1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቀድሞዋ ጀርመን መዲና የዛሪዋ ሳሊፊስቶች ማዕከል

ሰኞ፣ ኅዳር 8 2007

ከጀርመን ወደ 450 ጀርመናዉያን ሳላፊስቶች ወደ ሶርያ መጓዛቸዉ ተመልክቶአል። ከነዚህ መካከል ደግሞ 10 በመቶዉ የሚሆኑት ራድዮ ጣብያችን ከሚገኝበት ከቦን ከተማ መምጣታቸዉ ነዉ የተነገረዉ። የቀድሞዋ የምዕራብ ጀርመን መዲና ቦን ለምን የፅንፈኞች ማዕከል ለመሆን በቃች?

https://p.dw.com/p/1Dona
Symbolbild Islamisten in Deutschland
ምስል picture-alliance/dpa


የቀድሞዋ የምዕራብ ጀርመን መዲና ቦን ከተማ በተለይ የራይንን ወንዝ በተንተራሱት፤ በተመድ ቅርንጫፍ ቢሮ፤ በጀርመኑ የፋይናንስ ቢሮዎች፤ የታላቁን ጀርመናዊዉ የረቂቅ ሙዚቃ ሊቅ የቤትሆፈንን የሙዚቃ ስራዎች በመድረክ በማቅረብ፤ እንዲሁም በራይንዝ ወንዝ ላይ የመርከብ ላይ ድግስን በማዘጋጀት ትታወቃለች። በከቅርብ ግዜ ወዲህ ግን ቦን ከተማን በተመለከተ"ሳላፊስቶች" "አክራሪነት " "ሙስሊም አሸባሪዎች" እንዲሁም "ጀሃዲስቶች" የሚሉ ቃላቶችን ያካተቱ ርዕሰ ዜናዎች መታየትና መሰማት ጀምረዋል። ቦን ከተማ ዋና ባቡር ጣብያ ሊደርስ የነበረ የቦንብ ጥቃትን አሲረሃል የተባለ አንድ እስልምና ሃይማኖትን የተቀበለ ተጠርጣሪ ግለሰብ በዱስልዶርፍ ፍርድ ቤት ሰሞኑን ክስ ላይ ነዉ። «ቦነር አንሳይገር» በተሰኘዉ የቦን ዕለታዊ ጋዜጣ ላይ ቦንና ፅንፈኝነት በሚለዉ ርዕስ ላይ ረዘም ላለ ጊዜ የሰራዉ ጋዜጠኛ ፍራንክ ቫልኤንደር ጂሃዲስት የተባለዉ ቤካይ ሃራች እንዴት ርዕስ ሆኖ ጋዜጣ ላይ መጀመርያ እንደወጣ ያስታዉሳል። ሃራች በጎርጎረሳዉያኑ 2010 ዓ,ም ተገድሎአል። ከዝያ በፊት ስለቅዱስ ጦርነት በድረ-ገፅ ይፋ ባደረገዉ የቪዲዮ መልክት ፕሮፖጋንዳ አሰራጭቶአል። ጋዜጠኛ ፍራንክ ስለሁለቱ የቦን ወንድማማች ያሲንና ሙኒር ቱርካም ያስታዉሳሉ። እነዚህ ሁለት ወንድማማቾች አፍጋኒስታን ፓኪስታን ድንበር ላይ ሆነዉ ጀርመን ላይ ጥቃት እንዲደረግ በቪዲዮ መልክት አሰራጭተዋል።

« ቦን በብዙሃን መገናኛ ላይ በገሃድ የወጣችዉ ታነንቡሽ ሰፈር የሚኖረዉ ጀሃዲስት ቤካም ሃራሽ በድረ-ገፅ መገናኛ ላይ መልክቱን ይዞ ከወጣ በኋላ ይመስለኛል። የቦን ከተማ ነዋሪ የነበረዉ ሃራሽ በጎርጎረሳዉያኑ 2010 ዓ,ም አፍጋኒስታን ዉስጥ መሞቱ ይታወሳል። ቾካ ቢሚል መጠርያ የሚታወቁት ወንድማማቾቹ የቦን ከተማ ነዋሪዎችም ታዋቂ ጀሃዲስቶች ናቸዉ። እነዚህ ወንድማማቾች ከቦን ወደ ፓኪስታን መሄዳቸዉ፤ ከጀርመን ከተሞች የመጀመርያዎቹ ጀሃዲስቶች ከቦን መምጣታቸዉን የሚያመላክት ነዉ»

