1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሰርቢያ ና የአውሮፓ ህብረት

ረቡዕ፣ የካቲት 28 2004

ስርቢያ የአውሮፓ ህብረት አባል የመሆን ተሰፋዋባለፈው ሳምንት ለምልሟል ። ባለፈው ሳምንት ብራሰልስ ቤልጂየም የተካሄደው የህብረቱ አባል ሃገራት መሪዎች ጉባኤ ሰርቢያን ለህብረቱ አባልነት አጭቷል ።

https://p.dw.com/p/14G4m
ምስል Reuters

ስርቢያ የአውሮፓ ህብረት አባል የመሆን ተሰፋዋ ባለፈው ሳምንት ለምልሟል  ። ባለፈው ሳምንት ብራሰልስ ቤልጂየም የተካሄደው የህብረቱ አባል ሃገራት መሪዎች ጉባኤ ሰርቢያን ለህብረቱ አባልነት አጭቷል ። የሰርቢያ የአውሮፓ ህብረት አባልነት ተስፋ ና ቀሪ ቅድመ ግዴታዎቿ የዛሬው አወሮፓና ጀርመን ዝግጅታችን ትኩረት ነው ።

«ለሰርቢያ የአውሮፓ ህብረት የጩ አባልነት ደረጃ ለመስጠት ዛሬ ማታ ተስማምተናል ። ይህ ታላቅ ግምት  የሚስጠው ወጤት ነው ። ቤልግሬድና ፕርስቲና ባካሄዱት ውይይት ፣ በሁለቱ ወገኖች ጥረት የተገኘ ውጤት ነው  ። »

የአውሮፓ ህብረት ፕሬዝዳንት ኽርማን ፋን ሮምፖይ ባለፈው ሳምንት ብራሰልስ ቤልጂግ ውስጥ ከተካሄደው የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት መሪዎች ጉባኤ በኋላ ፣ ለሰርቢያ ና የህብረቱ አባልነቷ እንዲፋጠን ለሚፈልጉ ወገኖች ያበሰሩት መልካም ዜና ! ከመልካሙ ዜና በፊት ግን የሰርቢያ ዕጩነት ፈታኝ ሁኔታ ውስጥ ወድቆ ነበር ።

Van Rompuy trifft Tadic
ምስል picture-alliance/dpa

ሰርቢያ በሃገርዋ በሚገኙ አናሳ ሮማንያውን ላይ የሚደርስባቸውን ተፅዕኖ እንድታስወግድ ከዚህ ቀደም ከሮማንያ ጋር የተስማሙበትን ሰነድ ካልፈረመች በስተቀር ሮማንያ አባልነትዋን እንደማትቀበል ስታሳውቅ ለጊዜውም ቢሆን ተሰፋዋ ድበዝዞ ነበር ። ሆኖም ሰርቢያ ሰነዱን እንድትፈርም ከተደረገ በኋላ ጉባኤው የሰርቢያን ዕጩነት ሊያፀድቅ በቅቷል ። የአውሮፓ ህብረት ለአባልነት ያጫት የቀድሞዋ የዩጎዝላቭያ ግዛት ሰርቢያ ለህብረቱ ሙሉ አባልነት የሚያበቃት አንድ ትልቅ እርምጃ ላይ ደርሳለች ። ለዓመታት ከተካሄደ ጦርነት ና ይህም ካስክተለባት መገለል በኋላ ሃገሪቱ ለዚህ መብቃቷ በ 1990 ዎቹ በተካሄዱ ጦርነቶች ብዙ ህዝብ ባለቀበት በምዕራብ ባልካን ሀገራት ሰላም በማውረድ ረገድ  ከፍተኛ ድርሻ ይኖረዋል የሚል ተስፋ ተጥሎበታል ። የአውሮፓ ህብረት እንዳለው ሰርቢያ ለዕጩነት የሚያበቃትን መመዘኛዎች አሟልታ ነው ለአባልነት የታጨችው ። ሮዛ ባልፎር መቀመጫውን ብራሰልስ ቤልጂግ ያደረገው የአወሮፓ ፖሊሲ የጥናት ማዕከል ባልደረባ ናቸው ። በርሳቸው ግምገማ ከምዕራብ ባልካን ሃገራት በተሻለ +ደረጃ ላይ የምትገኘው ሰርቢያ ለአውሮፓ ህብረት አባልነት የተቀመጡትን ቅድመ ግዴታዎች የምታሟላ ሃገር ናት ።

