1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሙጋቤ ቃለ መሐላ ፈጸሙ

ሐሙስ፣ ነሐሴ 16 2005

የዚምባቡዌዉ ፕሬዝዳንት ሮበርት ሙጋቤ ለተጨማሪ አምስት ዓመት ዘመነ-ሥልጣን ዛሬ ቃለ መሐላ ፈፅመዉ በያዙት ሥልጣን ፀኑ።

https://p.dw.com/p/19Urk
ምስል Getty Images/Afp/Alexander Joe

ዚምባቡዌን ከነፃነት ጊዜ ጀምሮ የመሩት ሙጋቤ በቅርቡ በተደረገዉ ምርጫ ከተሰጠዉ አጠቃላይ ድምፅ ስልሳ-አንድ ከመቶዉን በማግኘት ነበር ያሸነፉት።የሙጋቤ ዋነኛ ተቀናቃኝ የእስካሁኑ ጠቅላይ ሚንስትር ሞርጋን ቻንግራይና MDC በሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ ፓርቲያቸዉ የምርጫዉን ሒደትና የተጭበረበረ በማለት ዉጤቱን ዉድቅ አድገዉታል።ቻንግራይ በዛሬዉ የሙጋቤ በዓለ-ሲመት ድግስ ላይም አልተገኙም።ሙጋቤ ቃለ-መሐላ ከፈፀሙ በሕዋላ ባደረጉት ንግግር የሚተቹ ተቃዋሚዎቻቸዉን «ከፈለጋችሁ ታነቁ» በማለት ወርፈዋቸዋል።በሐራሬ የዶቸ ቬለ ዘጋቢ ኮሎምቦስ ማሕፍሁንጋ እንደሚለዉ የሰማንያ ዘጠኝ አመቱ አዛዉንት በአዲሱ ዘመነ-ሥልጣናቸዉ የተከፋፈለችዉን ሐገራቸዉን ማቀራረብ እና ምጣኔ ሐብቷን ማሻሻል አለባቸዉ።

Amtsvereidigung Robert Mugabe 22.08.2013
የሙጋቤ ቃለ መሃላ ሥርዓትምስል Getty Images/Afp/Alexander Joe

«ባሁኑ ጊዜ ዋና ትኩረት የሚያስፈልገዉ ነገር ምጣኔ ሐብቱ እንዲያንሠራራ ማድረግ ነዉ።ላለፉት አስር ዓመታት፥(ከዚያም በላይ) ምጣኔ ሐብታችን እንዲያዉ በሐኪሞች ቋንቋ በነብስ አድን ክፍል ዉስጥ ነዉ ያለዉ።ይሕ ዋናዉ ትኩረት መሆን አለበት።ሥራ መፍጠር እና በአገልግሎት መስኩም ትምሕርቱን ወደነበረበት መመለስ፥ ሆስፒታሎችንና መንገዶችን ማሻሻል ያስፈልጋል።»

ምዕራባዉያን ሐገራት ከአምስት ዓመት በፊት ተደርጎ በነበረዉ አወዛጋቢ የምርጫ ዉጤት ሰበብ በፕሬዝዳት ሙጋቤ እና በከፍተኛ ባለሥልጣኖቻቸዉ ጋር የጣሉትን ማዕቀብ አላነሱም።ሙጋቤ በዛሬዉ ንግግራቸዉ ምዕራባዉያን ሐገራትንም «ሞራል ወይም ሕሊና ቢሶች» በማለት አበሻቅጠዋቸዋል።

የ89 ዓመቱ ሮበርት ሙጋቤ በዛሬዉ ዕለት ለቀጣይ አምስት ዓመታት የሀገሪቱ ፕሬዝደንት ሆነዉ ቃለ መሃላ ፈጸሙ። ሙጋቤ ባለፈዉ ሐምሌ ወር ማለቂ ላይ በተካሄደዉ ፕሬዝደንታዊ ምርጫ 61 በመቶ ድምጽ ማግኘታቸዉን የሀገሪቱ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሰኞ ዕለት ነዉ ያጸደቀዉ።

Morgan Tsvangirai
ቻንጊራይምስል JEKESAI NJIKIZANA/AFP/Getty Images

ተፎካካሪያቸዉ ጠቅላይ ሚኒስር ሞርጋን ቻንጊራይ ዉጤቱ ተጭበርብሯል ቢሉም ያንን የሚደግፍ መረጃ ለማግኘት ብሄራዊ የምርጫ ኮሚሽኑ አልተባበረኝምና ፍትህ አላገኝም በማለት ቀደም ብለዉ ክሱን ማቋረጣቸዉን አመልክተዉ ነበር። ከፍርድ ቤቱ ዉሳኔ በኋላ ዛሬ ሙጋቤ ቃለ መሃላ ሲፈጽሙም ብሪታኒያ እሳቸዉ ዳግም መመረጥ በገለልተኛ ወገን አቤቱታዉ ሳይጣራ ተአማኒነት ይጎድለዋል ብላለች። ላለፉት 33ዓመታት የዚምባቡዌ መሪ የነበሩት ሙጋቤ በነቃፊና ደጋፊዎቻቸዉ አይን እንዴት ይታያሉ? ለምንስ ስልጣን መልቀቅ አይፈልጉም? ሎንዶን የሚገኘዉን ዘጋቢያችን ድልነሳ ጌታነህን አንዳንድ ነጥቦች በማንሳት ቀደም ብዬ በስልክ አነጋግሬዋለሁ፤

ነጋሽ መሐመድ/ ድልነሳ ጌታነህ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