1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሠብዓዊ መብት ጥሰት ለውጥ 

ሐሙስ፣ ግንቦት 1 2011

ኢትዮጵያ ዉስጥ በተለያዩ አካባቢዎች በሚከሰቱ ግጭቶች ዜጎች ይገደላሉ፣ ይቆስላሉ፤ ይፈናቀላሉ። የመብት ተሟጋቾች እንደሚሉት ዜጎች የመኖር ዋስትናና ፍትህ ተነፍገዋል። ይሁንና መንግሥት የመሰረተዉ የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከሌሎች የመብት ተሟጋቾች የሚሰማዉን ትችትና ወቀሳ አይቀበለዉ።

https://p.dw.com/p/3IEsc
Äthiopische Menschenrechtskommission
ምስል DW/G. T. Hailegiorgis

ከለውጥ በሃላ የዜጎች የሰብዓዊ መብት ዋስትና

የኢትዮጵያ መንግስት ባለፈዉ አንድ ዓመት በዜጎችን ላይ የሚፈፅመዉ የሰብአዊ መብት ጥሰት መቀነሱን የተለያዩ የመብት ተሟጋች ድርጅቶች አስታዉቀዋል። ይሁንና የጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አሕመድ መንግሥት፣ ሌሎች ቡድናት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ወይም ግለሰቦች በሰላማዊ ሠዎች ላይ የሚያደርሱትን ጥቃት አይከላከልም፤ ሥርዓት አልበኝነትም አይቆጣጠርም በዚሕም ሰበብ ኢትዮጵያ ዉስጥ ሰብአዊ መብት የሚጥሰዉ ወገን ተቀየረ እንጂ ጥሰቱ ካለፈዉም የከፋ ነዉ ባዮች አሉ። በተለያዩ አካባቢዎች በሚከሰቱ ግጭቶች ዜጎች ይገደላሉ፣ ይቆስላሉ፤ ይፈናቀላሉ፣ ሐብት ንብረታቸዉም ይዘረፋል፣ ይጠፋልም። የመብት ተሟጋቾች እንደሚሉት ዜጎች የመኖር ዋስትናና ፍትህ ተነፍገዋል። መንግሥት ይሕን ሁሉ በደል ለመቆጣጠር ትኩረት እንዳልሰጠው  ይደመጣል። ይሁንና መንግሥት የመሰረተዉ የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከሌሎች የመብት ተሟጋቾች የሚሰማዉን ትችትና ወቀሳ አይቀበለዉ። የጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ መንግስት ሥልጣን ከያዘ ወዲሕ ኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት አያያዝ የተሻሻለ ሁኔታ ላይ መኖሩን አቶ ማርሴ አሰፋ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ተጠባባቂ ዳይሬክተር ለዶቼ ቤሌ ተናግረዋል። «ከመንግሥት ለውጥ በሃላ ታስረው የነበሩ የፖለቲካ እስረኞችና ጋዜጠኞች እንዲፈቱ ማድረግ፣ የምርጫ ህጉን ማሻሻል፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ማስፋት ነው ኮሚሽኑ ያየው። ከለውጡ ወዲህ የሰብዓዊ መብት አያያዝ የተሻሻለ ሁኔታ እንዳለ አሳይቷል።» ይሁንና አሁንም የሰብአዊ መብት ጥሰት መኖሩን አቶ ማርሴ አልካዱም።ጥሰቱ ግን በመንግስት ወይም በባለሥልጣናት የሚፈፀም ወይም በነሱ ስሕተት የሚደርስ አይደለም ባይ ናቸዉ። ኮሚሽኑ በምርመራ አረጋገጠ እንዳሉት፤ የመብት ጥሰቶቹ የሚፈፀሙት «ጥቅም ፈላጊ» ባሏቸው ቡድኖች እንደሆነ ነው። «በተለያዩ ቦታዎች ግጭቶች ይቀሰቀሳሉ። መፈናቀል እያስከተለ ያለው የተለያየ ፍላጎት ያላቸው ቡድኖች እንደሆነ ነው። አብዛኛውን ጊዜ መፈናቀሉ በመንግሥት በኩል ያለ ስህተት ሳይሆን የተለያየ ፍላጎት ያላቸው ቡድኖች እንደሆነ ነው።» ኮሚሽኑ የሰብዓዊ መብት ጥሰትን ለመከላከል እየሰራ እንዳለ ጠቅሰው፤ ምርመራ የሚያካሂድ የስራ ክፍል እንዳለው ገልጸዋል። ተቀዳሚ ስራውም በግለሰብም ሆነ በሚፈጠሩ ግጭቶች የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሲከሰት ምርመራ ያደርጋል፤ መንግስትን ያማክራል፣ ክትትልም ያደርጋል ይላሉ አቶ ማርሴ። «በግለሰብም ወደ ኮሚሽኑ መተው አቤቱታ ከሚያቀርቡ በተጨማሪ በተለያየ አካባቢ የሚከሰቱ ግጭቶች የሚያስከትሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ዙሪያ ላይ ምርመራ ያካሄዳል። ምርመራውን መሰረት አድርጎ መንግሥትን የማማከር ስራ ነው የሚሰራው።» የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሲከሰት መርመራ ማካሄድ፣ ክትትልና ጥበቃ ማድረግ፣ ማህበረሰቡ መብቱ አውቆ ማስከበር እንዲችል ማሳወቅ እንደሆነ ይህንኑ ኮሚሽኑ «ከሞላ ጎደል»  «እያከናወነ ነው» ብለዋል።


ነጃት ኢብራሂም

ነጋሽ መሐመድ