Belgrad Stadtbild
ምስል picture-alliance/dpa

«ክምዕራብ ባልካን ሃገራት ሰርቢያ ምናልባትም ለዚህ መዋቅራዊ ዝግጅት ያደረገች ሃገር ናት ። ከሌሎቹ ሃገራት አጅግ የተቀላጠፈ የህዝብ አሰተዳደር አላት ። ተቋማቷ ጠንካራ ና  የኮፕንሃገኑ መመዘኛዎች የሚጠይቋችውን ልዩ ልዩ ማማሻሻያዎች ተግባራዊ የማድረግ ከፍተኛ አቀምም ያላቸው ናቸው ። በተጨማሪም እነዚህን ሃገራት ወደ ዘመናዊ ዲሞክራሲ ለማሽጋገር የተቀመጡትን ብዙ ጥረት የሚያስፈልጋቸውንና ፈጣን  ማሻሻያዎችን ማካሄድ ትችላለች  ። »

የኮፕንሃገኑ መመዘኛ አንድ ሃገር የአውሮፓ ህብረት አባል ለመሆን የሚያበቃው ደንብ ነው ። በመሰፈርቱ መሠረት አባል መሆን የሚፈልግ  ሃገር ዲሞክራሲያዊ አስተዳደር ተግባራዊ ማድረግና ሰብዓዊ መበት ማስከበር የሚያስችሉ ተቋማት ሊኖሩት ይገባል ። የገበያ ኤኮኖሚን ማራመድ እንዲሁም የአውሮፓ ህብረትን ሃላፊነቶችና ዓላማዎችም መቀበልም ይኖርበታል ። እነዚህ የአባልነት ቅድመ ግዴታዎች እጎአ ሰኔ 1993 ኮፕንህገን ዴንማርክ ውስጥ በመደንገጋችው መስፈርቶቹ የኮፕንሃገኑ መመዘኛዎች በመባል ይጠራሉ  ።

EU Serbien Tadic Barroso Brüssel Pressekonferenz PK
ምስል Reuters

ሰርቢያ ለአውሮፓ ህብረት አባልነት ማመልከቻ ስታስገባ ከቀረቡላት ቅድመ ግዴታዎች ውስጥ አንዱ በቀድሞዋ ዩጎዝላቪያ የተፈፀሙ የጦር ወንጀሎቸን ለማጣራት በተቋቋመው በሄጉ ዓላም ዓቀፍ የጦር ወንጀሎች መዳኛ ፍርድ ቤት ይፈለጉ የነበሩትን 2 ቱን ቀንደኛ የጦር መሪዎች ማስረከብ ነበር ። ሰርቢያም ተፈላጊዎቹን ራዶቫን ካራቺችንና ራትኮ ምላዲችን በተከታታይ ዓመታት ይዛ አሥራ እንዳስረከበች በአውሮፓውያኑ 2011 መጨረሻ  ማለትም በታህሳስ ወር ላይ ለህብረቱ አባልነት ትታጫለች ተብሎ እየተጠበቀ ነበር ። ምንም እንኳን ሰርቢያ  በምዕራባውያን የተጠየቀችውን ሁሉ ብታሟላም የአባልነት ጥያቄዋን እስካሁን ወደ ኋላ ያጓተተባት አንዱና ዋነኛ ቸግር ገን እሳክሁንም መፍትሄ አላገኘም ። በባልፎር ግምገማ መሠረት ሰርቢያ አሁንም ግዛቴ ናት ለምትላት ለቀድሞዋ አካልዋ ለኮሶቮ እውቅና አለመስጠትዋ ትልቁ ዕንቅፋት ነው ።  በመሠረቱ ሰርቢያ ለኮሶቮ ዕውቅና እስካልሰጠች ድረስ ደግሞ የአውሮፓ ህብረት አባል መሆን አትችልም ። 

