1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በማነታረክ ላይ ያለዉ የሳት ቃጠሎ አደጋ

ዓርብ፣ ጥር 30 2000

እዚህ በጀርመን በራይን ላንድ ፋልስ ግዛት በሉድቪግስ ሃፈን ከተማ ዘጠኝ የቱርክ ተወላጆች ህይወታቸዉን ያጡበት ቃጠሎ መነሾ አሁንም አጠያያቂ ሆንዋል። የአካባቢዉ የበላይ አቃቤ ህግ ሁኔታዉን ለማጣራት ሳምንታት እንደሚፈጅ አስታዉቀዋል። የቱርኩ ጠቅላይ ሚኒስትር ሪሴፕ ጣይብ ኦርዶጋን እና የራይን ፋልስ ግዛት ተጠሪ ኩርት ቤክ ትናንት አመሻሱ ላይ የቃጠሎን ስፋራ በመጉብኘት የሃዘን መግለጫ የአበባ ጉንጉን አስቀምጠዋል።

https://p.dw.com/p/E0bg
በሉድቪግስ ሃፈን የጋየዉ ህንጻ
በሉድቪግስ ሃፈን የጋየዉ ህንጻምስል AP

ባለፈዉ እሁድ አመሻሹ ላይ በምዕራባዊ ጀርመን በሉድቪግስ ሃፈን ከተማ የቱርክ ተወላጆች ብቻ የሚኖሩበት ህንጻ ከላይ እስከታች በቅስበት ሲጋይ ጥቁር ጭስ በሚንቦለቦልበት መስኮት አዋቂዎች ጡት ያልጣ ህጻን ልጅን ለማትረፍ ከአራተኛ ፎቅ በመስኮት ወደ መሪት ሲወረዉሩት የሚያሳየዉ ዜና በአለም የብዙሃን መገናኛ ተሰራጭቶ የሚያሳዝን ስሜትን ቀስቅሶአል። ይህ በሉድቪግስ ሃፈን መሃል ከተማ ላይ በቆመዉ ህንጻ ዉስጥ ሃያ ራት የቱርክ ተወላጆች እንደሚኖሩበት በቀበሌ የተመዘገበ ቢሆንም በእለቱ በአካባቢዉ ይከበር የነበረዉን የካርናቫል ማለት የጎዳናዉን በአል በማስመልከት በእንግድነት በህንጻዉ ዉስጥ የነበረዉ ህዝብ ከስድሳ በላይ እንደነበር ተገልጾአል። ካርናባል የተሰኘዉ የአባባይ ድግስ ምክንያት ህንጻዉ አካባቢ በርካታ ህዝብ እንደ ነበር ተገልጾአል። በራድዮ ጣብያችን የቱርክ ቋንቋ ክፍል ባልደረባ የሆነዉ ሙራት ሳሊካፋ የአገሩ ህዝብ በሁኔታዉ ጥልቅ ሃዘን ላይ እንደወደቀ እና በተለይ የአገሪቷ ብዙሃን መገናኛ ይህ የዘር ጥላቻ ባለባቸዉ ጀርመናዉያን የተፈጸመ መሆኑን ያለ ማቋረጥ በመዘገብ ላይ መሆኑን ይጠቅሳል።

«በዚህ ቃጠሎ ሰበብ የተቀሰቀሰ ሁለት አይነት ሃሳብ አለ። አንዱ የቱርክ የብዙሃን መገናኛ ዘዴ ማለት ራድዮ፣ ቴሌቭዝን እንዲሁም ጋዜጦች ወንጀሉ የተፈጸመዉ በዘር ትላቻ ምክንያት ነዉ በማለት በመዘገብ ላይ ናቸዉ። በሌላ በኩል ታዋቂዋ የቱርክ ተወላጅ የሆኑት የጀርመን የምክር ቤት አባል ላላ አክጉን እንዲህ አይነቱ ፍርደ ገምድል አይነት አስተሳሰብ ትክክል እንዳልሆነ ይቃወማሉ»


