1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

መቐለ ለቤት ሰሪዎች ቦታ ስትሰጥ ገበሬዎች በካሳ ጉዳይ ቅሬታ እያቀረቡ ነው

ሰኞ፣ ጥር 20 2011

የመቐለ ከተማ አስተዳደር ለ6880 የቤተሰብ መሪዎች ቤት መስሪያ መሬት ሰጠ፡፡ በሌላ በኩል የመሬቱ ባለቤት የነበሩ አርሷደሮች መንግስት በቂ ካሳ አልሰጠንም ይላሉ፡፡

https://p.dw.com/p/3CKxB
Äthiopien Mekele Situation der Eritrea-Flüchtlinge
ምስል DW/James Jeffrey

ለ6880 የቤተሰብ መሪዎች ቤት መስሪያ መሬት ተሰጥቷል

 ኢትዮጵያ ውስጥ ካሉ የነዋሪዎቻቸው ቁጥር በየጊዜው እየተበራከተ ከመጡ ከተሞች መካከል አንድዋ የሆነችው መቐለ የመኖርያ ቤት ችግር እጅግ እየፈተናት ይገኛል፡፡

የነዋሪዎችዋ ችግር ለመፍታት የከተማዋ አስተዳደር በማሕበር ለተደራጁ ነዎሪዋች በሰባ ካሬ ሜትር የሚያርፍ ቤት እንዲገነቡ መሬት በማስተላለፍ ላይ ይገኛል፡፡ በአንደኛ ዙር ከ11 ሺህ ቤተሰብ መሪዎች እድሉን ቢያገኙም እስካሁን ያለቀ ቤት ግንባታ የለም፡፡

ትላንት እሁድ በተመሳሳይ በሁለተኛ ዙር ለ6880 ቤተሰብ መሪዎች ቤት መስርያ መሬት አስረክቧል፡፡ በተለይም በመካከለኛና ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የከተማዋ ነዎሪዋች ለማገዝ ተብሎ የሚተገበረው መርሐግብር መሬት ላገኙ የከተማ ነዋሪዎች ደስታ፣ ለፕሮጀክቱ ተብሎ ለተፈናቀሉ የመቐለ ዙርያ አርሶአደሮች ቅሬታ እየፈጠረ ነው፡፡

ቤት የሚገነቡበት መሬት ካገኙ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሪት ንግስቲ ሃይሉ ከዚህ ቀደም በቤት ኪራይ ተቸግራ መቆየትዋ በመግለፅ አሁን ከችግርዋ የምትወጣበት ተስፋ ማግኘትዋ ነግራናለች፡፡ በሌላ በኩል ለመኖርያ ቤቶቹ ግንባታና ኢንቨስትመንት ከማሳቸው የተነሱ አርሶአደሮች ደግሞ መንግስት ይዞታችንን ሲያስለቅቅ በቂ ካሳና ድጋፍ አላደረገልንም ይላሉ፡፡

አርሶአደሮቹ እንደነገሩን ከይዞታቸው ሲነሱ በካሬ 2ብር ከ30 ሳንቲም ብቻ እንደታሰበላቸው ገልፀዋል፡፡ ይህ ከከተማዋ የኑሮ ሁኔታ አንፃር ዝቅተኛ መሆኑ ነግረውናል፡፡ በጉዳዩ ላይ የአካባቢው የመንግስት ስራ ሐላፊዎች ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም፡፡
ሚሊዮን ኃይለስላሴ
አዜብ ታደሰ