጥታ አለመረጋጋት ቆቦ፣ ሮቢት፣ ሃርቡ፣ ጎብዬ፣ መርሳና ሲሪንቃ ከቶሞችን አዳርሷል።

https://p.dw.com/p/2rj2I
Karte Äthiopien Amhara, Tigray, Oromia Deutsch

ሰሜን ወሎ

ባለፈው ሳምንት መጨረሻ በመርሳና በሲሪንቃ በፀጥታ አለመረጋጋት ምክንያት የሰዉ ሕይወት ማለፉን፣ ብዙዎች መቁሰላቸዉንና ንብረት ላይ ጥቃት መድረሱን ዘገባዎች ያመለክታሉ። በመርሳ ስር የምትተዳደር ሃብሩ ወረዳ ዉስጥ ያሉት «ስልጣናቸዉን ያለ አግባብ ተጥቀመዋል በተባሉ አመራሮች፣ እና አለአግባብ ሰዎችን አስረዋል በተባሉ ፖሊሶች» ላይ ጥቃት መሰንዘሩንም የአከባቢዉ የአይን እማኞች ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል።

ጥቃቱ በአካባብዉ አመራሮች ላይ ብቻ የተገደበ እንዳልሆነና እኝህ የአይን እማኝ ይናገራሉ። በመርሳ አከባቢ የምገኝ የድንጋይ ማምረቻ ማሽን ድንጋዩን የምፈጨዉ በሰዎች መኖርያ አከባቢ ስለሆነ ለጤና ጠንቅ ነው ሲል ህብረተሰቡ ካሳ እንዶከፈለው መጠየቁን ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የፈለጉ የአይን እማኙ ገልጸዋል።

በዛሬዉ እለትም በመርሳ፣ በመሃል አምባ፣ በሲሪንቃና ሌሎች ቦታዎች የትራንስፖርት፣ የንግድና የባንክ አገልግሎቶች መቋረጡን እና  ዉጥረት መንገሱንም ይናገራሉ። በተመሳሳይ ሁኔታ በወልድያም ዛሬ ትልቅ ተቃዉሞ መቀስቀሱንም የከተማዋ ነዋሪዎች ያስረዳሉ። የጥያቄያቸዉ መሰረት የነበረዉ ከሕወሀት ጋር የሚተባበር ከተማዉን ለቆ እንዲወጣ የሚል እንደነበረ ሌላ የወልድያዉ የአይን እማኝ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል።

ስማቸዉ እንዳይጠቀስ  የፈለጉ ሌላ የራያ ቆቦ አከባቢ ነዋሪ እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት  መምህር በአከባቢው ትምህርት መቋረጡንም ይናገራሉ።

የአማራ ክልል የኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ሀላፊ አቶ ንጉሱ ጥላሁን ከላይ በተጠቀሱት ቦታዎች ዉስጥ የሰዎች ሕይወት ማለፉን፣ ሰዎች መቁሰላቸዉን እና ንብረት መዉደሙን ይናገራሉ። ማንነትን መሰረት ያደረገ ጥቃት የሕዝቡ አቋም አይደለም የሚሉት አቶ ንጉሱ ግን ጉዳዩ የብሄር መልክ እንዲይዝ ለማድረግ የሚጥሩ አሉ ይላሉ።

አሁን በክልሉ ያለዉ ትንቅንቅ ሕግና ስረዓት የማስጠበቅና በሌላ በኩል ደግሞ ሕግና ስረዓት እንዲደፈርስ በሚፈልጉ መካከል መሆኑን አቶ ንጉሱ ይናገራሉ።

መርጋ ዮናስ

ሂሩት መለሰ