Boris Tadic zur Verhaftung von Goran Hadzic
ምስል dapd

የአውሮፓ ህብረት ይህን ጉዳይ አንስቶ አሁን  በቀጥታ ባያናግርም ይላሉ ባልፎር የከዚህ ቀደሙን ስህተቱን ግን መድገም አይፈለግም ። እጎአ ከ1970 ዎቹ ጀምሮ የግሪክና የቱርክ ተብለው የተከፈሉት ሁለቱ ቆጵሮሶች ያቀረቡት የውህደት ጥያቄ መፍትሄ ሳያገኝ  ነበር ፣ ህብረቱ እጎአ  በ 2004 የግሪክ ቆጵሮስን የአውሮፓ ህብረት አባል ያደረገው ። በባልፎር አምነት አሁን ይህ ዓይነቱ ሁኔታ አይደገምም ።

«የአውሮፓ ህብረት የቆጵሮስ ዓይነት ችግር ሊገጥመው አይችልም ። ሰርቢያና ኮሶቮ ልዩነቶቻቸውን እስኪፈቱና ሰርቢያም በስተመጨረሻ  ለኮሶቮ እውቅና እስክትሰጥ ድረስ የአውሮፓ ህብረት ስረቢያን አባል አያደርግም ። የአውሮፓ ህብረት ይህን በማያሻማ መንገድ በግልጽ ማለት አይችልም ።ሆኖም ሁኔታው ይሄ ነው ።»

የአውሮፓ ህብረት እጎአ በ 1999 በቀድሞዋ የሰርብ ግዛት ኮሶቮ በተካሄደው ናበመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ህይወት በጠፋበት ጦርነት ምክንያት እንዲሁም ኮሶቮ  ክ 3 ዓመት በፊት ነፃነቷን በማወጇ ሰበብ የተካረረውን የሰርቢያና የኮሶቮን ፀብ  ሲሸመግል ነው የከረመው ።  ሰርቢያ ለህብረቱ ዲሞክራሲያዊ እሴቶች ተገዥ እንድትሆን ይፈልጋል ። በአካባቢውም ዘርን መሠረት ያደረገ ግጭት ዳግም እንዳይቀሰቀስ ማረጋገጥ ይሻል ። እጎአ ከ 1992 እሰከ 1995 በዘለቀው በቦስኒያው ጦርነት ፣  የቦሰኒያ ሰርቦች ከሙስሊሞችና ከክሮእቶች ጋር ባካሄዱት ውጊያ ወደ 100 ሺህ የሚጠጋ ህዝብ ህይወት እንደጠፋ ነው የሚገመተው ።

Flagen EU und Serbien
ምስል DW

በወቅቱ ሰርቢያ ፣ የቦስኒያ ስርቦችን በጦር መሣሪያና በገንዘብ ስትደግፍ ነበር ። የአውሮፓ ህብረት ከጓሮው የደረሰውን ይህን የባላካን ጦርነት ና እልቂት ለማሰቆም ተገቢውን ጥረት ባለማድረጉ አንደ አንድ ድከመት ይወስድብበታል ። አጎአ በ1990 ዎቹ  የያኔው የሰርቢያ መሪ ስሎቦዳን ሚሎሶቪች በክሮሺያ በቦስኒያ ና በኮሶቮ ላይ ጦርነት ሲከፍቱ ሰርቢያ ከህብረቱ ተግላ ነበር ።  በ 1999 NATO በኮሶቮው ጦርነት ጣልቃ ገብቶ በሰርቢያ ላይ የአየር ድብደባ ካካሄደ በኋላ ነበር ሁለቱ ወገኖች ለድርድር የተቀመጡት  ። ጦርነቱ ከቆመ ከአንድ አሥርት ዓመታት በኋላ ነው ህብረቱ የቀድሞዋን ዩጎዝላቪያ ግዛቶች ወደ ማህበሩ ማስገባት የጀመረው ። ስሎቬንያ ከቀደሞዋ የዩጎዝላቪያ ግዛቶች የህብረቱ አባል በመሆን የመጀመሪያዋ ሃገር ናት ። እጎአ በ 2004 ህብረቱን ተቀላቀለች ። ሌላዋ የቀድሞዋ የዩጎዝላቪያ ግዛት  ክሮኤሽያ  ደገሞ በሐምሌ 2013 የህብረቱ 28 ተኛ አባል እንደምትሆን ባለፈው ዓመት ይፋ ሆኗል ። እጎአ በ2008 ነፃንቷን ያወጀችው የቀድሞዋ የሰርቢያ ግዛት ኮሶቮም ክህብርቱ ጋር በፖለቲካና በኤኪኖሚ ይበልጥ የምትቀራረብበትን መንገድ ቀይሳለች ። ራስዋን ክሰርቢያ ለገነጠለችው ኮሶቮ ዩናይትድ ስቴትስን ጨምሮ ክ 80 በላይ ሀገራት እውቅና ስጥተዋል ። ከነዚህም 22 ቱ የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ናቸው ።  ከመካከላቸው 5 አባል ሃገራት እስካሁን የኮሶቮን መገንጥል አልተቀበሉም ።  ሰርብያ አሁንም ግዛቴ ናት ለምትላት ኮሶቮ እውቅና መሰጠቱን አጥብቃ እየተቃወመች ነው ። ሩስያም ሰርቢያን በመደገፋ የኮሶቮን ነፃነት ከሚቃወሙት ሃገሮች አንዷ ናት ። የኮሶቮ ጉዳይ የአውሮፓ ህብረት አባላትንም ለሁለት እንደከፈለ ነው ።  ያም ሆኖ ህብረቱ ሰርቢያንና ኮሶቮን በመሸምገሉ ጥረት ገፍቶ ባለቀ ሰዓት የቀረበ ገለጋይ ሃሳብ ሰርቢያ ለአውሮፓ ህብረት አባልነት እንድትታጭ መንገዱን ጠረጓል ። ይሁንና ባልፎር ፣ ሰርቢያ በኮሶቮ መገንጠል ያላት ቅሬታ ሳይፈታ ሁኔታ ባለበት ከቀጠለ ውጤቱ "አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ "ዓይነት መሆኑ አይቀርም ይላሉ 

« ጨለምተኛው ከሰተት ውይይቱ ወደ ሰመረ ግንኙነት የሚያመራ ቢሆንም  ሰርቢያ ለኮሶቮ እውቅና እንድትሰጥ የሚገፋፋ አለመሆኑ ነው ። በአካባቢው ያለውን ተጨባጭ ሁኔታም አይለውጠውም ። ስለዚህ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ሊገነፍል የታመቀ ሊባል የሚችል ዓይነት ውዝግብ ላይ መደረሱ አይቀርም ። ይህም በርግጥ ለአካባቢው በጣም የከፋ መዘዘዞችን  ሊያስከትል ይችላል ። እንደሚመስለኝ መዘዙ ለአውሮፓ ህብረትም ቢሆን ሊተርፍ የሚችል ነው ። »

Belgrad Wahrzeichen
ምስል picture-alliance/dpa

ሰርቢያ ለአውሮፓ ህብረት አባልነት መታጨትዋ የዋነኛውን ተቃዋሚ ፓርቲ ድጋፋ ቢያገኝም ተቃዋሚም አላጣም ። ብሔረተኞች የሃገሪቱ ፕሬዝዳንት ቦሪስ ታዲች በምዕራባውያን የተጠየቁትን ሁሉ እሺ በማለት በተለይ በኮሶቮ ጉዳይ ላይ የተስማሙበትን ገላጋይ ሃሳብ አጥብቀው ይተቻሉ ። ታዲች ለአውሮፓ ህብረት አባልነት ሲሉ የሰርቢያን መሬት ሸጠዋል ፣ ሃገሪቱን በጥቅም ለውጠዋል በማለት እየከሰሱዋቸው ነው ። በተለይ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር እና የሰርቢያ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ  ፓርቲ መሪ ቮይስላቭ ኩስቱኒቻ ሰርቢያ አንዳችም የምትደሰትበት ውጤት አላገኘችም ነገሩ ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ ዓይነት ጨዋታ ነው ብለዋል ። በኩስቱኒቻ አባባል ሰርቢያ ለአውሮፓ ህብረት አባልነት ለመታጨት ብዙ ዋጋ ከፍላለች ፤ አሁን የሚፈነጥዘውም እንደርሳቸው ፣ ህዝቡ ወይም ስራ አጡ ሳይሆን ባለሥልጣናቱ ና ከነርሱ የተጠጋው ክፍል ብቻ ነው ። 

ለአውሮፓ ህብረት አባልነት መታጨት ወደ ህብረቱ ለመግባት የመጀመሪያው ደረጃ ነው ። ሰርቢያ ለአባልነት የሚያስፈልገውን ድርድር ለመጀመር ምናልባትም አንድ ዓመት ያህል መጠበቅ ይኖርባታል ። ድርድሩም ለዓመታት ለወስድ ይችላል ። 7.5 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ወደብ አልባዋ ሰርቢያ ባለፉት ጦሮነቶችና ማዕቀቦች ምክንያት ከባድ የኤኮኖሚ ችግሮች ከፊቱ የተጋረጡባት ሃገር ናት ። ስራ አጥነት በሰርቢያ ወደ ሃያ በመቶ ነው ቢባልም ጉዳዩን የሚያጠኑ ወገኖች ግን ከዚያም በላይ ይሆናል ሲሉ ይከራከራሉ ። ሃገሪቱ የአውሮፓ ህብረትን መቀላቀሏ ለነዚህ ችግሮቿ መፍትሄ ይሆናል የሚል ተስፋ አለ ። ሰርቢያ ወደ ህብረቱ ለመግባት የግድ ለኮሶቮ እውቅና መስጠት እንደሌለባት ፣ ለአካባቢው መረጋጋት ሲባል ግን ቤልግሬድና ፕርሽቲና ግንኙነታቸውን እንዲያሻሽሉ ነው የጠየቀው የአውሮፓ ህብረት ። እስካሁንም በህብረቱ አግባቢነት ሰርቢያና ኮሶቮ በርካታ ልዩነቶቻቸውን አጥበዋል ። ለምሳሌ ኮሶቮ በዓለም ዓቀፍ ጉባኤዎች ላይ በምን መልኩ እንደምትወከል መግባባት ላይ ደርሰዋል ። በስምምነቱ  መሠረት ፕሪሽቲና የባልካን ሃገራትን ቤልግሬድ ዕውቅና ባትሰጣትም እንድትሳተፍ መግባባት ላይ ደርሰዋል ። የድንበር አስተዳደር ጉዳዮችም ላይም ተስማምተዋል ።

Symbolbild Kosovo Serbien Abkommen Einigung EU Graffiti Pristina
ምስል picture-alliance/dpa

ይህ ብቻ ግን በቂ አይደለም ወደፊት በሃይልና በቴሌኮምኒኬሽን ዘርፎች ባሉ ችግሮች ላይ መወያየት ይኖርባቸዋል ። በሚቀጥሉት ወራት የአውሮፓ ህብረት የሥራ አስፈፃሚ ኮሚሽን  ከኮሶቮ ጋር ያላትን ግንኙነት መሻሻል አለመሻሻሉን እንዲሁም ሌሎች ማሻሻያዎችንም ይገመግማል ።ከዚህ በኋለ ነው ሰርቢያ ለህብረቱ አባልነት የሚያስፈልገውን ድርድር ለመጀመር ዝግጁ መሆንዋ የሚወሰነው ። ያም ቢሳካ እንኳን እንደ ቱርክ ካሉ ሃገራት ልምድ በመነሳት ሂደቱ በቀላሉ የሚያልቅ እንደማይሆን ነው የሚገመተው ። ከዛሬ 13 ዓመት በፊት ለህብረቱ አባልነት የታጨችው ቱርክ በተወሰኑ አባል  ሃገራት ተቃውሞ እስካሁን የአባልነት ጥያቄዋ እንደተገታ ነው ። መቄዶንያም ተመሳሳይ ሁኔታ ውስጥ ነው የምትገኘው ። የኮሶቮም ወደፊት የሚታይ ይሆናል ።

ሂሩት መለሰ

ተክሌ የኋላ