1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሶማልያና ዓለም አቀፍ የጋዜጠኞች መብት ታጋይ ድርጅቶች ጩኸት፧

ማክሰኞ፣ ጥር 20 2000

እስካሁን ፀጥታዋ ሊረጋጋ ባልቻለው ሶማልያ ፧ ትናንት የአገሪቱ ዜና አገልግሎት ድርጅት ባልደረባ የነበረው ጋዜጠኛ፧ ሐሰን ካፊ ሃሬድ፧ የኬንያና የፈረንሳይ ተወላጆች ከሆኑ ሁለት ሀኪሞች፧ እንዲሁም ከአንድ ሌላ ሶማሊያዊ አውቶሞቢል አሽከርካሪ ጋር፧ ኪሳማዩ ወደብ አቅራቢያ በፈንጂ ሳቢያ መገደላቸው ታውቋል።

https://p.dw.com/p/E0Xr
እ ጎ አ ከ 1944 ዓ ም አንስቶ፧ በዓለም ዙሪያ፧ በሥራ ላይ እንዳሉ ህይወታቸውን ላጡ ጋዜጠኞች ሁሉ፧ በኖርማንዲ፧ፈረንሳይ የተቋቋመው የመታሰቢያ ሐውልት፧
እ ጎ አ ከ 1944 ዓ ም አንስቶ፧ በዓለም ዙሪያ፧ በሥራ ላይ እንዳሉ ህይወታቸውን ላጡ ጋዜጠኞች ሁሉ፧ በኖርማንዲ፧ፈረንሳይ የተቋቋመው የመታሰቢያ ሐውልት፧ምስል AP