ቦን ከተማ የሳላፊስቶች ማዕከል በመሆንዋ የከተማዋ የፍልሰት ጉዳይ ኃላፊ ላይ ትልቅ ጫናን ፈጥሯል። ይህን ጉዳይ በተመለከተ የከተማዋ ፍልሰት ጉዳይ ቢሮ ተጠሪ ኮሌታ ማነማን ከፍተኛ ስጋት እንዳላቸዉ ይገልፃሉ። በተለይ ይላሉ ማነማን ወጣት ወንዶች ወደ አክራሪ ቡድኖች እየተሳቡ መግባታቸዉ ችግሩን አጉልቶታል። በዚህም ሃይማኖቱ ላይ ጥላቻ እያደረ መምጣቱ አሳስቦአቸዋል። የምዕራብ ጀርመን መዲና የነበረችዉ ከቀድሞ ጀምሮ መስጂዶች በብዛት ይገኙባታል። ይህ የሆነዉ ደግሞ የአረብ ሃገር ኤንባሴዎች ሰራተኞቻቸዉ የፀሎት ቤት እንዲኖራቸዉ በመሻታቸዉ በከተማይቱ በርካታ መሳጎዶች ለመገንባት በቅተዋል። ከነዚህ መስጂዶች በአንዳንዶቹ ዉስ አሁን ደግሞ የፅንፈኞች መገናኛ ለመሆን መብቃቱና ቦን ከተማ ሰላፊስቶች መረባቸዉን ሊዘረጉ መቻላቸዉ ተመልክቶአል። ጋዜጠኛ ፍራንክ ቫልኤንደርም ይህ ረዘም ያለ ታሪክ እንዳለዉ ይገልፃሉ፤

« በ90 ዎቹ ዓመታት የንጉስ ፋድ አካዳሚ ተቋቋመ። በዚህም በርካታ የሃይማኖቱ ወግ አጥባቂዎችም ተከታዮች ተፈጠሩ። በዚሁ ትምህርት ቤት አቅራቢያ ከተለያዩ የዓረብ ሃገራት የመጡ የእስልምና ሃይማኖትን የሚከተሉ ቤተሰቦችም መኖር ጀመሩ።»

በዚህም ምክንያት በቦን ከተማ አረብኛ ቋንቋ ከጀርመንኛ ቀጥሎ በሁለተኛ ደረጃ በብዛት የሚነገር ቋንቋ ነዉ። ይህን ተከትሎ በተለይ በደቡባዊዉ ባድ ጎድስበርግ የቦን ክፍለ- ከተማ በአረብኛ ቋንቋ ብቻ የሚችል ሰዉ ያለምንም መግባባት ይቻላል። በዚህም ምክንያት ከተለያዩ ዓረብ ሃገራት ለህክምና ወደ ጀርመን የሚመጡ ታካሚዎች ቦን ከተማን አብዝተዉ ይመርጣሉ። የሚያሳዝነዉ ነገር ግን ይላሉ ጋዜጠኛ ፍራንክ ፋልኤንደር ፅንፈኞችም ይህችን ከተማ መምረጣቸዉ ነዉ። የጀርመን የፖሊስ መሥራያ ቤት በጎርጎረሳዉያኑ 2005 ዓ,ም በሃንቡርግ እና በኡልም ከተማ ይገኙ የነበሩ የአክራሪዎች መገናኛ ያላቸዉን ቦታዎች በይፋ ከዘጋ በኋላ ሰላፊስቶቹ ወደ ቦን እንደመጡም ተመልክቶአል።
ባድ ጎደስበር በተሰኘዉ የቦን ክፍለ ከተማ ስያምያቸዉ በአረብኛ ብቻ በጉልህ የተፃፈባቸዉ መድብሮች ፤ ምግብ ቤቶች እና ሻይ ቤቶች እንዲሁም የስልክ እና የኢንተርኔት መጠቀምያ ሱቆች በብዛት ይገኛሉ። በደቡባዊዉ የባድጎድስበርከ ክፍለ ከተማ የዉጭ ገፅታዉ መስጅድ የሚመስል «የንጉስ ፈሕድ አካዳሚ» የሚል ስያሜ ያለዉ አንድ የሳዉዲ ዓረብያ ትምህርት ቤትም ይገኛል። በከተማዋ የሰላፊስቶች አክራሪነት መስፋፋት ሲነሳ ይህ «የንጉስ ፋድ አካዳሚ» ሁሌ ተጠቃሽ ነዉ። ይህ ትምህርት ቤት ከጎርጎረሳዉያኑ 2003 ጀምሮ በተለያዩ ግዚያት በሩን ለጎብኝዎች በመክፈት ትምህርት ቤቱ ከሰላፊስቶች ነፃ መሆኑን ለማሳየት ጥረት ላይ መሆኑ ተዘግቦአል። ጥቅምት ወር መጨረሻ ላይ በሚካሄደዉ የጉብኝት ቀን ልጆች እናቶች አባቶች በጋራ በመሰባሰብና ዳቦና ሻይ በመቅመስ ሃሳብ ይቀያየራሉ። በዉይይቱ ፖለቲካዊ ማኅበራዊ ጉዳዮች እንዲሁም ስለሶርያ ኢራቅ እንዲሁም «እስላማዊ መንግሥት » የሚያካሂደዉ ጦርነት አንዱ የመነጋገርያ ርዕስ ነዉ።

Dr. Ibrahim Al-Megren König-Fahad-Akademie in Bonn
«የንጉስ ፋድ አካዳሚ» ዳይሬክተርምስል DW/M. von Hein
König-Fahad-Akademie in Bonn
«የንጉስ ፋድ አካዳሚ» የተሰኘዉ የሳዉዲ ት/ቤት በቦንምስል DW/M. von Hein
Bildergalerie Die Stadt Bonn
ቦን ከተማምስል DW/L.Tarek



ማትያስ ፎን ሃይን / አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሃመድ