1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ማርቲን ሹልስ ለሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ መሪነት በሙሉ ድጋፍ ተመረጡ

ሸዋዬ ለገሠ
ሰኞ፣ መጋቢት 11 2009

በመጪዉ ዓመት መስከረም ወር ጀርመን በምታካሂደዉ ምርጫ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክልን እንደሚፎካከሩ የሚጠበቁት ማርቲን ሹልስ፤ ሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ መሪ እንዲሆኑ በሙሉ ድምጽ ተመረጡ።

https://p.dw.com/p/2ZaXo
Deutschland Martin Schulz zum neuen SPD-Chef gewählt
ምስል Reuters/F. Bensch

የአዉሮጳ ኅብረት ምክር ቤት ፕሬዝደንት በመሆን ያገለገሉት የ61 ዓመቱ ሹልስ፤ ግራ ዘመሙን ሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ ለመምራት የአባላቱን መቶ በመቶ ድምጽ ያገኙ የመጀመሪያዉ ፖለቲከኛ መሆናቸዉ ተነግሯል። የፓርቲዉ ጉባኤ በተካሄደባት በርሊን ከ600 ለሚበልጡ የፓርቲዉ ተወካዮች ባደረጉት ንግግር «ፍትህ፣ አክብሮት እና ክብር» የፓርቲያቸዉ የምርጫ ቅስቀሳ መርህ እንደሚሆን ገልጸዋል።

«ማኅበራዊ ፍትህ ከመደብ ትግል መማሪያ መጽሐፍት ላይ የሚገኝ አስተሳሰብ አይደለም፤ ይልቁንም  ለሁሉም የጋራ እድል የተሰጠና መከበር የሚገባዉ የአንድ ነፃና እና ወደፊት የተራመደ ማኅበረሰብ መሠረታዊ ሁኔታ ነዉ።»

ሹልስ ፓርቲዉን ወክለዉ ሜርክልን እንደሚፎካከሩ ይፋ ካደረጉበት ጊዜ አንስቶ ሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ በሕዝብ አስተያየት መመዘኛዎች የ30 በመቶ የድጋፍ ድምጽ ጭማሪ አሳይቷል። ከአዉሮጳ ኅብረት ኃላፊነታቸዉን አጠናቀዉ ወደሀገራቸዉ ከተመለሱ ወዲህም በተለያዩ የጀርመን ግዛቶች በመገኘት የህዝቡን ፍላጎት ለመረዳት ኅብረተሰቡን ማነጋገራቸዉ ተነግሯል። ማርቲን ሹልዝ ከአሜሪካዉ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ የምርጫ ቅስቀሳ የተቀሰመዉን ትምህርት መሠረት በማድረግም «አንድ ህዝብ እንዳለ ማዉገዝ በጀርመን ቦታ የለዉም።» ማለታቸዉም ተገልጿል። 

ሸዋዬ ለገሠ

አዜብ ታደሰ