ድርጊቱ፧ ለጋዜጠኞች መብት የሚቆረቆሩትን፧ በኒው ዮርክና በፓሪስ የሚገኙትን ሁለት ታዋቂ ዓለም አቀፍ የጋዜጠኞች ድርጅቶችን አሳዝኗል፧ አስቆጥቷልም። የሶማልያን ጋዜጠኞች ይዞታ በተመለከተ፧ ተክሌ የኋላ፧ ዋና ጽህፈት ቤቱ ፓሪስ፧ ፈረንሳይ የሚገኘውን የድንበር አያግዴውን የጋዜጠኞች ድርጅት ፧ የአፍሪቃ ቅርንጫፍ ዋና ሥራ አስኪያጅ፧ Leonard Vincent ን በስልክ አነጋግሮ የሚከተለውን ዘገባ አጠናቅሯል።
ያለፈው 2000 ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት፧ በሶማልያ ከአጠቃላዩ የፖለቲካ ወታደራዊና ማኅበራዊ ውዝግብ ተያይዞ በተለይ ጋዜጠኞች ፍዳ ያዩበትና በሰፊው የህይወት መስዋእትነት የከፈሉበት ዘመን ነበር። ዘንድሮም ቢሆን፧ የኃይል እርምጃ ሰለባዎች እንደሆኑ ናቸው። ትናንት ሐሰን ካፊ ሃሬድ የተባለው የሶማልያ ዜና አገልግሎት ድርጅት ባልደረባ የነበረ ጋዜጠኛ ኪሳማዩ ወደብ አቅራቢያ በፈንጂ ሳቢያ የኬንያና የፈረንሳይ ተወላጆች ከሆኑ ሀኪሞችና ከአንድ ሌላ ሶማሊያዊ አውቶሞቢል አሽከርካሪ ጋር ህይወቱን አጥቷል። ዋና ጽህፈት ቤቱበኒውዮርክ የሚገኘው ለጋዜጠኞች ደህንነት የሚታገለው ድርጅት (CPJ) የጋዜጠኞች መብት ይከበር ዘንድ የሚያሳስብ ደብዳቤ፧ ለጠቅላይ ሚንስትር ሐሰን ሁሴን ልኳል። ዋና ጽህፈት ቤቱ ፓሪስ፧ ፈረንሳይ የሚገኘው ድንበር አያግዴው የጋዜጠኞች ድርጅትም ኀዘኑንና ቁጣውን ባወጣው መግለጫ መግለጫ ላይ አንጻባርቋል። ድርጅቱ፧ በምን ዓይነት መንገድ የሶማልያን ጋዜጠኞች ችግር ለማቃለል መርዳት ይችላል? ለድርጅቱ የአፍሪቃ ክፍል ዋና ሥራ አስኪያጅ ለ Leonard Vincent ያቀረብኩላቸው ጥያቄ ነበር።
«አስከፊውን ሁኔታ በተመለከተ፧ የሶማልያ ጋዜጠኞች ዋስትና በሌለበት ሁኔታ ለመሥራት የተገደዱበትን ዕጣ-ፈንታ እናወግዛለን፧ ማውገዛችንን እንቀጥላለን፧ ሶማሌያውያን ጋዜጠኞች የሚሠሩበት ሁኔታ፧ እዚህ ላይ «ሥራ« ስል፧ ቃሉን በጥንቃቄ ነው ከአንደበቴ የማወጣ፧ ሥራ ሊባል የሚችል አይደለምና! ጋዜጠኞቹ በተለይ በመቅዲሹ፧ በሞትና ህይወት መካከል ነው ለህልውናቸው የሚጥሩት። በአሁኑ ጊዜ ሁኔታው እጅግ አስከፊ ከመሆኑ የተነሣ፧ እኛ ማድረግ የምንችለው፧ ድምፃችን ከፍ አፍድርገን መጮህ ነው። በመጨረሻ፧ የፖለቲካ የሃይማኖትና የኅብረተሰብመሪዎች፧ እያንዳንዱ የጋዜጠኞች ኅልውና እንዲጠበቅ፧ ማድረግ የሚችል ሁሉ መታደግ እንደሚኖርበት፧ ጉዳዩ ለሶማልያ ላቅ ያለ ግምት የሚሰጠው ብሌራዊ ብሔራዊ አጀንዳ መሆኑን ይገነዘባሉ ብለን እናስባለን።«
በአፍሪቃ መሪዎች ደረጃም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ፧ የሶማልያን ችግር ለመፍታት የጎላ ጥረት ሲደረግ አይታይም። ብዛት ያለው የውጭ ፀጥታ አስከባሪ ኃይል ቢገባም እንኳ መፍትኄ ማስገኘቱ አጠራጣሪ ነው። ታዲያ ያገሪቱን ማኅበረሰብና የፖለቲካ ኃይሎች የሚያቀራርብ ሁኔታ ባልተከሠተበት፧ ትክክለኛ የፖለቲካና የፀጥታ የመፍትኄ ተጨባጭ ሐሳብ ባልቀረበበት ሁኔታ የዚያች አገር ውዝግብ ይፈታል ብለን መጠበቅ እንችላለን?
«አይደለም? በእርግጥ፧ እያንዳንዱ ጦርነት የፖለቲካ ፍጻሜም ሆነ መደምደሚያ አለው። የሁለተኛው የዓለም ጦርነትም ቢሆን፧ ጀርመንን በስፋት በመደብደብ ብቻ ሳይሆን፧ ራሳቸው ጀርመናውያን ጭምር እንዲሳተፉ በተደረገበት የፖለቲካ መፍትኄ ነው እልባት ያገኘው።
አሁን፧ በሶማልያ፧ ሁኔታው ከዚያ የሚለይበት ይኖራል ብለን አንገምትም። እርግጥ ነው የሽግግሩ መንግሥት፧ «ከዚህ ጋር፧..ከዚያ ጋር ይነጋገር« ለማለት፧ መብቱም፧ ሥጣኑም የለንም። ከማን ጋር ሰላም መፍጠር እንዳለበት....፧ለዚህ፧ የፖለቲካ ሰዎችም ሆኑ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች አሉ።
እኛ የምንለው፧ ጦርነት እስከተካሄደ ድረስ፧ ትኩረት የሚሰጣቸው ደንቦች አሉ። እነዚህ ደንቦች ደግሞ ዕለት- ተዕለት እየተጣሱ ናቸው። የሽግግሩ መንግሥት፧ የኢትዮጵያ ወታደሮች፧ ከዚያም ሰፋ ባለ መልኩ፧ ጦርነቱን ስንመለከት በእስላማውያን አማጽያንም ደንቡ እየተጣሰ ነው። እነዚህ ተፋላሚዎች ሁሉ ሊገባቸው ያልቻለው የፕረሱ ድርሻ ነው። የሶማልያ ጋዜጠኞች፧ በአገሪቱ፧ የእርስ-በርስ ጦርነት በተፋፋመበት ዘመን በተመሠቃቀለ ሁኔታ በጎሣ ጦር አበጋዞች ተከፋፍላ በነበረችበትም ጊዜ የሶማልያ ጋዜጠኞች ብቻ ነበሩ፧ በብቸኛነት፧ ድርጅት መሥርተው፧ አገሪቱን እያስተባባሩ በአንድነት ያቆዩአት። አሁን፧ በዚህ ለአንድነት በሚያካሂዱት ዘመቻ፧ ዴሞክራሲን ለማሥፈን በሚያድጉት ትግል፧ የመጀመሪያዎቹ የጥቃት ሰለባዎች ሆነዋል። ይህ ከዐበይት የህግ ጥሰቶች ውስጥ አንዱ፧ በዝችው ሀገር በሶማልያና በቀሪው የአፍሪቃ ክፍል ያጋጠመ ዕጣ-ፈንታ ሆኗል።