እንደ ጋዜጠኛ ሙራት አገላለጽ፣ የቱርክ ተወላጆች በጀርመን አገር ባልታወቀ ምክንያት በቃጠሎ ህይወታቸዉን ሲያጡ የመጀመርያ አይደለም ነዉ። የዛሪ 16 አመት በሰሜናዊ ጀርመን ሞለን በምትባለዉ ከተማ በአንድ መኖርያ ቤት ላይ በተነሳ ቃጠሎ ሶስት የቱርክ ተወላጆች ህይወታቸዉን አጥተዋል። አንድ አመት ዘግየት ብሎ ደግሞ በዚሁ በኖርዝ ዊስት ፋልያ ግዛት ሶሊገን ከተማ በተመሳሳይ በተቀሰቀሰ የቤት ቃጠሎ አምስት የቱርክ ተወላጆች ህይወታቸዉን አትተዋል ሲል ገልጾአል።

የዛሪ አምስት ቀን በሉድቪግስ ሃፈን አምስት ህጻናት እና አራት አዋቂዎች ህይወታቸዉን ያጡበት የእሳት አደጋ ተከላካዮችን ጨምሮ ከስድሳ በላይ ሰዎች ጉዳት ላይ የወደቁበት የእሳት አደጋ መንስኤ በቴክኒክ ችግር ምክንያት ወይም ይሁን ተብሎ የተጫረ መሆኑ አልታወቀም። ዘጠኝ አመት እድሜ የሚሆናቸዉ ሁለት ሴት ልጆች እሳቱን የጫረዉን ሰዉ አይተናል ሲሉ ለብዙሃን መገናኛ ቃላቸዉን መስጠታቸዉ ተገልጾአል። ጀርመናዉያን የአደጋዉን መንስኤ ለማጣራት ሌት ከቀን በመስራት ላይ መሆናቸዉ ቢገለጽም ቱርክ የራስዋን አንድ መርማሪ ቡድን ወደ ስፍራዉ መላክዋ ምርመራዉ በትክክል ለመካሄዱ ቱርክ በጀርመን ላይ ጥርጣሪ አላት በሚል የጀርመንን ፖለቲከኞች ትንሽ ቅር ያሰኘ ይመስላል ጋዜጠኛ ሙራትም አስተያየት አለዉ

«ለካለ መጠን ያልደረሰች ሴት ደፍረሃል በሚል በአንካራ ለዘጠኝ ወራት በእስር ላይ የቆየዉ የጀርመናዊዉ ወጣት ማርኮ ጉዳይ ተጠቃሽ ነዉ። ጀርመን ይህን ወንጀል ለማጣራት የራስዋ የሆነ መርማሪ ቡድን መላክዋ ይታወሳል። ቱርክም ታድያ ይህንን መሰረት በማድረግ ብድር በምድር ይመስላል የቃጠሎዉን መንስኤ የሚያጣራ መርማሪ ቡድን ልካለች። በሌላ በኩል ደግሞ ሲታይ የቱርክ መንግስት ዜጎቹ፣ ትዉልዶቹ ስለተጎዱ ለዜጎቹ መቆርቆሩን፣ በተለይ ደግሞ ከጎን መቆሙን ለማሳየት ያደረገዉ ነዉ»

የቱርኩ ጠቅላይ ሚኒስቴር በቃጠሎዉ ምክንያት ትናንት በድንገት ወደ ጀርመን ቢመጡም ቱርክ አዉሮጻዉ ህብረት ለመግባት የምታደርገዉን ድርድር ለማካሄድ ወደ ጀርመን ለመምጣት እቅድ ላይ እንደ ነበሩ ጋዜጠኛ ሙራድ ገልጾአል። በሉድቪግስ ሃፈን በደረሰዉ አሳዛኝ ቃጠሎ ሁኔታ በአሁኑ ወቅት በሁለቱ አገሮች መካከል ያለዉ ግንኙነት ዉጥረት ላይ ቢወድቅም ጠቅላይ ሚኒስትር ኦርዶጋን ህዝባቸዉ በዘር ጥላቻ ምክንያት የተፈጸመ ወንጀል ነዉ የሚል ድምዳሜ ላይ እንዳይደርስ ጥሪያቸዉን በድጋሚ አቅርበዋል።